Get Mystery Box with random crypto!

#Nairobi በትግራይ ክልል ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ የተቋረጡ መሰረታዊ አገልግሎቶችን ማስጀመር መ | 🇪🇹 E.Z መረጃ 🇪🇹

#Nairobi በትግራይ ክልል ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ የተቋረጡ መሰረታዊ አገልግሎቶችን ማስጀመር መሆኑን የተደራዳሪ ልዑካን መሪዎች ተናገሩ

በትግራይ ክልል የተቋረጡ መሰረታዊ አገልግሎቶችን ማስጀመር ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ እንደሚሆን የኢትዮጵያ እና የህወሓት ተደራዳሪ ልዑካንን የሚመሩት አቶ ሬድዋን ሁሴን እና አቶ ጌታቸው ረዳ ተናገሩ። ሁለቱ የልዑካን መሪዎች ይህን ያሉት፤ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እና የትግራይ አማጽያን የጦር አዛዦች ዛሬ ሰኞ በኬንያ ዋና ከተማ ናይሮቢ ተገናኝተው ድርድር ከመጀመራቸው በፊት ባደረጉት ንግግር ነው።

የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የብሔራዊ ደህንነት አማካሪ የሆኑት አቶ ሬድዋን ሁሴን በዚሁ ንግግራቸው “የቴሌኮም፣ የኢነርጂ እና የባንክ አገልግሎቶችን መልሰን ማገናኘት አለብን። ከዚያ በፊት [ግን] ሰዎቻችን በቅድሚያ ምግብ እና መድኃኒት ይፈልጋሉ። ይህን ለማፋጠን እየሞከርን ነው” ሲሉ ተደምጠዋል። ሬድዋን ክልሎችን ጨምሮ ሁሉም ወገኖች “በባለፉ ጉዳዮች ከመዘፈቅ ይልቅ” ተስፋ እንዲፈነጥቁ እና መጪውን ጊዜ በጸጋ እንዲቀበሉ መንግስታቸው እያበረታታ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

ባለፈው ሳምንት ረቡዕ በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ የተደረገውን የሰላም ስምምነት ህወሓትን በመወከል የፈረሙት አቶ ጌታቸው ረዳ በበኩላቸው፤ “በስምምነታችን የተካተቱ ብዙ መደረግ ያለባቸው ነገሮች አሉ” ብለዋል። ከእነዚህ ተግባራት መካከል የአገልግሎቶች መጀመር አንዱ መሆኑንም አቶ ጌታቸው ገልጸዋል። የአገልግሎቶቹ ቁጥር ከፍ ሲል በተደራዳሪ ወገኖች መካከል የሚኖረው “መተማመን እና ግንኙነት አብሮ እንደሚጨምር”፤ “በሰዎች አዕምሮ ውስጥም ተስፋ እንደሚዘራ” የገለጹት አቶ ጌታቸው፤ “ለማስፈን እየሞከርን ያለውን ሰላም የበለጠ ያጠናክራል” ብለዋል።

@Ezmerejaet
@Ezmerejaet