የአማራ ብልጽግና ጽሕፈት ቤት ኃላፊው ግርማ የሽጥላ ተገደሉ
አቶ ግርማ የሺጥላ ከመሃልሜዳ ሲመጡ ጓሳ በተባለ አካባቢ በተተኮሰባቸው ጥይት መገደላቸውን ምንጮች ገልፀዋል።
መሃልሜዳ ሆስፒታል ለህክምና ቢገቡም ህይወታቸውን ማትረፍ እንዳልተቻለ ከቅርብ ሰዎች ለማወቅ ተችሏል።
ይህንንም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ በማህበራዊ የትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ አረጋግጠዋል።
"ሐሳብን በሐሳብ ማሸነፍ ያቃታቸው አካላት የወንድማችንን የግርማ የሺጥላን ነፍስ ነጥቀዋል። ልዩነትን በሠለጠነ መንገድ መፍታት ባህል በሆነበት ክፍለ ዘመን፣ በሐሳብ የተለየንን ሁሉ በጠመንጃ ለማሳመን መነሣት የጽንፈኝነት የመጨረሻው ጥግ ነው። ተወልዶ ባደገበት አካባቢ ፣ ከእኛ የተለየ ሐሳብ ማሰብ አልነበረበትም ብለው የሚያምኑ ነውጠኛ ጽንፈኞች የፈጸሙት አስነዋሪና አሰቃቂ ተግባር፣ ጽንፈኝነትን በጊዜ ታግለን ካላስወገድነው ወደ መጨራረስ እንደሚወስደን ጉልሕ ማሳያ ነው።
ነፍስህ በሰላም ትረፍ" -
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ