Get Mystery Box with random crypto!

   'ፍቅር የሌለው እግዚአብሔርን አያውቅም፥ እግዚአብሔር ፍቅር ነውና' ካልን፤ እግዚአብሔር ደግሞ | በማለዳ ንቁ ቁጥር ! ፪

   "ፍቅር የሌለው እግዚአብሔርን አያውቅም፥ እግዚአብሔር ፍቅር ነውና" ካልን፤ እግዚአብሔር ደግሞ ፍጹም መልካምና ቅዱስ ነው፡፡ (1ኛ የዮሐንስ መልእክት 4፥8) ስለዚህ ፍቅርን የምናውቀው ቅዱስ በሆነው መልካም ነገር ሁሉ ውስጥ ነው ማለት ይሆናል፡፡

    ከጥንት የሰዎች መነሻ ታሪክ አንስቶ እስከ ዛሬው ዘመናችን ድረስ ክፉ መናፍስት የተቀደሰውን መልካም ነገር ባላንጣ ሆነው የሚዋጉት ፍቅርን እንዳንኖረው ነው፡፡ እግዚአብሔርን የማያውቅ ጊዜ፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ ትውልድ፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ ሕይወት፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ አሳብ፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ እውቀት፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ ጥበብ፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ ንብረት፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ ሥልጣን በምድራችን ላይ እንዲንሰራፋ ሰፊውን ድርሾ ወስዶ ሚናውን በሚገባ የተጫወተው የዲያብሎስ ሠራዊት፤ የአዳም ልጆች መልካቸውን ማስታወስ አቅቶአቸው፤ የዘመኑን ሥጋዊ መልክ መስለው እንዲኖሩ የፍቅርን ምንነትና ኃይል ከነፍሳችን እንዳይገለጥ ከጽድቅ መንፈስ በጣም የራቀ አኗኗር ለዓመታት አስለምዶን ቆይቶአል፡፡

   በመሆኑም አብዛኞቻችን የፍቅር እውነተኛ ትርጉም ተደብቆብናል፡፡ ፍቅር የሕይወታችን ብቻ ሳይሆን የሰብአዊነታችን አካል መሆኑን ስለዘነጋን፤ ፍቅርን አስፈላጊና በተመረጠ ቦታ ላይ የምንገልጸው ስጦታ አድርገነዋል፡፡ ከሌላ ሰው በተሰጠን ጊዜ የምንመልሰው ምላሽ አድርገነዋል፡፡ በቤተሰብ፣ በጾታና በትውውቅ ግንኙነቶች መካከል የተወሰነ የመግባባት አጥር አድርገነዋል፡፡ ሲመቸን፣ ደስተኛ ስንሆን፣ ጉድለት ሲጠፋልን፣ ችግር ሲርቅልን የምንገለጽው ስሜት አድርገነዋል፡፡ ፍቅር ግን እጅግ በጣም ትንሽ ከምትባለው የሰኮንዶች መልካም ነገር ጀምሮ ሁሉንም የተቀደሰ መልካም አሳብ፣ መልካም ቃልና መልካም አኗኗር የሚጠቀልል የመለኮት ውበት ነው፡፡

   ለዚህ ደግሞ መታመኛ ምስክራችን የተፈጠርንበት የልዩ ሦስትነት መልክ ነው፡፡ መልካችን የሆነው ወላዲ አባት እግዚአብሔር አብ መለኮታዊ አሳብ(ልብ) ነው፡፡ ተወላዲ ልጁ እግዚአብሔር ወልድ መለኮታዊ ቃል ነው፡፡ ከአብ የሠረፀው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሕይወት(እስትንፋስ) ነው፡፡ (የዮሐንስ ወንጌል 1፥1)

    ነፍስ የነዚህን ሦስት አካላት መልክ በሕልውናዋ በመያዝ፤ ልባዊ(የምታስብ)፣ ነባቢ(የምትናገር) እና ሕያው(የምትኖር) ሆናለች፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ ፍቅር ነው ካልን፤ እንግዲያ በልዩ አካላዊ ሦስትነቱም እንዲሁ አሳቡም ፍቅር፣ ቃሉም ፍቅር፣ ሕልውናውም ፍቅር ነው ማለት ነው፡፡ (አብ ፍቅር ነው፣ ወልድ ፍቅር ነው፣ መንፈስ ቅዱስ ፍቅር ነው)

   ስለዚህ የእኛ ሰው የመሆናችን ቁልፍ እዚህ ውሰጥ አለ፡፡ የሰብአዊነት መልካችን እግዚአብሔር ሲሆን፤ እንደ መልካችን በመገለጥ ፍቅርን ስናስብ፣ ፍቅርን ስንናገር እና ፍቅርን ስንኖር ሰውነትን አግኝተነዋል፡፡

   አንድ አሳብ፣ አንድ ቃልና አንድ ድርጊት በፍቅር ወለል ላይ ቆሞ እርምጃ ሲጀምር፤ መልኩ የሰውነትን ቅርጽና የሰውነትን መንፈስ ይይዛል፡፡ የእግዚአብሔርንም ኃይል ይሸከማል፡፡ (አንዱ ቃል በፍቅርና በጥላቻ ባሕሪይ ሲነገር የተለያየ ተጽዕኖ የሚፈጥረው በዚህ ምክንያት እንደሆነ ልብ ይሏል!) ከዚህ ባሻገር ግን፤ የሰው እጅና እግር፣ የሰው ጭንቅላት፣ የሰው ቆዳና በአጠቃላይ የሰውን ውጪያዊ መልክ መያዝ ብቻውን "ሰው" አያሰኝም፡፡ በዚህ ልኬት ላይ የሰውነት ሚዛን ቢሰፈር ኖሮ፤ ራሳቸው የሰው ልጆች ከሠሯቸው ተንቀሳቃሽ ሮቦቶች(artificial intelligence) ጀምሮ ብዙ ቁሳዊ ነገሮች ሰው የመሆንን ስያሜ ይጋሩት ነበር፡፡

ወደ ሥጋና ደሙ መጓዛችንን እንቀጥላለን...
#ጸባኦት_ይከተላችሁ
@bemaledanek