2022-08-18 07:38:01
✥✥✥ታቦር ወአርሞንዔም በስመ ዚኣከ ይትፌስሑ✥✥✥
(መዝ.88÷12)
በዚህ ርዕስ ሥር
1. በዓሉ የሚከበርበትን ምክንያት/
ከሐዋርያት ሦስቱ ሓዋርያት ብቻ መመረጣቸው ፤ ከነቢያት ሙሴና ኤልያስ መገለጣቸው ስለምን ነው?
2. ደብረታቦር የተመረጠበት ምክንያትና ምሳሌነቱ
3. የበዓሉ መጠሪያ ስሞች (ደብረ ታቦር / ቡሄ/ ቡሔ መባሉ ስለምንድ ነው?)
4. ችቦ የመብራቱ ፣ ሙልሙል ዳቦ የመጋገሩና የጅራፍ ማጮኽ ምክንያት እንመለከታለን፡፡
1. ይህ በዓል ከዘጠኙ ዐበይት በዓላት አንዱ ሲሆን የሚከበረው ጌታችን የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅነቱን ያስመሰከረበት፣ ጌትነቱን እና ክብሩን የገለጠበት በመሆኑ ነው፡፡ (ማቴ.17÷1 ማር.9÷2 ሉቃ.9÷28 2ጴጥ.1÷16-18)፡፡
ጌታችን ሐዋርያትን ‹‹ ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ብለው ይሉታል? ›› ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ቅድስናህን ዓይተው ሙሴ ነህ ይሉሃል፤ የኃይል ሥራህን ድንግልናውንም ዓይተው ኤልያስ ነህ የሚሉህ አሉ ……… ብለውት ነበረና እግዚኣ ሙሴ ወኤልያስ (የነቢያት ጌታ) መሆንኑን ለመግለጥ፤ አንድም ጌታችንም መልሶ ‹‹ እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ? ›› አላቸው ቅዱስ ጴጥሮስም እስከ ክርቶስ ተብሎ የተነገረልህ ‹‹ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ ›› አለው (ማቴ.16÷13-20/ ትን.ዳን.9÷25) ይህን በፍጡር አንደበት የተመሰከረውን ጌትነቱን በአብ ምስክርነት ለማጽናት እና በተግባር ለመግለጥ የሐዋርያትንም እምነታቸውን ለማጽናት አዕማደ ሓዋርያት የሆኑትን ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ቅዱስ ያዕቆብ፣ ቅዱስ ዮሐንስን ይዞ ወደ ቅዱሱ ተራራ ኣወጣቸው፡፡
ስለምን እነዚህን ብቻ አወጣቸው ቢሉ ለፍቅሩ ይሳሳሉና በፍቅሩ ይናደዳሉና ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታ እሞታለሁ ቢለው " አንተስ አትሞትም እኔ እሞታለሁ እንጂ " ማለቱ እኒም እኔ የምጠጣውን ጽዋ (ሞት) ልትጠጡ ትችላላችሁን? ቢላቸው " አዎ እንችላለን " (ስለኣንተ እንሞታለን) ማለታቸው እጅግ ቢወዱት ነው ስለዚህ ሦስቱን መረጣቸው፡፡
ቀሪዎችን ስምንቱ ሐዋርያትንና ይሁዳን ከእግረ ደብር አቆይቷቸዋል ከይሁዳም በስተቀር ከላይ ላሉት የተገለጠ ምሥጢር ከሥር ላሉትም ተገልጦላቸዋል፡፡ ይሁዳን ‹‹ያእትትዋ ለኃጥእ ከመ ኢይርአይ ስብሓተ እግዚአብሔር›› (የእግዚአብሔርን ክብር እንዳያይ ኃጢአተኛው ያስወግዱታል፡፡) (ትን.ኢሳ.26÷10) እንዲል ኋላ የሚሠራት ኃጢአት ይህን ምሥጢር እንዳያይ አድርጋዋለች ምሥጢር የማይገልጥለት ከሆነ ከሌሎች ሐዋርያት ጋር አበብሮ እንዲሆን
ለምን አስፈለገ ቢሉ ከእነርሱ ቢለየኝ በሞቱ ገባሁበት ብሎ ምክንያት እንዳያገኝ ነው፡፡
መልኩም በፊታቸው ተለወጠ፤ ፊቱም ከፀሓይ ይልቅ አበራ፤ ልብሱም ልብስ አጣቢ ከሚያነጻው ይልቅ እንደ በረድ ፀዓዳ ሆነ፡፡ ‹‹ እነሆ ሙሴና ኤልያስም ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው›› ቅዱስ ጴጥሮስም ጌታን ‹‹ አቤቱ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው፤ ብትወድስ ሦስት ቤቶችን በዚህ እንሥራ፤ አንዱን ለአንተ÷ አንዱንም ለሙሴ÷ አንዱንም ለኤልያስ አለው›› በዚህ ቃል የትህትና እና የደካማነት ምልክት አለበት፡፡ ትህትና ያልነው ቅዱስ ጴጥሮስ ለራሱና ለባልንጀሮቹ ሓዋርያት ቤት ይሠራ ዘንድ ስለ አላሰበ ነው ራሱንና ባልንጀሮቹን እንደ ባሮች፤ ነቢያትን ደግሞ እንደ ጌቶች (የጌታ ባለማሎች) አድርጎ አስቧልና፡፡ ደካማነት የተባለው ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን ከሰማይ የወረደበትን (ሰው የሆነበት) ሥራ ትቶ በተራራ ላይ ይኖር ዘንድና
ራሱን የሚሰውርበትን ቤት ይሠራለት ዘንድ የተናገረው ነው፡፡ ስለዚህም ጌታችን ምድራዊ ቤት እንደማያስፈልገው ያስረዳው ዘንድ የክብሩ መገለጫ የሆነ ብሩህ ደመና መጥቶ እንደቤት ሁኖ ጋረዳቸው፡፡ ‹‹እነሆ በደመናው ውስጥም የምወደው በእርሱም ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት የሚል ቃል
መጣ፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ሰምተው ደንግጠው በግንባራቸው ወደቁ እጅግም ፈርተው ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስም ቀርቦ ዳሰሳቸው ተነሡ አትፍሩም አላቸው፡፡ ዓይናቸውንም አቅንተው ዓዩ ነገር ግን ከጌታችን ከኢየሱስ ብቻ በቀር ያዩት ማንም አልነበረም፡፡ ››
ከነቢያት ሁሉ ለይቶ ሙሴና ኤልያስ እንዲገለጡ ማድረጉ ስለምንድን ነው ቢሉ ሙሴ ከአምላክ ጋር 570 ጊዜ ያህል ቃል ለቃል ተነጋግሮት ነበርና ባለማልነቴ ይገለጥ ዘንድ ባይህ እወዳለው አለው፡፡ አምላክም ፊቴን ዓይቶ አንድ ሰዓት ስንኳ መቆም የሚቻለው የለም ብሎ መለሰለት ሙሴም ይህ ካልሆነማ ባለሟልህ መባሌ ምኑ ላይ ነው በቃልማ ሌሎቹንስ ታናግር የለምን ቢለው አምላክም " ድኅረሰ ትሬኢ ገጽየ " መሥዋዕት ሁኜ በምቀርብበት ጊዜ (በዘመነ ሥጋዌ) እታይሃለሁ ብሎት ነበርና ይህ እንዲፈጸም፡፡ (ዘጸ.33÷18-23)፤ ኤልያስ ስለአምላክ እጅግ በመቅናቱ ተስፋ ተሰጥቶት ነበርና፡፡ ክብሩ በተገለጠ ጊዜ ግን ሙሴ ‹‹ትኄይሰኒ መቃብርየ›› (መቃብሬ ትሻለኛለች ብሏል)፤ ኤልያስም ወደ እሳት ሠረገላው ተመልሷል፡፡
• አንድም፡- ሙሴ ኤልያስ ይሉሃል ብለውት ነበረና እግዚኣ ሙሴ ወኤልያስ መሆኑን በራሳቸው አንደበት ለማስመስከር፡፡
• አንድም፡- የሕያዋን (ሞት ያላገኛቸው) የሙታን (ሞት
ያገኛቸው) አምላክ መሆኑ ለማጠየቅ ነው ከእርሱ በቀር
የሙሴን መቃብር (ይሁ.ቍጥ.9)፤ ኤልያስም የተሰወረባት (ብሔረ ሕያዋንን) የሚያውቅ የለምና፡፡
• ፍጻሜው ግን፡- ደብረ ታቦር የቤተክርስቲያንና የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ እንድትሆን ነው፡፡
2. ደብረታቦር የተመረጠበት ምክንያትና ምሳሌነቱ፡-
• ደብረ ታቦር ማለት ደብር ተራራ ሲሆን ታቦር የቦታው ስም ነው ከኢያቦር ወገን የነበረ ቦር የሚባል ሰው ነበረና በሱ ስም ታቦር አሉት ታቦር ማለት ትልቅ ማለት ሲሆን "ታ" ን ጨምረው ታቦር ብለውታል።
በደብረ ታቦር ያደረገው በሌላ ያላደረገው ስለም ነው ቢሉ ትንቢቱ ምሳሌው ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ ትንቢቱ ‹‹ ታቦር ወኣርሞንዔም በስመ ዚኣከ ይትፌሥሑ ›› (መዝ 88÷12)ያለው ነው። ምነው ክብሩን የገለጠ በታቦር አይደለምን አርሞንዔምንም አነሳ ቢሉ ብርሃኑ እስከ አርሞንዔም ደርሷልና ነው፡፡
ምሳሌው ፡- በዚህ ተራራ ላይ ነቢያቱ ዲቦራ ከባርቅ ጋር በመሆን የከነዓናውያን ንጉሥና የጦር መሪ ሲሳራንና ኢያቡስን በጦርነት ድል አድርገውበታል (መሳፍንት 4፥5–24) ጌታም በልበ ሓዋርያት ያደረ ሰይጣንን ድል ነሥቶበታልና፡፡
• ደብረ ታቦር የቤተክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡ በዚህ ተራራ ላይ ብሉይን የሚወክሉ ነቢያት፤ ሓዲስንም የሚወክሉ ሐዋርያት እንዲሁም ሓጋጌ ሕግ የሆነም ጌታ እንደተገኙ በእግዚአብሔር ቤትም ብሉይና ሓዲስ እንደሚነገሩ ምእመናንም በእነዚህ ሕግ እንደሚመሩ ያስረዳል፡፡ መምህር ጳውሎስም ስለዚህ ነገር ሲያስረዳ ‹‹በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ ታንጻችኋልና፤ የሕንጻው የማዕዘን ራስ ድንጋይ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ እርሱም ሕንጻ ሁሉ የሚያያዝበት÷ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ግንብ የሚያድግበት ነው፡፡ እናነተ በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ማደሪያ ልትሆኑ በእርሱ ታነጻችሁ፡፡›› አለ፡፡ (ኤፌ.2÷20-21)
• አንድም፡- የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ናት ነቢያትም
ሐዋርያት አንድ ሁነው እንዲወርሷት፤ ከመዓስባን ሙሴን
ከደናግላን ኤልያስን አመጣ መዓስባንና ደናግላን አንድ ሁነው እንደሚወርሷት፤ ከምዉታን ሙሴን ከሕያዋን ኤልያስ አመጣ ሁሉም በትንሣኤ እንደሚወርሷት ለማጠየቅ፡፡
3. የበዓሉ መጠሪያ ስሞች (ደብረ ታቦር / ቡሄ/ ቡሔ መባሉ ስለምንድ ነው?)
1.3K viewsAmha Silase ( Mekuria Tesfaye), 04:38