2022-06-08 12:11:15
"የታላቁ ህዳሴ ግድብ ኹሉንም የተፋሰሱ ሀገራት ተጠቃሚ ያደርጋል ብለን እናስባለን" የታንዛኒያ ፕሬዝዳንት ሳሚያ ሱሉሁ
ሰኔ 01/2014 ዓ.ም (አሚኮ) በታንዛኒያ የኢትዮጵያ ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ኾነው የተሾሙት አምባሳደር ሽብሩ ማሞ የሹመት ደብዳቤያቸውን ለታንዛኒያ ፕሬዚዳንት ሳሚያ ሱሉሁ አቅርበዋል።
አምባሰደሩ የሹመት ደብዳቤያቸውን ባቀረቡበት ወቅትም የኹለቱን ሀገራት የረጅም ዘመናት ግንኙነትና ቀጣይ የትብብር መስኮችን በሚመለከት ከፕሬዝዳንቷ ጋር ሐሳብ ተለዋውጠዋል።
አምባሳደር ሽብሩ በኢትዮጵያ ስላለው ወቅታዊ ሁኔታ እና መንግሥት እየወሰዳቸው ስላለው እርምጃ እንዲሁም ስለ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ለፕሬዝዳንቷ ገለጻ አድርገውላቸዋል።
በታንዛኒያ እስር ቤት በአስከፊ ችግር ውስጥ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ተለቀው ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱም አምባሳደሩ ለፕሬዝዳንቷ ጥያቄ አቅርበዋል።
ፕሬዝዳንትሳሚያ ሱሉሁ በኢትዮጵያ ስላለው ወቅታዊ ሁኔታና በአምባሳደሩ ስለቀረበላቸው ገላጻ ምሥጋና አቅርበዋል። ኢትዮጵያ ያጋጠማትን ችግር ለመፍታት መንግሥት እየወሰደ ያለውን እርምጃ እንደሚያደንቁም ተናግረዋል።
የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታን በሚመለከትም ግድቡ ኹሉንም የተፋሰሱ ሀገራት ተጠቃሚ የሚያደርግ ፕሮጀክት መኾኑንም መግለጻቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል ዐቀባይ ጽሕፈት ቤት የተገኘ መረጃ ያመላክታል።
በአዲስ አበባ የሚገኘውን የታንዛኒያ ኤምባሲ መሬት ጉዳይ በቅርብ መፍትሔ እንዲያገኝ የኢትዮጵያ መንግሥት ያሳለፈው ውሳኔ እንዳስደሰታቸው የተናገሩት ፕሬዝዳንቷ የኹለቱ ሀገራት ግንኙነት ዘመን በማይሸር ወዳጅነት የተሳሰረ በመኾኑ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
በታንዛኒያ እስር ቤት ውስጥ የሚገኙ ዜጎች እንዲለቀቁና ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ለማድረግ መንግሥታቸው ቀና ውሳኔ እንደሚሰጥበትም አረጋግጠዋል።
ፕሬዚዳንት ሳሚያ የታንዛኒያ ዜጎች ኢትዮጵያ በአቬየሽን ዘርፍ ሥልጠና እየወሰዱ መኾናቸውን አስታውሰዋል። ለዚህም ኢትዮጵያ በዘርፉ ሙያ የአፍሪካ ተምሳሌት መኾኗን በመጥቀስ ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ያላቸውን አድናቆት ገልጸዋል።
@Ethionews55
@ethionews55
261 views09:11