Get Mystery Box with random crypto!

+ ትሞታለህና ቤትህን አስተካክል + ንጉሥ ሕዝቅያስ በጠና ታምሞ ተኝቶአል:: ነቢዩ ኢሳይያስ | የዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ ትምህርቶች

+ ትሞታለህና ቤትህን አስተካክል +

ንጉሥ ሕዝቅያስ በጠና ታምሞ ተኝቶአል:: ነቢዩ ኢሳይያስ ሊጠይቀው መጣ:: ሆኖም እንደ ልማዱ እግዚአብሔር ይማርህ አላለውም:: ለጆሮ የሚከብድ ቃል ጥሎበት ወጣ:: "ትሞታለህና ቤትህን አስተካክል!"

ነቢዩ ይህንን ብሎት ከወጣ በኁላ ሕዝቅያስ ወደ ግድግዳው ዞሮ ስቅስቅ ብሎ አለቀሰ:: አምላኩ በንግግር ብዛት የሚሰማ አምላክ አይደለምና ፊቱን ወደ መቅደሱ አቅጣጫ አዙሮ አለቀሰ::

ከጥቂት ደቂቃ በኁዋላ ነቢዩ ኢሳይያስ ሌላ መልእክት ይዞ ተመለሰ:: እግዚአብሔር እንዲህ ይላል :- ጸሎትህን ሰምቻለሁ ዕንባህን አይቻለሁ በዕድሜህ ላይ ዐሥራ አምስት ዓመት እጨምራለሁ" (ኢሳ 38:5)

ሕዝቅያስ ቤትህን አስተካክል ከተባለ በኁዋላ ፊቱን አዙሮ ከማልቀስ በቀር ምንም አላደረገም:: ሕዝቅያስ ሆይ ከአልጋህ ሳትወርድ ያስተካከልከው ቤት ምን ዓይነት ቤት ነው? ለባሪያዎችህ መመሪያ ሳትሠጥ የምታስተካክለው ቤትስ እንዴት ያለ ነው? በደቂቃዎች ውስጥ ትሞታለህ ከተባልክ በኁዋላ ዐሥራ አምስት ዓመት ያስጨመረልህ ምን ዓይነት ማስተካከያ አድርገህ ነው? ለእኛም ንገረንና ዕድሜ እናስጨምር::

ሕዝቅያስ ከአልጋው ሳይነሣ ያስተካከለው ቤቱ ልቡ ነበር::
ልብህን ካስተካከልህ ቤትህ ይስተካከላል:: እግዚአብሔር እንደሆን ትሞታለህ ቢልህም መሞትህን አይፈልግም:: እርሱ ካንተ ጋር ጸብ የለውም::

"በውኑ ኃጢአተኛ ይሞት ዘንድ እፈቅዳለሁን? ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ከመንገዱስ ይመለስና በሕይወት ይኖር ዘንድ አይደለምን?" ይላል መሐሪው (ሕዝ 18:23)

እርሱ ትሞታለህ የሚልህ መኖርህን ፈልጎ ነው:: አንዴ ብያለሁ ብሎ አይጨክንብህም:: በንስሓ ተመለስ እንጂ ምሬሃለሁ ለማለት ይቸኩላል:: አሁን ትሞታለህ ብዬው አሁን ትድናለህ ብለው ይንቀኛል ሳይል ተመልሶ ይምርሃል:: ኃጢአትህንም ወደ ጥልቁ ይጥለዋል:: በጎ እንድትሠራም ዕድሜ ይጨምርልሃል:: አንተ ብቻ ተመለስና አሁኑኑ ንስሓ ግባ::
ከበደል አልጋ ጋር ያጣበቀህን ፈተናም ድል መንሻው ጊዜ አሁን ነው:: ሕዝቅያስ በደቂቃ ዕንባ ምሕረት አግኝቶ ዕድሜ ካስጨመረ በዐቢይ ጾም ሙሉ የሚያለቅስ ምን ያህል ዕድሜ ያገኝ ይሆን?
ወዳጄ አንተም ተነሣና በዚህ ወር ቤትህን አስተካክል::
እንደ ሕዝቅያስ ፈጣሪህ ይጠብቅሃል:: የተቀየምከውን ይቅር በል የበደልከውን ካስ የሚበቀልህን የማይተኛ ጠላትህን ዲያቢሎስ ተበቀለው::

የዐቢይ ጾም የወንጌል ምንባብ ስለ ዲያቢሎስ ፈተና ሦስቱ ወንጌላት የተናገሩትን ስናስተውል ሦስት ዓይነት ጥቅሶች እናገኛለን::

አርባ ቀን ከዲያብሎስ ተፈተነ። (ሉቃ 4:2)

በምድረ በዳም ከሰይጣን እየተፈተነ አርባ ቀን ሰነበተ (ማር 1:13)
የሚሉት ቃላት ጌታችን ዐርባውንም ቀን መፈተኑን ያሳያሉ::

አርባ ቀንና አርባ ሌሊትም ከጦመ በኋላ ተራበ። ፈታኝም ቀርቦ እንዲህ አለው (ማቴ 4:2)

የሚለው ደግሞ ከጾሙ በኁዋላ የቀረቡለትን ሦስት ፈተናዎች የሚያሳይ ነው::
ሦስተኛው ጥቅስ ደግሞ ከተፈተነ በኁዋላ ያለው ሲሆን

ዲያቢሎስም ፈተናውን ሁሉ ከጨረሰ በኋላ እስከ ጊዜው ከእርሱ ተለየ። (ሉቃ 4:13) ይላል:: ዲያቢሎስ ፈተናውን ቢጨርስም የሚተወው ለጊዜው እንጂ መፈተኑን አያቆምም:: የዲያቢሎስ ፈተና ስልቱ ይቀያየራል እንጂ ይቀጥላል::

ዐቢይ ጾም ዲያቢሎስ ድል የተደረገበት የጦር ዐውድማ ነው:: በዚህ ወራት ድል ያላደረግነውን ፈተና በሌላ ጊዜ አናደርገውም:: ሰነፍ ገበሬ በሰኔ ይሞታል እንደሚባለው በዐቢይ ጾም የተኛ ክርስቲያን መቼም አይነቃም:: ከነስሙ ሁዳዴ (ሰፊ እርሻዬ) የምንለው ይህ ጾም ለነፍሳችን ብዙ ዘር የምንዘራበት አጋንንት መድረሻ የሚያጡበት ጾም ነው:: በዐቢይ ጾም ያልተገራ አንደበት መቼም አይገራም:: በዐቢይ ጾም ያልተፈወሰ ቂም መቼም አይፈወስም::

ጌታችን በወንጌል አንዴ ወደ እሳት አንዴ ወደ ውኃ የሚጥል ጋኔን ያለበትን ልጅ ሲፈውስ "ይህ ዓይነቱ ጋኔን ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም" ብሎ ነበር:: ሀገራችንን አንዴ ወደ እሳት አንዴ ወደ ውኃ የሚጥላት የጥላቻ ጋኔንም ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም::

ወዳጄ ከቁስልህ የምትፈወስበት ወር እንደደረሰ ዕወቅ:: አንተስ ብትሆን ልትላቀቀው እየፈለግህ ያቃተህ ክፉ ልማድ የለብህም:: እንደ ቅዱስ ጳውሎስ "የምፈልገውን መልካም ነገር አላደርግም የማልፈልገውን ክፉ ነገር ግን አደርጋለሁ:: ምንኛ ጎስቋላ ለዚህ ለሞት ከተሠጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?" ብለህ ምርር እንድትል ያደረገህ ኃጢአት የለም? እንግዲያውስ እወቀው:: ይህ ዓይነቱ ወገን ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም:: ይህ ጾም ቁስል የሚሽርበት ጾም ነው:: ይህ ጾም ሸክም ማራገፊያ ጾም ነው:: እንደ ሕዝቅያስ በዚህ ወር ቤትህን በንስሓ አስተካክል::

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
የካቲት 15 2012 ዓ ም
ዝዋይ ኢትዮጵያ