Get Mystery Box with random crypto!

ክርስቶስን መውደድ እንዴት? (በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ) አንድ በጣም የምንወደው እንግዳ ወደ ቤ | ቤተ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

ክርስቶስን መውደድ እንዴት?
(በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)

አንድ በጣም የምንወደው እንግዳ ወደ ቤታችን ሲመጣ እጅግ በጣም ከመደሰታችን የተነሣ የምናደርግለት ኹላ ሊጠፋብን ይችላል፡፡ እንደምንወደው፣ እንደናፈቀን እንነግሯለን፡፡ ከዚያም በላይ የሚወደውን እናቀርብለታለን፡፡ ባይኖረን እንኳን ስላላቀረብንለት እናዝናለን፡፡ ያለንን፣ ቤት ያፈራውን ግን እናቀርብለታለን፡፡ ስለምንወደውና ስለናፈቀን ርሱን የሚያስከፋ ነገር ምንም አናደርግም፡፡ ብናደርግም ወዳጃችንን ኾን ብለን ለማስከፋት ብለን የምናደርገው አይደለም፡፡ እንወዷለን የምንለው እንግዳችንን ትተን ሌላ ሥራ አንሠራም፡፡ በቃላት ብቻ እወድኻለኁ ብንለው፥ ነገር ግን በተግባር እንግዳችንን መውደዳችን ባንገልጥ ግን እንግዳችን ያዝንብናል፡፡ ከቃላችን በላይ ተግባራችንን ስለሚያይም እንደምንወደው ብንነግረውም አያምነንም፡፡ መውደድ የቃላት ጨዋታ ሳይኾን በተግባር የሚገለጥ ነውና፡፡
ልክ እንደዚኹ ፍጹም ሰው ኾኖ፣ ባሕሪያችንን ባሕርይ አድርጐ ወደ እኛ የመጣውን ክርስቶስን እንደምንወደው እየተናገርን፥ ነገር ግን በተግባር የምናሳዝነው ከኾነ መውደዳችን ትክክለኛ መውደድ አይደለም፡፡ ብንወደው ኖሮ ልክ ከላይ እንደገለጥነው እንግዳችን የሚበላ ነገርን እናቀርብለታለን፡፡ የክርስቶስ መብሉስ ምንድነው? እርሱ እራሱ እንዲኽ ሲል ነግሮናል፡- “የእኔስ መብል የላከኝን ፈቃድ አደርግ ዘንድ ሥራውንም እፈጽም ዘንድ ነው” /ዮሐ.4፡34/፡፡
ተርቦ ስናየው የሚበላ ነገርን እንስጠው፤ ተጠምቶ ስናየው የሚጠጣ ነገርን እንስጠው፤ ርሱም ይቀበለናል፡፡ የሚቀበልንም ስለሚወደን ነው፤ ከማንወደው ሰው ስጦታን አንቀበልምና፡፡ ስጦታችን ትንሽ ሊኾን ይችላል፤ ነገር ግን አፍቃሪያችን ነውና ስለ ስጦታችን ታናሽነት አልቀበላችኁም አይለንም፡፡ ስጦታችን በርሱ ዘንድ ትልቅ ነው፡፡ በስንፍና አንያዝ እንጂ ስጦታችን አምስት ሳንቲምም ልትኾን ትችላለች፤ ርሱ ግን ወዳጃችን ነውና አምስት ሳንቲም ናት ብሎ ስጦታችንን አያቃልላትም፡፡ እንደ ድልብ ስጦታ አድርጎ አምስት ሳንቲሟንም ይቀበልልናል እንጂ፡፡ ስጦታችንን የሚቀበለው ድኻ ስለኾነ አይደለም፡፡ ስጦታችንን የሚቀበልልን ስለ ስጦታችን ታላቅነት ሳይኾን ስለ ልቡናችን ኀልዮት (intention) ነው፡፡ ስለዚኽ ስንሰጥ ክርስቶስ ስለተቀበለን ትንሽዋንም ስጦታችንን ይቀበል ዘንድ በቤታችን ታዛ ስለገባ ልናመሰግነው ይገባል፡፡ እውነተኛ ሐሴት ማለትም ይኸው ነው፤ በመቀበል ሳይኾን በመስጠት የምናገኘው፡፡ ወደ ቤታችን፣ ወደ ሕይወታችን የመጣው ለእኛ ሲል ነው፡፡ ነፍሱን አሳልፎ ለሞት የሰጠው ለእኛ ሲል ነው፡፡ ፍቅሩ ግን እዚኽ ላይ አላበቃም፡፡ አኹንም እኛ ጋር እየመጣ ነው፡፡ ሐዋርያው “ስለ ክርስቶስ መልእክተኞች ነን” ብሏል /2ኛ ቆሮ.5፡20/፡፡

ስለዚህ ተርበውና ተጠምተው ወደ እኛ የሚመጡት ሰዎች የክርስቶስ መልእክተኞች ናቸው ማለት ነው፡፡ የንጉሡን መልእክተኛ፡የሚያባርር ታድያ ማን ሞኝ ነው? ነገር ግን ብዙዎቻችን ሞኞች ኾነናል፡፡ የነገሥታት ንጉሥ የክርስቶስ መልእክተኞችን እያባረርናቸው ነውና፡፡ ክርስቶስን እንወድኻለን እያልን በተግባር ግን እናባርረዋለን፡፡ ከዚኽ የበለጠ ምስኪንነት ከወዴት ይገኛል? ክርስቶስን በቃል እወድኻለኁ እያሉ በተግባር ግን ርሱን ማባረር የማይጠቅም ብቻ ሳይኾን የሚጐዳን ጭምር ነው፡፡

እንኪያስ ተወዳጆች ሆይ! ክርስቶስን በቃልም ገቢርም እንውደደው፡፡ በታላቁ እንግዳችን በክርስቶስ ደስ መሰኛታችንን በተግባር እንግለጠው፡፡ ይኽን እንድናደርግ ርስቱንና መንግሥቱንም እንደ ቸርነቱ እንዲያወርሰን እኛን በመውደዱ ወደ እኛ የመጣው ደግሞም የሚመጣው ክርስቶስ ይርዳን አሜን!!!