Get Mystery Box with random crypto!

ከትንሳኤ በኋላ ያሉ ዕለታት ማክሰኞ ቶማስ ይባላል እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ሲፈጥረው | የኦርቶዶክስ አስተምህሮዎች

ከትንሳኤ በኋላ ያሉ ዕለታት
ማክሰኞ
ቶማስ
ይባላል
እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ሲፈጥረው የሚያንቀላፋና የሚነቃ አድርጎ ፈጥሮታል፡፡
ማንቀላፋቱ የሞት ፤ መንቃቱ ደግሞ የትንሣኤ ምሳሌ መሆኑን ስናስብ ሁሌም ይደንቃል፡፡ አባቶቻችን የትንሣኤውን ምሥጢር በአበው እና በስነፍጥረትም ይመስሉታል፤ አቤል ከሞተ በኋላ በደሙ መናገሩ እና የሔኖክ ሳይሞት በእግዚአብሔር መሰወሩ የትንሣኤ ምሣሌ ናቸው፡፡ በተፈጥሮ ፀሐይ መውጣቷ የመወለዱ ፤ መጥለቋ የሞቱ እና ዳግመኛ መውጣቷ የትንሣኤው ምሣሌ ነው፡፡
አምላካችን ክብር ይግባውና በእርሱ ያመንን ሁላችን እንደምንነሳ የእርሱ ከሙታን መካከል በሥልጣኑ መነሳት ለሁላችን መነሳት በኩር መሆንና ማረጋገጫም እንደሆነ በቃሉም በተግባሩም ያስተማረን የትንሣኤ ጌታ ነው፡፡
በቃሉ "በመቃብር ያሉት ሁሉ ድምጹን የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል ፤ መልካም
ያደረጉ ለሕይወት ትንሣኤ ፤ ክፉም ያደረጉ ለፍርድ ትንሣኤ ይወጣሉና በዚህ አታድንቁ " (ዮሐ፭፡፳፱) እንዲሁም በተግባር የአራት ቀን ሬሳ አልዓዛርን አስነስቷል፡፡(ዮሐ፲፩፡፵፫)
የትንሣኤው ምሥጢር ሁላችን አምላክ የሆንበት ፤ በሁሉ ላይ ሥልጣን ያገኘንበት ፤ነጻ ወጥተን ነጻ አውጪ የሆንበት ፤ ከማይጠፋ ዘር እንደተወለድን ያረጋገጥንበት ፤ ሞትን የተዘባበትንበት ፤ ጨለማን የረታንበት ከዓለም እና ከዲያብሎስ እስራት ነጻ የወጣንበት ልዩ ክብር ኃይል እና ጸጋን ያገኘንበት ምሥጢር ነው፡፡

ይህቺ ዕለትም ይህንኑ ምሥጢር ነው የምትገልጥልን ሐዋርያው #ቶማስ ተብሎ ለምን ተሰየመ የሚለውን ከማየታችን በፊት ማነው የሚለውን ማየት ነገርን ከስሩ እንድንረዳው ይረዳናልና እውነት ሐዋርያው ቶማስ ማነው?
ሐዋርያው ቶማስ
ሐዋርያው ቶማስ የስሙ ትርጓሜ ፀሐይ ማለት ሲሆን የቀድሞ ስሙ ዲዲሞስ ይባላል ትርጉሙም ጨለማ ማለት ነው፡፡ ቁጥሩ ከ፲፪ ሐዋርያት ነው፡፡ (ማቴ፲፡፫)
(መዝገበ ታሪክ ክፍል ሁለት ገጽ፹፱) ፤ ሐዋርያ ማለት ደጅ አዝማች ፤ ቀላጤ ፤ ምጥው ፤ ፍንው ፤ ሂያጅ ማለት ነው፡፡(ወንጌል ቅዱስ ገጽ፻፶፱)
ሐዋርያው ቶማስ አልዓዛር በሞተ ጊዜ ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም አቅራቢያ ወደነበረው መቃብሩ ለመሄድ በተነሳ ጊዜ አይሁድ ሊገሉት ስለሚፈልጉ ሌሎቹ ሐዋርያት ክርስቶስ እንዳይሄድ ቢፈልጉም ቶማሰ ሌሎቹን ሐዋርያት በድፍረት እኛም ከእርሱ ጋር እንሞት ዘንድ አብረን እንሂድ ያለ የእምነት ሐዋርያ ነው፡፡ (ዮሐ፲፩፲፮)
ሐዋርያው ቶማስ ጌታችንን በእውነት እስከ ሞት ድረስ ያመነው ከሙታን ተለይቶ ከተነሳ በኋላ በ8ኛው ቀን እሁድ ሲሆን ሐዋርያት የነገሩትን ካላየው አላምንም ብሎ የተወጋ ጎኑን ከዳሰሰ በኋላ ነው፡፡ የእምነት ምስክርነቱም ጌታዬ አምላኬም ብሎ የገለጠው፡፡(ዮሐ፳፡፳፬)
ሐዋርያው ቶማስ መንፈስ ቅዱስን ከሐዋርያት ጋር ከተቀበለ በኋላ በ፵፮ ዓ.ም ገደማ በፋርስና በሕንድ እንዳስተማረ የተለያዩ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ይገልጣሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናንዙ ፤ ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ ፤ ቅዱስ አምብሮስ ተጠቃሾች ናቸው፡፡በመጨረሻም ብዙ ተአምራት እና ድንቅን አድርጓል፡፡ የሐዋርያው ቶማስ ተአምር እና አገልግሎት ብዙ ተአምራትን ቢያደርግም ለአሁኑ አንዱን ብቻ እናያለን፡፡ የኸውም የሉክዮስ አገልጋይ ሆኖ በሕንጻ ማነጽ እና በሐውልት መስራት ተቀጥሮ በሚሰራበት ወቅት የሉክዮስን ሚስት ከእነ ልጆቿ እና አገልጋዮቿ አሳምኖ ያጠመቀ ሐዋርያ ነው፡፡
ሐዋርያው ቶማስ ለሕንጻ እና ለሐውልት ማሰሪያ ከሉክዮስ የተቀበለውን ገንዘብና ወርቅ ሁሉ ለነዳያን በመመጽወቱ ንጉሡ እጅና እግሩን አሥሮ ቆዳውን አስገፍፎ ስልቻ አሰፍቶ በአሸዋ ሞልቶ አሸክሞት ገበያ ለገበያ ሲያዞረው የሉክዮስ ሚስቱ አርሶንዋ ተመልክታ በድንጋጤ ሞታለች፡፡ ንጉሡም ለሚስቴ መሞት ምክንያት አንተ ነህ ካዳንካት እኔም በአምላክህ አምናለው ሲለው ጌታችን ቁስሉን እንደ ውኃ አቀዝቅዞለት ካለችበት ሄዶ ስልቻውን ቢያስነካት ተነስታለች በዚህም ሉክያኖስ አምኖ ተጠምቋል፡፡
ሐዋርያው ቶማስ በራሱ ቆዳ በተሰራ ስልቻ እየተዘዋወረ ሙት አስነስቷል ፤ ድውያንን ፈውሷል አሕዛብን አሳምኖ አጥምቋል ፤ በቀንጦፍያ አንድ ሽማግሌ ሰባት ልጆቹን ገድለውበት ሰባቱንም ከሞት አስነስቷል ፤ በኢናስም በቃሉ ትምህርት እና በእጁ ተአምራቱ ብዙዎችን አሳምኖ አጥምቋል፡፡
የሐዋርያው ቶማስ ሰማእትነት
በሕንድ የነበሩት የብራሕማን እምነት ተከታዮች የቶማስ ትምህርት የእነርሱን እምነት የሚጻረር እና የሚያጠፋ መሆኑን ተገንዝበው ተነሱበትና በብዙ ስቃይ አሠቃይተው በ፸፪ዓ.ም በሰማዕትነት አርፏል፡፡ በሶርያ ትውፊት መሠረት የሐዋርያው የቶማስ አጽም በአንድ የሶርያ ነጋዴ ተወስዶ በኤዴሳ በክብር አርፏል፡፡ (የእግዚአብሔር መንግሥት ታሪክ በምድር ላይ አንደኛ መጽሐፍ ገጽ ፺፪)
ሐዋርያው ቶማስ ለምን ሰምቶ አላመነም?
እንደ ወንጌል ትርጓሜ ሐዋርያው ቶማስ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዝግ ቤት ገብቶ ሰላም ለእናንተ ይሁን ባለ ጊዜ አልነበረም ፤ በነገሩት ጊዜም አላመነም ያለማመኑ ምክንያት ሰዱቃዊ ስለነበር እና ሐዋርያቱ አይተው እርሱ ሰማው ብሎ ከሚያስተምር ማየት ወዶ ነው፡፡

"ጌታዬ አምላኬም" (ዮሐ፳:፳፰)

@Ethiopian_Orthodox
@Ethiopian_Orthodox