Get Mystery Box with random crypto!

#ለወላጆች ' ወላጆች ያምኑናል ብለን ተስፋ እንደርጋለን ' - ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ የ12ኛ ክፍል | Educate Ethiopia

#ለወላጆች

" ወላጆች ያምኑናል ብለን ተስፋ እንደርጋለን " - ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ

የ12ኛ ክፍል ብሄራዊ ፈተና ተፈታኞች ከቤተሰባቸው ርቀው ነው ፈተናውን የሚወስዱት በዚህ ወቅት ስልክን ጨምሮ ምንም አይነት የመገናኛ ቁሳቁስ ይዘው መሄድ አይችሉም ፤ ተማሪዎቹ ከቤተሰቦቻቸው ጋር መገናኘት ባለመቻላቸው የሚፈጠር #የስነልቦና_ጫና ይኖር ይሆን ? ይሄ እንዴት ይታያል ? የወላጆች ኃላፊነትስ ምንድነው ?

ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ (የትምህርት ሚኒስትር) ለብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ የተናገሩት ፦

" .... ሆን ብለው ችግሮችን ለመፍጠር ካሰቡ ብዙ ምክንያቶችን ማድረግ ይቻላል ግን አሁን እነዚህ ልጆች ማትሪክ ሲያልፉ ከቤተሰቦቻቸው ወጥተው ሊኖሩ ነው አይደለም እንዴ ለረጅም ጊዜ ፤ ለአራት ቀን ለአምስት ቀን ሲሆን እንደውም በዛ እድሜ ላይ ያሉ ልጆች ደስ እያላቸው የሚሄዱ ነው የሚመስለኝ።

ይሄ አድቬንቸርም ነው ከቤት ወጥተው ፣ ዩኒቨርሲቲ ሄደው ይፈተናሉ ይሄ አዲስ ነገር ነው። በዚህ አመት ለሚያደርጉት ይሄ ነገር የተጀመረው የመጀመሪያዎቹ ተማሪዎች ስለሚሆኑ ለልጆቻቸውም የሚነግሩት ነገር ይዘው ነው የሚሆነው ፤ ታሪካዊም ነው። ለመጀመሪያ ጊዜ ነው ይሄ የተደረገው ፤ በእኛ ጊዜ ነው ይሄ የሆነው ፣ ይሄ ነገር ምን አለው የሚለውን ያያሉ።

በእኛ በኩል ዋና ኃላፊነታችን ሰላማቸው እንዲጠበቅ ማድረግ ፣ በምግብ ችግር እንዳይኖርባቸው ማድረግ ፣ ህክምና ማዘጋጀት በየዩኒቨርሲቲዎቹ ይሄንን እያዘጋጀን ነው።

ሰላም መግባታቸውን ፣ ችግር በሚኖር ጊዜ ለማሳወቅ ከየክልሉ ትምህርት ቢሮ ተወካዮች አሉ አብረው የሚመጡ ወደ ግቢ አይገቡም ፤ ግን ችግር በሚኖር ጊዜ ከእነሱ ጋር ግንኙነት እየተደረገ ለቤተሰቦቻቸው መንገር የሚቻልበትን መንገድ አስቀምጠናል።

ሁሉን ነገር ለማየት ሞክረናል ይሄ ነገር አዲስ ስለሆነ ቀላል የሎጅስቲክስ ስራ አይደለም አንድ ሚሊዮን የሚደርስ ሰው አንቀሳቅሶ ይሄን ማድረግ በተወሰነ ደረጃ እንደ ሀገርም ያውም ጦርነት እየተዋጋን ባለንበት ሁኔታ መንግስት ይሄን ማድረግ መቻሉ በእውነት የሚገርም ነው። እኛ ውስጥ ስላለንበትም እያየን ስለሆነ ነው ይሄን የምናገረው ቀላል የሎጅስቲክስ ስራ አይደለም።

እጅግ በጣም ብዙ ሰው ነው የሚሳተፍበት ወደ 8 ሺ የፌዴራል ፖሊስ ይሳተፍበታል ፣ ሰላሳ / አርባ ሺህ ፈታኞች ከየዩኒቨርሲቲው ወጥተው ይሳተፋሉ ፣ ብዙ ምግብ አብሳዮች ይሳተፋሉ። በአጠቃላይ ትልቅ ሀገራዊ እንቅስቃሴ ነው። እንደ ሀገርም ችሎታችንን አቅማችንን፣ በተወሰነ ደረጃ እየተጠናከረ ትላልቅ ነገሮችን ለመስራት ያለን ብቃት እየጨመረ የሚሄድበት ነው ፤ ስለዚህ ደስ የሚልም ነገር አለው።

ለቤተሰቦች የምንለው በተቻለን መጠን የልጆቻችሁን ኃላፊነት ወስደን ነው ይሄን ነገር የምንሰራው። እንደ ልጆቻችን ልንጠብቅ ፣ እንደ ልጆቻችን እንዳይራቡ እንዳይጠሙ ልናደርግ ፤ ምንም አይነት የደህንነት አደጋ ውስጥ እንዳይገቡ ተጠንቅቀን ነው ይሄንን ነገር የምናደርገው። ያ ማለት ግን ምንም ነገር አይፈጠርም ማለት አይደለም መቶ በመቶ ማረጋገጫ መስጠት አይቻልም።

ማንኛውም ተማሪ ወደዚህም ቦታ ባይመጣ ቤቱም ሆኖ ሊታመም ይችላል ግን በእኛ በኩል ከህክምና ጋር በተያያዘ የጤና ባለሞያዎችን በየቦታዎቹ ላይ አስቀምጠናል ፤ ችግር በሚኖር ጊዜ ልጆቹ ህክምና እንዲያገኙ።

ቁርሳ ፣ ምሳ እንዲሁም እራታቸውን እንመግባቸዋለን ፤ ምግብ እንኳን ስናዘጋጅ የሃይማኖት ፤ የባህል ነገሮችም እንዳይመጡ እሱን ሁሉ ጥንቃቄ እያደረግን ነው። ወላጆች ያምኑናል ብለን ተስፋ እንደርጋለን።

...ወላጆች ትልቅ ኃላፊነት አለባቸው። ልጆቻቸው ወደ ፈተና በሚሄዱበት ጊዜ ትብብር ማድረግ ፤ ፈተናውን ለመፈተን በሚሄዱበት ጊዜ የተከለከሉ ነገሮችን ይዘው እንዳይሄዱ ከቤት ነው ይሄ ነገር የሚጀምረው ምክንያቱም የ12 ዓመት ጥረት አፈር ነው የሚገባው አንድ የተከለከለ ነገር ይዘው ቢገቡ ፤ ስለዚህ እኛ እንደውም ፍተሻው ፖሊስ ጋር መጥቶ ከመድረሱ በፊት ቤት ወላጆች ናቸው አይተው መላክ ያለባቸው።

ወላጆች ለልጆቻቸው የሚሰጧቸው የሚያስፈልጋቸው ነገሮች ይኖራሉ ለምሳሌ ፦ እንደ ደረቅ ምግብ ድንገት ለሊት ሲያጠኑ ቢያስፈልጋቸው ቆሎም ይሁን ሌላ የሚሰጧቸው ነገር ካለ ፣ አንሶላ፣ ብርድልብስ እነዚህን እንደሚያዚዟቸው ሁሉ የዛን ያህል የተከለከሉ ነገሮችን እንዳይዙ መቆጣጠር አለባቸው፤ ይህንንም ያደርጋሉ ብለን እናምናለን።

ከዛ ውጭ በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ የሚጮኸውን አለመስማት ነው ፤ ምክንያቱም ዋነኛው ስራቸው በእንዲህ አይነት ነገር ማህበረሰብን ማሸበር እንደ ችሎታ እና እንደእውቀት የወሰዱ ጤነኛ ያልሆኑ ብዙ ሰዎች ያሉበት ዘመን ላይ ነው ያለነው።

ወላጆች የልጆቻችሁን ጉዳይ በሚመለከት በቀንጥታ ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር፤ የምንነግራችሁ ቁጥሮች አሉ፣ የምንልካቸው የአካባቢው ትምህርት ተወካዮች አሉ በዛ በኩል መገናኘት ያስፈልጋል።

አንድ ነገር ቢፈጠር #በእርግጠኝነት የምንነግራችሁ ፤ ከእኛ ውሸት አትጠብቁ የሆነውን ነገር ይሄ ነው የሆነው ብለን እንነግራችኃለን። ምንም የምንደብቅበት ምክንያት የለም።

ይሄ የፖለቲካ ስራ አይደለም ፤ ይሄ የትምህርት ስራ ነው።  የትምህርት ስራ ደግሞ ሁላችንንም የሚያገናኝ እና የሚያጣብቅ ስራ ነው።

ወላጅን ከአስተማሪዎች፣ አስተማሪዎችን ከአጠቃላይ የትምህርት ስርዓቱና ከትምህርት አስተዳዳሪዎች ጋር የሚያይዘው ውስጣችን ለልጆቻችን ጤንነት ፤ ለልጆቻችን የእውቀት ጥማት እና ህይወትን ለማሻሻል የሚያደርጉትን ጥረት ከማገዝ በላይ ምንም ሌላ ነገር የለም ከዚህ የሚገኝ የፖለቲካ ጥቅም ሆነ ትርፍ የለም።

ይሄን ማወቁ ምንም የፖለቲካ ልዩነቶች እንኳን ቢኖሩ ትምህርትን የዛ መጠቀሚያ አናድርገው ፣ ትምህርትን ከዛ ውስጥ እናውጣው ትምህርት ስለልጆቻችን ነው። "

ለበለጠ ትምህርታዊ መረጃ @educate_ethiopia ቤተሰብ ይሁኑ