Get Mystery Box with random crypto!

የመምህራንና ትምህርት ቤት አመራሮችን የዲጂታል ቴክኖሎጂ አቅም ለመገንባት እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ፡ | Ministry of Education Ethiopia

የመምህራንና ትምህርት ቤት አመራሮችን የዲጂታል ቴክኖሎጂ አቅም ለመገንባት እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ፡፡
======================
ጥር 14/2016 ዓ.ም (ትምህርት ሚኒስቴር) በሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ለሚገኙ መምህራን እና የትምህርት ቤት የአመራሮችን የዲጂታል ቴክኖሎጂ አቅም ማሳደግን ኢላማ አድርገው በዓለም ባንክ እገዛ የተገዙ 3,790 ታብሌቶች ርክክብ ተደረጓል፡፡

በትምህርት ሚኒስቴር የአጠቃላይ ትምህርት ልማት ዘርፍ የመምህራንና ትምህርት አመራር መሪ ስራ አስፈጻሚ ዶ/ር ሙሉቀን ንጋቱ በርክክብ ስነስርዓቱ ላይ የተሰራጩት ታብሌቶች የትምህርት ስርዓቱን በቴክኖሎጂ በመደገፍ በኩል ትልቅ እገዛ እንዳላቸው ገለጸዋል።

ዶ/ር ሙሉቀን አክለዉም ታብሌቶቹ በተመረጡ ጉድኝት ማእከላት ትምህርት ቤቶች በኩል 18,000 የሚሆኑ የ1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን ተደራሽ እንደሚያደርጉ ጠቅሰው ለታለመለት ዓላማና ተግባር ብቻ እንዲውሉ አሳስበዋል፡፡

በትምህርት ሚኒስቴር የአጠቃላይ ትምህርት ልማት ዘርፍ የመምህራንና ትምህርት አመራር ዴስክ ኃላፊ የሆኑት ወ/ሮ አሰግድ መሬሳ በበኩላቸው የታብሌቶቹ ስጦታ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት መምህራን የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎት በማሻሻል መምህራን የመማር ማስተማር ተግባርን በዲጂታል ቴክኖሎጂ አስደግፈው አንዲሰጡ ለማስቻል፣ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት መምህራንና ትምህርት ቤት አመራሮች አጫጭር የስራ ላይ አቅም ማጎልበቻ ስልጠናዎችን በዲጂታል ቴክኖሎጂ ለማገዝና አጠቃላይ የመምህራን ስልጠና ስርዓትን ዲጅታላይዝ ለመድረግ ያለመ ነው ብለዋል።

በርክክቡ ወቅትም ስራው ከዓለም ባንክ ጋር በጋራ እየተሰራ መሆኑንና በ2015 ዓ.ም 47 2ኛ ደረጃ ት/ቤቶችን ማእከል ያደረገ 1000 ታብሌቶች ለክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተሰራጩ መሆኑ ተገልጿል፡፡