2022-06-18 21:07:49
ከዚህም በኋላ ያ ባለጸጋ ምክንያት አዘጋጅቶ "የሚያገለግለኝ ልጅ ይሆነኝ ዘንድ ልጅሽን ስጪኝ እኔም እየመገብኩና እያለበስኩ አሳድገዋለሁ ለአንቺም ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሻለሁ" አላት። ይህንንም ነገር ከበለጸጋው በሰማች ጊዜ ስለችግራ እጅግ ደስ አላት ልጅዋንም ሰጠችው እርሱም ሃያውን ወቄት ወርቅ ሰጣት ልጅዋንም ወሰደው የምሻው ተፈጸመልኝ ብሎ ደስ አለው።
ከዚህም በኋላ በልጁ ቁመት ልክ ሣጥን አሠርቶ ሕፃኑን በሳጥኑ ውስጥ አስገብቶ ዘጋበት እስከ ባሕርም ተሸክመው ወስደው በባሕር ጣሉት ክብር ይግባውና በጌታችን ፈቃድ ያ ሣጥን ሳይሠጥም ከዚያች አገር የሃያ ቀን መንገድ ያህል ርቃ ወደምትገኝ ወደ አንዲት አገር ወደብ እስከ ሚደርስ ባሕሩ ላይ ተንሳፈፈ። በባሕሩም አካባቢ በጎቹን አሰማርቶ የሚጠብቅ አንድ ሰው ነበርና ሣጥኑን በውኃ ላይ ተንሳፎ አየው እርሱም ከባሕሩ አውጥቶ ወደ ቤቱ ወሰደው ይህንም ሣጥን እንዴት እንደሚከፍተው ያስብ ጀመረ ይህንም ሲያስብ ወደ ባሕሩ ይሔድ ዘንድ ጌታችን በልቡናው ኃሳብ አሳደረበት ወዲያውኑም ተነሥቶ ወደ ባሕሩ ሔደና አንድ ዓሣ የሚያጠምድ ሰው አገኘ። ዓሣ አጥማጁንም "መረብህን በኔ ስም ጣል ለሚያዘውም ዓሣ ዋጋውን እሰጥሃለሁ" አለው። አጥማጁም እንዳለው አደረገ ያን ጊዜም ታላቅ ዓሣ ተያዘ ዋጋውንም ሰጥቶ ዓሣውን ተቀበለ ዓሣውንም ይዞ ወደቤቱ ሔደ ለራትም ይጠብሰው ዘንድ አረደው በሆዱም ውስጥ መክፈቻ አገኘ። በልቡም ይህ መክፈቻ ይህን ሣጥን ይከፍተው ይሆን" አለ በሣጥኑ ቀዳዳም በአስገባው ጊዜ ፈጥኖ ተከፈተ በውስጡም ይህን ታናሽ ብላቴና አገኘ። ልጅ የለውም ነበርና ታላቅ ደስታም ደስ አለው ጌታችንንም አመሰገነው። ሕፃኑንም በመልካም አስተዳደግ አሳደገው ሕፃኑንም አድጎ ጐልማሳ ሆነ።
ከብዙ ዘመናትም በኋላ ያ ባለ ጸጋ ተነሥቶ ወደ ዚያ አገር ሔደ በመሸም ጊዜ ወደ በግ ጠባቂው ደጅ ደረሰ በግጠባቂውን "እስከ ነገ የምናድርበት ማደሪያ በአንተ ዘንድ እናገኛለን? ኪራዩንም እሰጥሃለሁ" አለው በግ አርቢውም "እንዳልክ ይሁንና እደር" አለው ባለጸጋውም በዚያ አደረ። ራት በሚቀርብም ጊዜ ሕፃኑን ባሕራን ብሎ ጠራው ባለጸጋውም ሰምቶ "ልጅህ ነውን?" ብሎ ጠየቀው በግ ጠባቂውም "አዎን ታናሽ ሕፃን ሆኖ ሳለ ከባሕር አግኝቼዋለሁና እግዚአብሔር የሰጠኝ ልጄ ነው" አለው ባለጸጋውም "በምን ዘመን አገኘኸው" አለው እርሱም "ከሃያ ዓመት በፊት" ብሎ መለሰለት። ያን ጊዜም እርሱ ወደ ባሕር የጣለው መሆኑን አውቆ አጅግ አዘነ።
በማግሥቱም ጎዳናውን ሊጓዝ በተነሣ ጊዜ ሰይጣናዊ ምክንያት አመካኝቶ በግ ጠባቂውን እንዲህ አለው "ዕገሊት ወደምትባል አገር በቤቴ የረሳሁት ጉዳይ ስለ አለ እንድልከው ልጅህን ትሰጠኝ ዘንድ እሻለሁ እኔም የድካም ወጋውን ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሃለሁ" አለው። የብላቴናውም አባት ስለገንዘቡ ደስ ብሎት ልጁ ባሕራንን ሰጠው እንዲህም ብሎ አዘዘው "ልጄ ባሕራን ይህ የከበረ ሰው ስለ ጉዳዩ ወደ ቤቱ ይልክህ ዘንድ ና ወደ ቤትህም በሰላም ትመለሳለህ"። ባሕራንም "አባቴ ሆይ እሽ በጎ ያዘዝከኝ ሁሉ አደርጋለሁ" አለ።
ያን ጊዜም ባለጸጋው ወደ መጋቢው እንዲህ ብሎ ደብዳቤ ጻፈ "ይችን ደብዳቤ በምታነባት ጊዜ ደብዳቤዋን ይዞ የመጣውን ገድለህ በጒድጓድ ውስጥ ጣለው ማንም አይወቅ" በመካከላቸውም የሚተዋወቁበትን ምልክት ጽፎ አሸጋት። ለባሕራንም ሰጠው ለመንገዱም የሚሆነውን ስንቅ ሰጠው ባሕራንም ተነሥቶ ጉዞውን ጀመረ ሲጓዝም ሰንብቶ የአንዲት ቀን ጉዞ ሲቀረው እንሆ የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል በንጉሥ ጭፍራ አምሳል በነጭ ፈረስ ላይ ተቀምጦ "አንተ ጐልማሳ የያዝኸው ምንድነው?" አለው "ወደ ዕገሌ አገር ወደ ቤቱ ለማድረስ ከአንድ ባለጸጋ የተጻፈች መልክት ናት" አለው "ያቺን ደብዳቤ አሳየኝ" አለው እርሱም ስለ ፈራ ሰጠው።
በዚያን ጊዜም የከበረው መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ያቺን የሞት መልክት ደመሰሳት በእርሷ ፈንታም በንፍሐት ለውጦ እንዲህ ብሎ ጻፈ "ይቺን ደብዳቤ ይዞ ለመጣ ባሕራን ለሚባል ሰው ይቺ ደብዳቤ ደርሳ በምትነበብበት ጊዜ ልጄ ዕገሊትን አጋቡት በውስጥና በውጭ ያለ ንብረቴንና ጥሪቴን ወንዶችና ሴትች ባሮቼን ጠቅላላ ንብረቴንም አውርሼዋለሁና የፈለገውንም ሊያደርግ ሥልጣን ሰጥቼዋለሁና እኔን አትጠብቁኝ። እኔ ብዙ እዘገያለሁ የኔ ሹም ዕገሌ ሆይ በእኔና በአንተ መካከል ይቺ ምልክት እነኋት" ከዚህ በኋላ አሽጐ ለባሕራን ሰጠውና "ወደ ባለጸጋው ቤት ሒደህ ይቺን ደብዳቤ ለሹሙ ስጠው በጎዳናም እኔ እንደ ተገናኘሁህ አትንገረው እንዳይገድልህም ይህን የሞት ደብዳቤ ለውጨልሃለሁ" አለው። ባሕራንም እሺ ጌታዬ ያዘዜኸኝን ሁሉ አደርጋለሁ" አለ።
ባሕራንም ወደ ባለጸጋው ቤት በደረሰ ጊዜ ያቺን ደብዳቤ ለሹሙ ሰጠው በአነበባትም ጊዜ በመካከላቸው ያለውን ምልክት አገኘ አስተውሎም እርግጠኛ እንደሆነ አወቀ። ከዚህም በኋላ ለባሕራን ሠርግ አዘጋጅቶ እንደሚገባ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በተክሊል የባለጸጋውን ልጁ አጋቡት። አርባ ቀን ያህልም ደስታና ሐሴት እያደረጉ ኖሩ።
ከዚህ በኋላ ባለጸጋው ከሔደበት መመለሻው ጊዜ ሁኖ በደስታ የሆነውን የመሰንቆና የእንዚራ ድምጽ ሰምቶ "ይህ የምሰማው ምንድነው?" ብሎ ጠየቀ እነርሱም "ስሙ ባሕራን ለተባለ የአንተን ደብዳቤ ላመጣ ጐልማሳ ሰው ልጅህ ዕገሊትን አጋቡት እንሆ ለአርባ ቀናት በሠርግ ላይ ነው። ገንዘብህንና ጥሪትህን ሁሉ ወንዶችና ሴቶች ባሮችህን አንተ እንዳዘዝክ ሰጥተውታል" አሉት። ይህንንም በሰማ ጊዜ ደንግጦ ከፈረሱ ላይ ወድቆ በድንገትም ሞተ።
ባሕራንም በጎ ሥራዎችን የሚሠራ ሆነ የተገለጸለትና ከመገደል ያዳነው የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል እንደሆነ ሊገድለው የሚሻውን የባለጸጋውን ጥሪቱን ሁሉ ያወረሰውም እርሱ እንደ ሆነ ተረዳ የዚህንም የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤልን መታሰቢያ በየወሩ ያደርግ ጀመረ ቤተ ክርስቲያንም ሠራለት የቅዱስ ሚካኤልንም ሥዕሉን አሥሎ በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ አደረገው ከእርሱም ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ ባሕራንም ቅስና ተሹሞ እስከ ዕለተ ሞቱ በዚያች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚያገለግል ሁኖ ኖረ በዚህ በከበረ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል አማላጅነት ከእናቱና ከአባቱ ከልጆቹም ጋራ የዘላለም ሕይወትን ወረሰ።
+ + +
ቅዱስ አስተራኒቆስና ሚስቱ ቅድስት አፎምያ፦ ይህም ሰው በየወሩ ሦስት በዓላቶችን እያከበረ ኖረ እሊህም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደቱ መታሰቢያ በየወሩ በሃያ ዘጠኝ፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም በዓል መታሰቢያ በየወሩ በሃያ አንድ የከበረ የመላእክት አለቃ የሆነ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል መታሰቢያም በየወሩ በዐሥራ ሁለት ናቸው።
የሚሞትበትም ጊዜው ሲቀርብ እርሱ ሲሠራው የነበረውን ምጽዋት ይልቁንም እሊህን ሦስቱን በዓላት እንዳታስታጉል ሚስቱን ቅድስት አፎምያን አዘዛት። እርሷም የከበረ የመልአኩ የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል ያሥልላት ዘንድ ባሏን ለመነችው እርሱም አሠርቶ ሰጣትና በቤቷ ውስጥ በክብር አኖረችው።
82 viewsBereket Damene, 18:07