2022-08-14 14:03:18
አዲስ መጽሐፍ በገበያ ላይ
+ + + + + + + + + + + + + +
ሰላም ለ’ናንተ ይሁን ውድ ቤተሰብ!!! የሚፈሩና በይሉኝታ የሚታለፉ ብሎም ጠለቅ ያሉ ርዕሶች ዙሪያ እየተሽከረከረ ሁለንተናዊ ልዕልና ያለው ሰብዕናዊና ሕብረተሰባዊ እድገት እንዲኖር እንደሚተጋ የሚታወቀው ኢ/ር እንዳላማው አራጌ ሁለተኛ መጽሐፉን አሳትሟል። ኢንጅነሩ በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ የሲቪል ምኅንድስና መምህር፣ የነገረ-ሕይወትና የነገረ-ኢትዮጵያ ተመራማሪ ብሎም የኒትሮ ምሕንድስና ኃ/የተ/የግ/ኩባንያ መስራች መሆኑን መጽሐፉ ላይ የተቀመጠው መረጃ ያሳያል። ኢንጅነሩ በራሱ ማህበራዊ ድረ-ገጽ ላይ እንዳሳወቀን፡ የመጀመሪያ መጽሐፉ ከሆነው «ግንጥል ልዕልና በኢትዮጵያ ልደት» በኋላ በነበሩት ያለፉት አራት አመታት አራት መጽሐፍትን የደረሰ ሲሆን እነኝህን ስራዎች በተከታታይ ሊያቀርብ መዘጋጀቱን አሳውቋል። የእነኝህ ስራዎቹ ቀዳሚ አሁን የታተመው «ራኤል» ቁጥር-1 ነው። ለዚህ ስኬቱ ደራሲውን እንኳን ደስ ያለህ እያልን ከእኛ ጋር አብሮ ለመስራት ስለመረጠንና መጽሐፉን እንድናከፋፍል ስለቻልን ያለንን አክብሮትና የተሰማንን ደስታ እንገልጻለን።
ስለሆነም፡ ሀሁ መጽሐፍት መደብር መጽሐፉን በያላችሁበት ለማድረስ ዝግጁ መሆኑን ስንገልጽ በደስታ ነው። በሀገሪቷ የተለያዩ ቦታዎች ያላችሁ መጽሐፍት መደብሮች ከዚህ በታች ባለው አድራሻችን መሰረት ብታገኙን መጽሐፉን እናደርሳችኋለን። ከሰኞ ጀምሮ አዲስ አበባ ውስጥ ባሉ መጽሐፍት ቤቶች ሁሉ የምናደርስ ይሆናል። እንዲሁም ከስር በተጠቀሱት አድራሻዎች መሰረት በእኛ መደብሮች መጽሐፉን ታገኙታላችሁ። አንብቡት፡ ብዙ እንደምታተርፉበት እምነታችን ነው! ስለ መጽሐፉ የበለጠ መረጃ ለማግኘት ከስር ይመልከቱ↓
አድራሻ፦
መደብር ቁ.1፡ አ.አ. ናሽናል ታዎር
መደብር ቁ.1፡ ሜክሲኮ ደብረ ወርቅ ህንፃ
ስ.ቁ. 09 11 00 67 05
ሀሁ መጽሐፍት መደብር - አዲስ አበባ
************
ስለ መጽሐፉ….
********
ደራሲው ስለ ሁለተኛ መጽሐፉ እንዲህ ይላል፡-
«ሁለተኛው መጽሐፌ» እንደ ስሙ ‹‹ራኤል›› ነው፤ ምን ማለቴ እንደሁ ስታነ’ቡት ታወቃላችሁ።»
እንዲሁ፡ የደመወዝ ጎሽሜ «ዓሥራ ሥድሥት» የተሰኘው መጽሐፍ የሽፋን ገጽ ላይ ምስክርነት የሰጠው የ‹‹እግዚእ፡ The Wisdom Compass to Eternal Life›› መጽሐፍ ደራሲ አቤል ጋሼ በተመሳሳይ ዘውግ ውስጥ ስላለውና በብዙ ሀሳቦች ስለታጨቀው ይህ የመኃንዲሱ መጽሐፍ እንዲህ ሲል የሽፋን የጀርባ ሽፋን ገጽ ላይ ምስክርነት ሰጥቷል፡- ↓
//«ይኸ ደራሲ ምሥጢር ይወዳል። ምሥጢር ይፈልጋል፤ ምሥጢር ያገኛል። በምሥጢር ይናገራል። ይፈላሰፋል፣ ይመረምራል። “ግንጥል ጌጥ በኢትዮጵያ” በሚል ኮርኳሪ ጽንሰ ሃሳብ የመጀመሪያ መጽሐፉን ያስነበበን ደራሲ ኢንጂነር እንዳላማው አራጌ፡ ዛሬም “ራኤል” በሚል ሌላ ምሥጢራዊ ጽሁፍ ውስጥ የሚገርሙ የሚታየውንና የማይታየውን አለም ምሥጢራት ኢትዮጵያን ባማከለ ሁኔታ ይዞልን ቀርቧል። ጊዜው እንደሚጠይቀው ደራሲው የትውልዱ ምልክት ነው። አጠያቂ ነው፣ ራሱን ከመንጋ አስተሳሰብ ለይቶ በተሰጠው ችሎታ ስለ ነገረ ፍጥረት፣ ስለ እግዚአብሔርና ስለ ሰውነት ያስባል፡ ይመረምራል። ስለ ሀገሩ መንፈሳዊ ዕጣ ፈንታ ያጠይቃል። ፈጣሪ አለምን የፈጠረባቸውን አይነተኛ እሳቤዎችና ምልክቶች በቁጥር ቀመርና ስሌት ያሰላስላል፤ ጊዜንና የፍጥረትን ብሂል ይመረምራል። በኢትዮጵያ ገዳማትና አብያተ ክርስቲያናት የተደበቁ ጥንታዊ መጻሕፍትና ድርሳናት ውስጥ ተደብቀው የሚኖሩ ብዙ ምሥጢራት እንዳ’ሉ የሚያምነውና ራሱን “የጥበብ ብላቴና” የሚለው ይህ ደራሲ፡ እነዚህ የጥበብ ዘለላዎችን ከብዙ አለማት ጎትቶ ያመጣና ትረካውንና ፍለጋውን ግን የምሥጢራት ማዕከል ከሆኑት “ቅዱሱ ሀይቅ” በሚለው የጣና ሀይቅ ደሴቶችና የወሎ ቅዱሳን መካናት ላይ ያነጣጥራል። ጠቢባንን ፈልጎ መንፈሳዊ እውቀትን ይጎለጉላል።
ከዚህ በፊት ጥበብን በመሻት ይልቁንም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በውስጧ አምቃ የያዘቻቸውን ምሥጢራት የመረመሩት አንጋፋ መርማሪዎችን እነ የኔታ አስረስ የኔሰው፣ እነ መራሪስ አማን በላይ ሌሎችም እንደነሱ ያሉ የሰሯቸውን ሥራዎች አንብቦ ያገኘውን ከርሱ ምልከታና አጠይቆ ጋር አሰናስሎ፡ ይልቁንም በሳይንስ እውቀት ያዳበረውንና ከብዙ ቦታ የለቀማቸውን የጥበብ ነጠብጣቦች፡ በአስገራሚ ትንታኔ ውስጥ አካትቶ ያሳየናል። የዚችን አለም አሰራር በመንፈሳዊ ዓይን ለሚመለከትና “የዚች አለም ምሥጢሯ ምን ይሆን?” ለሚል ተመራማሪ፡ ይህ ድርሰት ብዙ የሚያስብበት ሃሳብን ያቀርብለታል። ኢትዮጵያ ምሥጢር ነች። ሥጦታዋም መንፈሳዊ እሴቶች ናቸው። የእግዚአብሔር የጥብበ ጎተራ ነች ብሎ የሚያሳስብ ጽሁፍ ነው። ፊዚክስ፣ ቲኦሎጅ፣ ስነ ከዋክብት፣ አስትሮኖሚ፣ ነገረ ድኅነት በክርስትና እምነት ... ወዘተ… ሁሉም አብረው በዚህ ጽሁፍ ይ’መረመራሉ። ‹‹ግን ትውልዱ ይኸንን አያውቅም። የኢትዮጵያን ስጦታ ያውቃል?›› ጽሁፉ ትውልዱን ይሞግታል። ኢትዮጵያዊው የኢትዮጵያን ምሥጢር እንዲመረምር በኅሊና ጅራፍ ሊገርፍ ተነስቷል! 777 ቁጥር በመጀመሪያ መጽሐፉ ላይ ጎልቶ እንደወጣው ዛሬም በዚህ መጽሐፍ ይንከባለላል። ሌሎች የቀመር ትንታኔዎችን ተጠቅሞ ሰማያዊውን አለም ከሰው ማንነት ጋር እያሰናሰለ የመጨረሻውን ዘመንና የድኅነትን አንድምታ ያመሰጥራል። ቀመር ለሚወድ ይኸ ደራሲ እስኪጠግብ ድረስ ያጠጣዋል።
ደራሲው ስለክርስትናም ያጠይቃል። “በክርስቶስ ሁሉን እንችላለን” የሚለው ታላቅ አዋጅ እውን እንዲሆን ‹‹መክሊታዊ ክርስትና›› ያስፈልጋል ብሎ ይሰብካል። ብላቴናው ጥረቱ ሁሉ ለሀገሩ አንድ መልካም ነገር ማድረግ እንደሆነ በጽሁፉ ውስጥ መመልከት ይቻላል። በጠቅላላ በድርሰቶቹ ውስጥ እንደሚንጸባረቀው፡ ‹‹እንዴት ከገባንበት አረንቋ እንውጣ?›› የሚል ጭንቀት በውስጡ የሚዝመነመን መሆኑን መገመት አያዳግትም። በጽሁፉ ውስጥ ለሱ መልሱ አንድ ነው። ብላቴናው እንዲህ ይላል፡-
“ከግንጥሉ ‹‹የድኅነት ብቻ ክርስትና›› ወደ ሞገሳማው ‹‹መክሊታዊ ክርስትና›› መሸጋገርና ከቅድስተ ቅዱሳን እልፍኝ መቋደስ አ’ለብን። አሁን ካለንበት ሁለንተናዊ የሰብዕና ቀውስ ለመውጣትና ሀገሪቷን ብሎም ዜጎቿን በትንሳኤው ዘመን ለሚጠበቅባቸው ሀላፊነት ለማዘጋጀት፡ በተድበሰበሰው “ተሀድሷዊ የለውጥ መንገድ” ሳይሆን በትክክለኛዋ “ንስሓዊት የለውጥ መንገድ” መጓዝ አ’ለብን።”
ይኸ ደራሲ በመንፈሳዊ ቀመር እያሟሸ፣ በአዳዲስ ጽንሰ ሀሳቦች የአመክንዮ ሥርአታችንን ያጭራል። ትውልዱን ይሞግታል። ለሀገር ልዕልና የሚበጀውን መንገድ ይጠቁማል። ግንጥል ጌጥ ይዞ ሀገር እንደማይቆም አጥብቆ ይመክራል። በነፃነት አስበን ወደ ጥበብ-ተዋህዶ እንሻገር ይላል። ‹‹የተሟላ ሀገራዊ ልዕልና እንዴት ይገኛል?›› ያነበበ ሃሳቡን ይ’ረዳል። አንብቦ ደግሞ የራስን አስተሳሰብ ለማዳበር እድል ያገኛል። በርግጥም ይኸንን ጽሁፍ ያነበበ በአያሌው ያተርፍበታል። እኔ ብዙ አትርፌበታለሁ። መልካም ንባብ።»//
********************
ይነበብ!
ሀሁ መጽሐፍት መደብር - የመጽሐፉ አከፋፋይ
አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
335 views11:03