2022-08-28 07:00:26
+++ ማርታም ታገለግል ነበር+++
ማርያምና ማርታ እኅትማማቾች ናቸው፡፡ ‹ኢየሱስም ማርታንና እኅትዋን ፣ አልዓዛርንም ይወድ ነበር› (ዮሐ. 11፡5) ስለዚህም በቢታንያ በሚገኘው ቤታቸው እንግዳ ሆኖ ተገኘ፡፡ እጅግ ለሚወዱት ጌታ ፍቅራቸውን ለመግለጽ እኅትማማቾቹ ይሻላል ብለው ያሰቡትን ሁለት የተለያየ ዓይነት አቀባበል አድርገውለት ነበር፡፡ ማርታ ለምትወደው እንግዳዋ ምግብ ለማቅረብ ብዙ ተጨንቃ በጓዳ ሥራ ላይ ተወጠረች፡፡ ‹ለታላቁ ጌታ ምን ላቅርብለት ይሆን?› ብላ ተጠበበች፡፡
መቼም የምናከብረው ሰው እንግዳ ሆኖ ሲመጣ ሙያውም ሊጠፋብን ይችላል፡፡
ማርታም የገጠማት ይኼው ነው ፣ ምኑን ከምኑ አድርጋ እንደምታቀርብ ግራ ገባት ፤ ጌታችን እንዳለው ‹በብዙ ነገር ተጨነቀች ታወከች›፡፡
እኅትዋ ማርያም ግን ሃሳቧን ጥላ ቃሉን ልትሰማ ከጌታ እግር ሥር ቁጭ አለች፡፡
ማርያምን በማርታ ዓይን ሆነን ስናያት እንግዳ ሲመጣ ሥራ ላለመሥራት ከእንግዳ ጋር ከሚቀመጡ ሥራ ጠል እኅቶች አንድዋን ትመስለናለች፡፡
እኅትዋ ከጭስ ጋር ስትታገል ፣ ምን ልሥራ ብላ ስትርበተበት እስዋ በቤትዋ እንደ እንግዳ መቀመጥዋን ስናይ ‹ምን ዓይነቷ ግፍ የማትፈራ ናት› ብለን መታዘባችን አይቀርም፡፡
ማርታ ግን ታዝባ ዝም አላለችም፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ፥ እኔ እንድሠራ እኅቴ ብቻዬን ስትተወኝ አይገድህምን? እንኪያስ እንድታግዘኝ ንገራት አለችው። ጌታችንም ኢየሱስም መልሶ፦ ማርታ፥ ማርታ፥ በብዙ ነገር ትጨነቂአለሽ ትታወኪማለሽ፥ የሚያስፈልገው ግን ጥቂት ወይም አንድ ነገር ነው፤ ማርያምም መልካም ዕድልን መርጣለች ከእርስዋም አይወሰድባትም አላት።››
ሉቃ. 10፡38-42 በእኛ ግምገማ ማርታ የበለጠ ለጌታ ፍቅር ያላት ቢመስለንም ጌታችን ግን የማርታን በፍቅር ለሥራ መድከም ሳይነቅፍባት የማርያም ምርጫ ግን ‹የማይቀማ በጎ ዕድል› መሆኑን ተናገረ፡፡ እንዴት ሊሆን ይችላል?
በእኅትማማቾቹ ቤት የተገኘው ሌላ እንግዳ ቢሆን ኖሮ ማርያም ያደረገችው የሚያስወቅስ ይሆን ነበር፡፡ በእነርሱ ቤት የተገኘው ግን የሰማይና የምድር ፈጣሪ ነው፡፡
እርሱ ደግሞ የሚቀበሉት እንጂ የሚሠጡት እንግዳ አይደለም፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ እንዳለው ‹‹ማርታ ጌታ ራሱ የፈጠረውን ምግብ በገበታ ልታቀርብለት›› ተጨነቀች፡፡(Martha gave him to eat: viands which He had created she placed before Him)
@deaqonhanok
የዋኋ ማርታ ያላወቀችው ነገር እርሱ ደስ ብሎት የሚበላው ምግብ እርስዋ የምትሠራው ዓይነት ምግብ እንዳልሆነ ነው፡፡
እንደ ሐዋርያቱ ቀርባ ብትጠይቀው ኖሮ ፡- ‹‹አንቺ የማታውቂው የምበላው መብል ለእኔ አለኝ›› ይላት ነበር፡፡
(ዮሐ. 4፡32) ምን ትጠጣለህ? ብትለው ለሙሴ እንደነገረው ‹ኃጢአተኛ ሲጸጸት ዕንባውን እጠጣለሁ› (ኃጥእ አመ ይኔስሕ ዕንባሁ እሰቲ) ብሎ ይመልስላት ነበር፡፡
አልጠየቀችውም እንጂ መራራ ሐሞት እስኪጠጣ ድረስ በሰው ልጅ ፍቅር ስለተጠማው ጕሮሮው ይነግራት ነበር፡፡
(‹ሰላም ለጕርዔከ በጽምአ ፍቅረ ሰብእ ሐማሚ፡፡ እስከ ስቴ ሐሞት ጥዕመ ወዘወይነ ትፍስሕት ከራሚ› እንዲል) የእርሱ ምግብና መጠጥ የሰው ልጅ ልቡን ሠጥቶ ወደ እርሱ መመለሱ ነው፡፡
ማርያም ግን የማይቀሟትን በጎ ዕድል መረጠች፡፡ ከራሱ ከጌታችን እግር ሥር ቁጭ ብሎ ከመማር በላይ ምን ዕድል አለ? ፈጣሪ ሲናገር መስማትስ እንዴት መታደል ነው? እርሱ የሚናገረው ቃል እኮ መለኮታዊ ቃል ነው! ከጌታ የሚወጣው ቃል የሚሠራና ሕያው የሆነው የራሱ የእግዚአብሔር ቃል ስለሆነ
‹ነፍስንና መንፈስንም ጅማትንና ቅልጥምንም እስኪለይ ድረስ ይወጋል፥ የልብንም ስሜትና አሳብ ይመረምራል› (ዕብ. 4፡12) እርሱ የሚናገረው ቃል ሙቱን አፈፍ አድርጎ ያስነሣል ፣ ለምጻሙን ያነጻል፡፡
አስረው እንዲያመጡት ከአይሁድ የተላኩት የሮም ወታደሮች እንኳን ከትምህርቱ ጣዕም የተነሣ ተደንቀው ‹‹እንደዚህ ሰው ማንም እንዲሁ ከቶ አልተናገረም›› ብለው ባዶ እጃቸውን ተመልሰዋል፡፡
(ዮሐ.7፡46) የኤማሁስ መንገደኞችም ‹በመንገድ ሲናገረን ልባችን ይቃጠል አልነበረምን?› ብለዋል፡፡(ሉቃ. 24፡32) ይህ የጌታችን ድንቅ ትምህርት ማርታ ማድቤት ሆና አመለጣት፡፡
‹ብዙ ነቢያት ሊሰሙት ወድደው ያልሰሙትን› ቃል የመስማት ዕድል ቤቷ ድረስ መጥቶላት እርስዋ ግን ሥራ ላይ ነበረች፡፡ እንደ ሙሴ ወደ ተራራ ሳትወጣ ፣ በደመና ሳትከበብ ቤቷ ድረስ እግዚአብሔር መጥቶ ሊያናግራት ሲል እስዋ ግን ምግብ እየሠራለች ነው፡፡
‹ማርታ ግን አገልግሎት ስለበዛባት ባከነች› ይላል፡፡ ይህ ቃል በእግዚአብሔር ቤት ለምናገለግል ፣ የማርታ ችግር ላለብን ሰዎች ምንኛ ከባድ ቃል ነው? ለመቅደሱ ቀርበን ከፈጣሪ ለራቅን ፣ ጠዋት ማታ በሥራ ፣ በዕቅድ ፣ በስብሰባ ተወጥረን እንደ ማርታ ብዙ ድስት ለጣድን ለእኛ ምንኛ ከባድ ቃል ይሆን? አቡነ ሺኖዳ ‹‹እስከ ዛሬ የእግዚአብሔርን ቤት አገለገልሁ ፤ የቤቱን ጌታ የማገለግለው መቼ ይሆን?›› ብለው ነበር፡፡
ቤቱን እያገለገልን የቤቱን ጌታ ማገልገል ያቃተን ፣ በአገልግሎት ተወጥረን ከጸሎት ፣ ከንስሓ ፣ ከሥጋ ወደሙና ቃሉን ለራስ ብሎ ከመስማት ለተለየን ሰዎች እጅግ ከባድ ቃል ነው፡፡
እያገለገሉ ከፈጣሪ መራቅ እጅግ ከባድ ነው፡፡ እንደ ማርታ ፈጣሪ ባለበት ቤት እየኖሩ ከፈጣሪ መለየትም እጅግ የከፋ ነው፡፡
ማርያም የምትማርበትን ክፍል አጽድተን ፣ በኋላም ገበታውን አቅራቢ ሆነን የምንወደውን ፈጣሪ ሳንሰማው መቅረት እንዴት ያሳዝናል? ለሰብአ ሰገል ወደ ቤተልሔም ሔደው እንዲሰግዱ የጠቆሟቸው አይሁድ ነበሩ ፤ እነርሱ ግን ሔደው አልሰገዱለትም፡፡ ቅዱስ አምብሮስ እንዳለው ኖኅ መርከብ ሲሠራ የረዱት የቀን ሠራተኞች ነበሩ ፤ እነርሱ ግን ከጥፋት ውኃ አልዳኑም፡፡ ለፍቶ ደክሞ አገልግሎ ፣ ሌላውን አስተምሮ ፣ ቤተ እግዚአብሔርን ሠርቶ መኮነን እንዴት ያሳዝናል? እንደ መርፌ የሌላውን ቀዳዳ እየሠፋን የራሳችንን መስፋት ያቃተን ፣ እንደ መቋሚያ ለሌላው ድጋፍ እየሆንን ራሳችንን ማቆም ያቃተን ‹አገልግሎት ስለበዛብን የባከንን› ብዙዎች ነን፡፡
ማርታ ከቃሉ በመራቋ ምክንያት አገልግሎትዋን እንኳን በጸጥታ ማገልገል አልቻለችም፡፡ ብቻዋን መሥራትዋም አስቆጫት፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ፥ እኔ እንድሠራ እኅቴ ብቻዬን ስትተወኝ አይገድህምን? እንኪያስ እንድታግዘኝ ንገራት አለችው።›› ይህ ንግግርዋ ብዙ ጉድለት እንዳለባት ያሳያል፡፡ እኅትዋ እስከሆነች ድረስ ቀስ ብላ ጠርታ ‹ምን ማድረግሽ ነው? ነይና አግዢኝ እንጂ› ልትላት ትችል ነበር፡፡ አልዓዛር በሞተ ጊዜ በለቅሶ ቤት ‹ማርያምን በስውር ጠርታ፦ መምህሩ መጥቶአል ይጠራሽማል› ብላ እንደተናገረችው አሁንም በስውር ጠርታ ልትወቅሳት ትችል ነበር፡፡
(ዮሐ. 11፡28) እርስዋ ግን በቀጥታ ለእኅትዋ ከመናገር ይልቅ እኅትዋን በጌታ ፊት አሳጣቻት ፣ ከእኅትዋ ይልቅ እርስዋ ለጌታ የበለጠ ፍቅር ያላት እንደሆነች የሚያሳይ ንግግር ተናረች፡፡ ሰው ቃለ እግዚአብሔር ሲጎድለው ጠበኛ ይሆናል፡፡ እርሱ እየሠራ የሌሎች አለመሥራት ያበሳጨዋል ፣ በቀጥታ ሔዶ ለሰው ችግሩን ከመናገር ይልቅ በተዘዋዋሪ መናገር ይቀልለዋል፡፡ የዋኋ ማርታ ለአገልግሎት ስትባክን የገጠማት ፈተናም ይኼው ነው፡፡
55 views , 04:00