Get Mystery Box with random crypto!

ደብረ ማርቆስ ዩንቨርሲቲ በሸበል በረንታ ወረዳ ስለሚሰሩ የማህበረሰብ አገልግሎት ፕሮጀክቶች ከአጋር | Debre Markos University /ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ

ደብረ ማርቆስ ዩንቨርሲቲ በሸበል በረንታ ወረዳ ስለሚሰሩ የማህበረሰብ አገልግሎት ፕሮጀክቶች ከአጋር ድርጅቶች ጋር ውይይት አካሄደ
===============
ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ፣ ጥቅምት 24/ 2015 ዓ.ም (ህዝብ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ዳይሬክቶሬት) ዩንቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ባሻገር የምርምርና የማህበረሰብ አገልግሎት ስራዎችን በስፋት ይሰራል፡፡ በዚህ ዓመትም አግሪ ሰርቪስ ኢትዮጵያ ከተባለ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት እና “Bread for the world” ከተሰኘ አለም አቀፍ የጀርመን ድርጅት ጋር በሸበል በረንታ ወረዳ “Shebel Berenta Integrated Capacity and development”(ICDP) የተባለ ማህበረሰቡን ዘርፈ ብዙ በሆኑ ጉዳዮች ተጠቃሚ የሚያደርግ የተቀናጀ የልማት ፕሮጀክት ለመጀመር የዩኒቨርሲቲውን ፕሬዝዳንት ጨምሮ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች ከድርጅቱ የስራ አመራሮች ጋር ስለ ፕሮጀክቱ አተገባበርና ስኬት ውይይት አካሂደዋል፡፡

በዩኒቨርሲቲያችን የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት አስካለማርያም አዳሙ (ዶ/ር) ዩኒቨርሲቲው እስካሁን በተለያዩ አካባቢዎች የሰራቸውን ማህበረሰብ አቀፍ አገልግሎቶችን የገለጹ ሲሆን በስናን ፣ በማቻከል፣ በጎዛምን ፣ ደጀን ፣ እነብሴ ሳር ምድር ፣ቁይ እና ሌሎችም አካባቢዎች የተፈጥሮ ሀብት ልማት፣ በሰብል ልማት፣ የእንስሳት እርባታ እና የንፁህ መጠጥ ውሃን ተደራሽ ለማድረግ ሲሰራ እንደቆየ አብራርተዋል፡፡ በቀጣይም በሸበል በረንታ ለሚካሄደው ፕሮጀክት በትጋት እንደሚሰሩ ገልፀዋል፡፡

በዩኒቨርሲቲያችን የማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ስር የማህበረሰብ ልማት ኦፊሰር እና የፕሮጀክቱ አስተባባሪ መብራቱ በላቸው (ዶ/ር) ፕሮጀክቱ በንፁህ መጠጥ ውሃ፣ በምግብ ዋስትና፣ በተፈጥሮ ሀብት ልማት፣ በእንስሳት ጤና፣ በእንስሳት እርባታ እና ጎጅ ልማዳዊ ድርጊቶችን ከማስቀረት አኳያ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ እስካሁንም ለአንድ ዓመት ፕሮጀክቱን በማደራጀት እና ገንዘብ በማፈላለግ ሳይጀመር የቆየ ሲሆን አሁን ላይ “Bread for the World” የተሰኘው አለም አቀፍ የጀርመን ድርጅት 75 በመቶ እና ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ 25 በመቶ በመሸፈን ወደ ተግባር ለመግባት ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውንም አክለው ገልፀዋል፡፡ አያይዘውም የሸበል በረንታ ወረዳ ማህበረሰብ የፕሮጀክቱን ኣላማ በመገንዘብ ከጎናቸው እንዲቆም እና የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብም በየሙያ ዘርፉ ተሳታፊ እንዲሆን አሳስበዋል፡፡

በሌላ በኩል ከአግሪ ሰርቪስ ኢትዮጵያ ጋር ከሚሰራው “Bread for the world” ድርጅት የመጡት ወ/ሪት ፅዮን ታደሰ ዩኒቨርሲቲው ለማህበረሰቡ የሚሰጠው አገልግሎትና ተነሳሽነት በጣም እንዳስደሰታቸው ገልፀው ይህን የተቀናጀ የገጠር ልማት ስራ ስኬታማ ለማድረግ ድርጅቱ 75 በመቶ የሆነውን በጀት ሲሸፍን በደስታ ነው ብለዋል፡፡ ወደፊትም በተለይ ዩኒቨርሰቲው ሁሌም ያለ ተቋም በመሆኑ ከማህበረሰቡ ጎን በመቆም የማህበረሰቡን የልማት ስራዎች የማገዙን ተግባር አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ኣሳስበዋል፡፡

በአግሪ ሰርቪስ ኢትዮጵያ ጎጃም አካባቢ የሚሰሩ ፕሮጀክቶች አስተባባሪ አቶ ተመስገን ወንድይፍራው በበኩላቸው አግሪ ሰርቪስ ኢትዮጵያ እስካሁን ማህበረሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ ስራዎችን ሲሰራ መቆየቱንና ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲም በርካታ ምሁራን የሚገኙበትና ስኬታማ የሆኑ የማህበረሰብ አገልግሎቶችን ሲሰራ የቆየ በመሆኑ በጋራ ለማህበረሰቡ ዕድገት ለመስራት መስማማታቸውን ገልፀው ወደፊትም በሌሎች ወረዳዎች ተደራሽ ለማድረግ እንደሚሰሩ ተናግረዋል፡፡ ዩንቨርሲቲው ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ በሚሰራው ስራም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

በመጨረሻም የመጡት እንግዶች በሀዲስ አለማየሁ የባህል ጥናት ተቋም የምርምር ማዕከል የተላመዱ መድሀኒታማ ዕፅዋትን፣ በግብርና ኮሌጅ የለማውን ሰርቶ ማሳያ አትክልት እና የወቢ እነችፎ የሚገኘውን የዩኒቨርሲቲውን የመስኖ ልማት በመጎብኘት አድናቆታቸውን ገልፀዋል፡፡