2023-04-10 14:26:16
ለይለቱል ቀድር
- ቁርአን የወረደባት ለሊት ናት
እኛ (ቁርኣኑን) በመወሰኛይቱ ሌሊት አወረድነው፡፡[አል ቀድር 1]
- ከአንድ ሺህ ወራት በላጭ ናት
መወሰኛይቱ ሌሊት ከሺሕ ወር በላጭ ናት፡፡[አል ቀደር 3]
ከአንድ ሺህ ወራት በላጭ ናት በሚለው ፍቺ ላይ የእውቀት ባለቤቶች የተለያየ ንግግር አላቸው።
ኢብኑ ጀሪር አጥጦበሪይ እንዲህ ይላሉ፦
" ለይለቱል ቀድር ባለችበት በእዚህች አንድ ለሊት የሚሰራ ስራ ለይለቱል ቀድር ከሌለባቸው አንድ ሺህ ወራቶች ከሚሠራው ስራ በላጭ ነው"[ተፍሲር አጥጦበሪይ 30/167]
የሚለው ሃሣብ አመዛኝ መሆኑን ይናገራሉ።
- መላእክቶች እና ጅብሪልም ወደ ምድር ይወርዳሉ
በርሷ ውስጥ መላእክትና መንፈሱ(ጅብሪል) በጌታቸው ፈቃድ በነገሩ ሁሉ ይወርዳሉ፡፡[አል ቀድር 4]
ነብዩ እንዲህ ብለዋል፦ ለይለቱል ቀድር ሃያ ሠባተኛው ወይም ሃያ ዘጠነኛው ለሊት ነው። በዚህች ለሊት ላይ መላእክቶች ምድር ላይ ከጠጠሮች ብዛት በላይ ሆነው ይወርዳሉ።
[ኢብኑ ኹዘይማህ2194].
- ሠላም የሆነች ለሊት ናት
እርስዋ እስከ ጎህ መውጣት ድረስ ሰላም ብቻ ናት፡፡[አል ቀድር 5]
የእውቀት ባለቤቶች ፍቺዋ ላይ የተለያዩ ሃሣቦች አንስተዋል። ከነዚህም፦
*ከመጥፎ ሁሉ ሰላም የሆነች ለሊት ናት
*በእርሷ ውስጥ ሰላም እንጂ አይኖርም
* የመላእክቶች ሠላምታ ለምዕመናኖች
* ሸይጧን በእርሷ ለሊት መጥፎን ማድርግ አይችልም...
- የተባረከች ለሊት ናት
እኛ (ቁርኣኑን) በተባረከች ሌሊት ውስጥ አወረድነው፡፡ [ሡረቱል ዱኻን 3]
ኢብኑ ዓባስ 'ለይለቱል ቀድር' ናት ብሏል።
- አመታዊ ውሳኔዎች የሚወሰኑባት (ሚብራሩባት)ለሊት ናት
በውስጧ የተወሰነው ነገር ሁሉ ይልለያል፡፡[ሡረቱል ዱኻን 4]
- ነብዩ እንዲህ ብለዋል "ለይለተል ቀድርን አምኖ እና ከጌታው ምንዳን ፈልጎ እርሷን (በአምልኮ በስግደት) የቆማት ያለፈው ወንጀሉ ይማርለታል." [ቡኻሪይ እና ሙስሊም]
- ስያሜዋን አስመልክቶ 'ቀድር' በምትለዋ ቃል አማካኝነት የእውቀት ባለቤቶች በፍቺዋ ላይ ልዩነት አላቸው። ቀድር ማለት (ተዕዚም)ማላቅ ማለት ነው።ቁርአን ስለወረደባት፣ መላእክቶችም ስለሚጣዷት፣... ለይለቱል ቀድር ማለት የላቀች ለሊት ማለት ነው።
-ለይለተል ቀድርን መጠባበቅ እና አስርቱ ቀናት ላይ በአምልኮ ጥረት ማድረግ
-ነብዩ እንዲህﷺ ብለዋል፦
" ለይለተል ቀድርን ከረመዳን የመጨረሻ አስርቱ ጎዶሎ በሆኑ ለሊቶች ላይ ተጠባበቁ።" [ቡኻሪ እና ሙስሊም]
-ዓዒሻ አሏህ መልካም ስራዋን ይውደድላትና እንዲህ ትላለች፦ ነብዩﷺ የመጨረሻ አስርቱ የረመዳን ቀናት ሲገቡ ማሠሪያቸውን(ቀበቷቸውን) ጠበቅ ያደርጉ ነበር፣ ለሊቱንም በአምልኮ ያሣልፉ ነበር፣ (ለሶላት)ቤተሰቦቻቸውንም ይቀሰቅሱ ነበር።[ቡኻሪይ እና ሙስሊም]
ቀበቷቸውን ጠበቅ ያደርጉ ነበር ማለት፦ ሚስቶቻቸውን ርቀው አምልኮ ላይ ጥረት ያደርጉ ነበር። ለማለት ነው።
ነብዩﷺ እንዲህ ብለዋል፦ " ይህ ወር በእርግጥም ተጥዷችኋል(መጥቷችኋል)፤ በእርሱ ውስጥ ከሺህ ወራቶች የሚበልጥ ለሊት አለ፤ እርሷን የተነፈገ በእርግጥም መልካም ነገር የተባለን በጠቅላላ ተነፍጓል፤ የእርሷን መልካም ገጠመኝ ያላገኘ እድለቢስ ቢሆን እንጂ አይነፈግም።[ኢብኑ ማጀህ ዘግቦታል /ሀዲሱን የሀሠን ደረጃ ሰጥተውታል]
- በዚህች ለሊት የሚወደዱ ስራዎች
በጥቅሉ መልካም በተባሉ የአምልኮ ዘርፎች ላይ ጥረት ማድረግ ይወደዳል። ነብዩ የረመዷን የመጨረሻ አስርቱ ቀናት ላይ ከሚከውኗቸው ተግባራት መካከል፦
- ኢዕቲካፍ
ዓዒሻ አሏህ መልካም ስራዋን ይውደድላትና፦
"ነብዩﷺ የረመዷን መጨረሻ አስርቱ ቀናትን ዒዕቲካፍ ያደርጉ ነበር አሏህ ከዚህ አለም በሞት እስኪያሰናብታቸው ድረስ።" ብላለች [ቡኻሪ እና ሙስሊም]
- ለሊቷን በሶላት መቆም
ነብዩﷺ እንዲህ ብለዋል "ለይለተል ቀድርን አምኖ እና ከጌታው ምንዳን ፈልጎ እርሷን (በአምልኮ በስግደት) የቆመ ያለፈው ወንጀሉ ይማርለታል." [ቡኻሪይ እና ሙስሊም]
'አምኖ' ማለት ምንዳውን ከአሏህ እንደሚያገኝ አረጋግጦ እውነት ብሎ ማለት ነው።
'ምንዳን ፈልጎ' ማለት እዩልኝን ወይም ሌላን ሳይሆን የጌታውን ምንዳ ብቻ ከጅሎ ማለት ነው።
- ዱዓ
ዓዒሻ አሏህ መልካም ስራዋን ይውደድላትና ለነብዩ ﷺእንዲህ አለቻቸው፦ ለይለቱል ቀድርን ብገጥም(ባገኝ) ምን ስል ዱዓ ላድርግ ?
ነብዩﷺ " አሏሁመ ኢነከ ዓፍውን ቱሂብል ዓፍወ ፈዕፉ ዓኒ" (አሏህ ሆይ! አንተ ይቅር ባይ ነህ ይቅር ማለትንም ትወዳለህና ይቅር በለኝ) በይ አሏት።[ቲርሚዚይ]
- ቤተሰቦችን ለሶላት መቀስቀስ
ነብዩﷺ "... (ለሶላት)ቤተሰቦቻቸውንም ይቀሰቅሱ ነበር።" [ቡኻሪይ እና ሙስሊም]
-ጊዜዋ
የተገደበ ጊዜዋን አስመልክቶ በእውቀት ባለቤቶች መሃከል ሰፊ ልዩነት (ወደ አርባ የሚጠጉ ንግግሮች) ሲኖሩ ከነዚህ አመዛኙና የተሻለው ብለው ያስቀመጡት "ከረመዷን የመጨረሻ አስርቱ ጎዶሎ ለሊቶች ላይ ናት እርሷም ትቀያየራለች " የሚለው ነው።
ትቀያየራለች የሚለው በተለያዩ ሃዲሶች ላይ የተለያዩ ቀናቶች በመጠቀሳቸው ነው።
ሃያ አንድ፣ ሃያ ሶስት፣ ሃያ ሰባት፣ የመጨረሻዋ ለሊት ላይ ተጠባበቋት የሚሉ ዘገባዎች አሉ።
-ለሊቷ የመደበቋ ወይም ያለ መታወቅ ምክንያት ምንድነው?
ዑባደት ኢብኑ ሷቢት እንዲህ ይላል፦
ነብዩﷺ ለይለተል ቀድር ሊያሣውቁን ወጡ(ጉዞን ጀመሩ)፤ (በመንገዳቸው ላይ) ሁለት ሙስሊሞች ተጨቃጨቁ (ሲጨቃጨቁ ተመለከቱ)፤ ከዚያም ነብዩﷺ እንዲህ አሉ፦
"ወደ እናንተ ለይለተል ቀድር መች እንደሆነ ልነግራቹህ በወጣሁበት እገሌ እና እገሌ ሲጨቃጨቁ ረሣሁት(ተወገደብኝ)፤ ለእናንተ መልካም ሊሆን ይችላል(ይሆናል)፤ ስለዚህም በሃያ አምስት፣ ሰባት እና ዘጠናኛው ለሊቶች ተጠባበቋት።" [ቡኻሪይ]
በሌላ ዘገባም ነብዩﷺ እንዲህ ብለዋል፦
" ለይለተል ቀድርን(በህልሜ) ተነገረኝ(እንዳውቅ ተደረግኩኝ) ከዚያም ከፊል ቤተሰቦቼ ቀሰቀሱኝና ረሣሁት።" [ሙስሊም]
ሃፊዝ ኢብኑ ሃጀር እንዲህ ይላሉ፦
" ይህ ሌላኛው ምክንያት ሲሆን፤ ምክንያቶቹ የተደጋገሙ ሊሆኑ ይችላሉ።አንደኛው ሃዲስ ላይ የተጠቀሰው ለሊቷን እንዲያውቁ የተደረጉት በህልም ሲሆን የመርሳታቸው ምክንያት ደግሞ የቤተሰቦቻቸው መቀስቀስ ነው። ወይም በሌላ ሀዲስ ላይ እንደተጠቀሰው የመርሳታቸው ምክንያት ጭቅጭቁ ህልማቸውን አቋርጦ ቀስቅሷቸው ነው። ወይም ሁለቱን ታሪኮች ወደ ማስማማት ሲኬድ በሁለት ምክንያቶች ሁለት መርሣቶች ተገኝተዋል ይባላል። ወይም ቤተሰቦቼ ቀሰቀሱኝና የሁለት ሰዎችን ጭቅጭቅ ሰምቼ እነርሱን ለመዳኘት በገባሁበት በእነርሡ ጉዳይ በመወጠሬ ረሣሁት የሚለውንም ፍቺ ሊሰጥ ይችላል። [ፈትሁል ባሪ 4/268]
- ለይለቱል ቀድር የመደበቋ ጥበብ
ሃፊዝ ኢብኑ ሃጀር እንዲህ ይላሉ፦
" የእውቀት ባለቤቶች እንዲህ ብለዋል፦ ለይለተል ቀድር ያለመታወቋ ጥበብ እርሷን ለማግኘት ጥረት ማድረግ እንዲኖር ተፈልጎ ነው። ለሊቷ የታወቀች ብትሆን ሰዎች እርሷን ለሊት ብቻ ይጣዱ ነበር።
[ፈትሁል ባሪ 4/315]
- ምልክቶቿ
ለሊቷ ለይለተል ቀድር መሆኗን የሚያመላክቱ ሀዲሶች ተዘግበዋል። ከነዚህም ሶሂህ ከሆኑት
- በለሊቷ ሞቃታማ እና ቀዝቃዛማ ያልሆነ የአየር ሁኔታ መታየት
ነብዩﷺ እንዲህ ብለዋል፦ "ለይለተል ቀድር መች እንደሆነ ተነግሮኝ(ተገልጦልኝ) ነበር ረሣሁት። የመጨረሻዎቹ አስርቱ ለሊት ላይ ናት። እርሷም የንጋት ፍካት የሚታይባት ሞቃት እና ብርዳማ ያልሆነች ለሊት ናት።"[ኢብን ኹዘይማህ]
t.me/alhadith_islamic
38 views11:26