"ይህችን ዓመት ተወኝ!" ከዓመት እስከ ዓመት - ፍሬን ሳላፈራ - ደረቅ እንደሆንኩኝ በራድ ወይም ትኩስ - ሁለቱንም ሳልሆን - እንዲያው ለብ እንዳልኩኝ አለሁኝ በቤትህ - ለሙን መሬትህን - እያጎሳቆልኩኝ አውቃለሁ አምላኬ - ፍሬዬን ለመልቀም - እንዳመላለስኩህ ዛሬም ሳላፈራ - እሾህን አብቅዬ - ደርቄ ጠበቅሁህ ያልተደረገልኝ - ያላፈሰሰክብኝ - ያልሰጠኸኝ የለም ነገር ግን ይህ ሁሉ - አላርምህ አለኝ - አልለየኝም ከዓለም የማትሰለቸኝ ሆይ - ተነሥቼ እስክቆም - እባክህ ታገሠኝ የእኔን ክፋት ተወው - መልአክህን ሰምተህ - ይህችን ዓመት ተወኝ! አውቃለሁ ታውቃለህ - ቀጠሮን ሰጥቼ - እንደማላከብር ብዙ ጊዜ አቅጄ - ብዙ ጊዜ ዝቼ - በወሬ እንደምቀር ‹ዘንድሮስ…!› እንዳልኩኝ - አምና ይሄን ጊዜ - ሰምተኸኝ ነበረ ምንም ሳልለወጥ - ‹ዘንድሮዬ› አልፎ - በአዲስ ተቀየረ ፍሬ የማይወጣኝ - እኔን በመኮትኮት - እጆችህ ደከሙ እኔ ግን አለሁኝ - ዛሬም አልበቃኝም - በኃጢአት መታመሙ የቃልህን ውኃ - በድንጋይ ልጅህ ላይ - ሳትታክት ስታፈስስ - ዘመን ተቆጠረ ወደ ልቤ ሳይሰርግ - ሕይወቴን ሳይለውጥ - እንዲያው ፈስሶ ቀረ ቃልህን ጠግቤ - እያገሳሁት ነው - ሌሎች እስኪሰሙ በቃልህ መኖር ግን - አልያዝህ አለኝ - ከበደኝ ቀለሙ ብዙ ጥቅስ አገኘሁ - ከቅዱስ መጽሐፍህ - ገልጬ አይቼ ከራሴ ላይ ብቻ - አንድ ጥቅስ አጣሁኝ - በበደል ተኝቼ ውጤቴ ደካማ - ትምህርት የማይሠርጸኝ - ተማሪ ብሆንም ይህችን ዓመት ተወኝ - ደግሞ ትንሽ ልማር - ታገሠኝ አሁንም! እባክህ አልቆረጥ - በቅዱስ መሬትህ - ልቆይ ፍቀድልኝ ያፈሩት ቅዱሳን - የፍሬያቸው ሽታ - መዓዛ እንዲደርሰኝ የተሸከምከኝ ሆይ - ዛሬም ተሸከመኝ - አትሰልቸኝ አደራ ማን ይታገሠኛል - ጠላት እየሆንኩት - አይሠሩ ስሠራ! አታውጣኝ ከቤትህ - ብዙ ቦታ አልይዝም - ፍሬ ስለሌለኝ ስፍራ የማያሻኝ - ቤት የማላጣብብ - ፍሬ አልባ በለስ ነኝ! ቦታስ የሚይዙት - ባለ ምግባሮቹ - ቅዱሳንህ ናቸው ልክ እንደ ዘንባባ - የተንዠረገገ - ተጋድሎ ጽድቃቸው! ከሊባኖስ ዝግባ - እጅጉን የበዛ - ገድል ትሩፋታቸው! እኔ አይደለሁም - ቦታስ የምትይዘው - የአንተው እናት ናት ሥሮቿ በምድር - ጫፎቿ በሰማይ - ሲደርሱ ያየናት ይሀችን ዓመት ተወኝ - ከሥርዋ እሆናለሁ - ባፈራ ምናልባት!.. ይህችን ዓመት ተወኝ - እባክህ አምላኬ - አንድ ዓመት ምንህ ናት ሺህ ዓመት አንድ ቀን - አይደለም ወይ ለአንተ - ዓመት ኢምንት ናት! ይሄ ዓመት አልፎ - ዳግም ‹ዓመት ሥጠኝ› - እስከምልህ ድረስ እባክህን ጌታ - ይህችን ዓመት ተወኝ - የወጉን እንዳደርስ! ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ --- 18.1K views: ፦, 06:48