የተቃጠለ ልብ
ክፍል
ደራሲ ዘሪሁን ገመቹ ዋቤ
:
:
...የዲላ ከተማ ነዋሪ የሆነችው የ45 አመቷ ወ/ሮ ምንትዋብ በህይወቷ አሥቸጋሪ ግዜ ላይ ትገኛለች።ሀዘን ውሥጧን ሠብሯታል።ስጋት ቅሥሟን ሠልቧታል።ሞራሏንም ንብረቷንም ፍቅሬ ብላ ላሥጠጋችው፤ ትዳሬ ብላ ለተቀበለችው ሰው ቀሥ በቀሥ አስረክባው ነበር። ያ ሰው ግን በዚህ ወቅት ሁሉን ነገር ይዞባት ተሰውሯል...ለንግድ ብሎ እንደወጣ የዉሀ ሽታ ሁኖ ከቀረ እነሆ ሁለት ወራት ደፍኗል...ሶስተኛው እየተጋመሰ ነው።መልዕክት የለ...ሥልክ የለ...ምንም ፍንጭ የሌለው ድፍንፍን ያለ ወጋገን አልባ ጨለማ ስጋት ዙሪያዋን ከቧታል።
ምንትዋብን እንዲህ ስጋት ላይ የጣላት የሶሶት አመት ባለቤትዋ ሁኖ አልጋዋን ሲጋራት የነበረው ወርቅ አለማው ነው።እርግጥ መጀመርያ ከቤት ሲወጣ እንደወትሮው ለተለመደ ሥራ ነበር..ያልተለመደው ሥልክ ደውሎ ያለማወቁ..ከዚያ በፊት ከሚያሳልፈው የሣምንትና የአስራ አምስት ቀን የግዜ ቆይታ ባልተጣጣመ መልኩ ከሁለት ወር በላይ መዘግየቱ ነው።ይዞ የሄደው ንብረት ወይም በእሡ እጅ ያለው ንብረት ቀላል የሚባል አይደለም።ከዛ ውሥጥ ደግሞ 80 ፐርሰንቱ የሷ የግል ንብረት ነው..እረ ምን የሷ ብቻ የአንድዬ ልጇም ንብረት ነው፤ከአባቱ በውርሥ የተላለፈለት..ከሟች ባሏ ጋር በአንድነት ያፈሩት የቤተሠቡ መተዳደርያ ጥሪት ነው..ወደድኩሽ ብሎ ለተጠጋት ባል ነኝ ብሎ እቤቷ ለአመታት ለኖረው ወርቅ አለማው አምናና አሳልፋ የሠጠችው።ወርቅ አለማው የምንትዋብ የበፊት ሟች ባል ተቀጣሪ ሰራተኛ ሁኖ ከአምሥት አመት በላይ የኖረ የ40 አመት ጎልማሳ ነው።ምንትዋብ ከእሡ ጋር የመቀራረብ እድሉ ያጋጠማት የልጇ አባት የሆኑት አዛውንት ባሏ ከሞቱ በሁዋላ በእሳቸው ይተዳደር የነበረውን ሆቴል እሷ መቆጣጠር ስትጀምር ነበር።ምክንያቱም ወርቅ አለማውም የሆቴሉ ስራ-አስኪያጅ ስለነበር በየቀኑ የመገናኘትና የመነጋገር እድል ነበራቸው።ሳያስቡት መቀራረብ ቀስ በቀስ
መሳሳብ ጀመሩ..
ነገር ፈታተን እና ከፋፍለን እንየው ከተባለ ግን ሳያስቡት የሚለው ቃል የሚሠራው ለምንትዋብ ብቻ ነው...ወርቅ አለማው እያንዳንዷን እርምጃውን በእቅድ ነበር ያከናወናት...ቀድሞውንም በፍቅር ስም እየማለ የሚከውነው ከፍቅር ውጭ የሆነ አላማ ነበረው።በፍቅር መሠላልነት በመንጠላጠል ወደ ሀብት ማማ ላይ ትክክለኛውንመንጠልጠል..አዎ ይሄን በልቡ ውስጥ በሚስጥር ቀብሮ ለማንም ትንፍሽ ሳይል በአላማ ሲንቀሳቀስ ነበር።...ያው ጥሩም ሆነ መጥፎ ነገር ሠው ብርቱና የአሸናፊ ሀይል በውስጡ ይዞ የሚዞር የእግዛብሔርን እስትንፋስ የተጋራ ልዩ ፍጡር ነውና ከልቡ ካቀደ..ያቀደውንም እንዲሳካለት ሳይሰለች ከጣረና ከለፋ ይሳካለታልና ይሄው ለሶስት አመት በማድባት ከሠራ በኋዋላ ዛሬ ያሳካው ይመስላል...ክፋቱ ይሄንን እግዛብሔር ከእስትንፋሱ ጋር ደባልቆ የሠጠውን የአሸናፊነት ሀይል በጎ ላልሆነ ነገር ስለተጠቀመበት(ተጠቅሞበት ከሆነ ማለቴ ነው)እንዴት ነው የሚቀጣው......? አዎ ምንትዋብ ዛሬ ነገሮች ከእጇ ሾልከው ያመለጡ ከመሠሉ በሁዋላ ነው አይኖቿ በድርበቡም ቢሆን የተከፈቱላት እና ልቦናዋም በጥርጣሬ ይታመሥ የጀመረው... ...እርግጥ አሁን ሥጋት ነው እንጂ ምንም የሚታወቅና የተረጋገጠ ነገር የለም።እውነት በውስጧ እንደጠረጠረሽው ከድቷት ይሆን ወይስ በሄደበት ሀገር አደጋ አጋጥሞት.. ...?ሌባ ዘርፎት ወይስ ሽፍታ ገድሎ አንድ ስርቻ ጥሎት? እግዜር ነው የሚያውቀው።ምንትዋብ ማለቂያ የሌላቸው ግትልትል ሀሳቦቿን በአእምሮዋ ስታመላልስ ቆይታ ድንገት እንደመባነን ብላ ወደ ቀልቧ ስትመለስ የ29 አመቱ ወጣት የፖሊስ መኮንን ልጇ ስሯ ተንበርክኮ አይን አይኗን በሀዘኔታ እያያት ትካዜዋን ሲጋራት ተመለከተች......
<<የኔ ውሻ>>አለችው እጇን ግንባሩ ላይ ጭና
<<አቤት እማ>>
<<የምሳ ሰአት ደርሶ ነው የመጣኸው? ምን አንበረከከህ ደግሞ..? ለምን አትነሳም?>>
<<አዎ 7 ሰአት ሊሆንኮ ነው...ጠዋት ትቼሽ የሄድኩበት ቦታ ሳገኝሽኮ ደነገጥኩ>> በማለት ከተንበረከከበት በመነሳት ከጎኗ ሶፋው ላይ ተቀመጠና መናገር ጀመረ
<<እማ ያንቺ ስጋት ሙሉ በሙሉ ግልፅ አልሆነልኝም..ለስራ ነው የወጣው አይደል...? ለዚያውም ጅቡቲ ድረስ...እርቀቱን አስቢው የቆየበትን ግዞኮ ያን ይህል ተስፋ የሚቆረጥበት አይደለም...ሶስት አራት ወር የሚቆይበት ጉዳይ ሊያጋጥመው ይችላል>>እናቱን ለማፅናናት ብሎ እንጂ ሰውዬው ያለምንም ነገር ድምጹን አጥፍቶ ይሄን ያህል ግዜ እንዳልቆየ የሱም ልብ ጠርጥሯል።
<<መቆየቱ አይደለም ያስጨነቀኝ።ባልተለመደ መልኩ ለአንድ ቀንም ቢሆን ያለመደወሉ...ስልኩም ጥሪ ያለመቀበሉ ነው ያሳሰበ ኝ....በቃ ውስጤ ፈርቷል ።>>አለችው ከአይኖቿ ያለፍላጎቷ የሚረግፈውን እንባ በእጆቿ እየጠራረገች
<<እርግጥ መደወል ነበረበት...ሳይመቸው ቀርቶ ይሆናል።ወይንም የሡ አለመደወል እኛን ይሄን ያህል ያስጨንቃቸዋል ብሎ ስላላሠበም ሊሆን ይችላል።>ን
ምንትዋብ ከተቀመጠችበት ተነሳች...በአንድ እጇ ወገቧን ይዛ በሌላ እጆ የተንጨፈረረ ፀጉሯን ይበልጥ እንዲንጨፋረር እያፍተለተለች ንግግሯን ቀጠለች<<አዎ..እሡን እንኳን እውነትህን ነው..አጅሬ ምን ጎደለበት? እስቲ ተወኝ..ጉድ ሳያደርገኝ አልቀረም...በውስጤ እሳት እየተንቀለቀለ ነው።አሁን ትንሽ እረፍት ልውሰድ....>>ብላ እግሮቿን እየጎተተች ሳሎኑን ለቀቀችና ወደ መኝታ ቤቷ ሄደች።
ኮማንደር መሀሪ የእናቱን ወደ መኝታ ቤቷ ገብታ በራፉን ከውስጥ መቀርቀሯን ከተመለከተ በሁዋላ ከኪሱ ሞባይሉን አወጣና ደወለ...ፍቅረኛው ጋር።
የእናቱ ጭንቀት የሱም ጭንቀት ሆኗል...ከዚህ ጭንቀቱ ረገብ እንዲል ደግሞ ወደ ሥራ ከመግባት ይልቅ ፍቅረኛውን ማግኘት ይሻለዋል። ከአምስት ጥሪ በሁዋላ ስልኩ ተነሳ።ግን እሷ አልነበረችም ያነሳችው ታናሽ እህቷ ነበረች።
ሞባይሏን እቤት ጥላ እንደወጣችና እቤት እንደሌለች ነገረችው...ምንም አላላትም ስትመጣ እንድትደውልለት መልእክት አስቀምጦላት ስልኩን ዘጋው።
ይ ቀ ጥ ላ ል