2022-07-10 07:36:40
የዒድ ትዝብት
=================
በቅድሚያ ሰላቱን ጨምሮ ሙሉ ስርአቱ እንዲያምርና እንዲሰምር የበኩላቸውን ያደረጉና የሚያደርጉ ሁሉ ሊመሰገኑ እንደሚገባ ግልፅ ነው፤ በተለይ በአንዳንድ ቦታዎች ካለፉት አመታት የተሻሉ መስተንግዶዎችና ቅንጅቶች መኖራቸው አስደሳች ነው። ይህ በእንዲህ እንዳለ፦
1/ ሰዎች ኹጥባውን እንዲሰሙ ለማድረግ በመጓጓት ኹጥባውን ማድመጥ ግዴታ እነደሆነ አድርጎ ማቅረብ ትክክል አይደለም፤ "ዋጂብ" የሚለው ቃል ከአፍ ባይወጣ እንኳ ከመጠን ያለፈ ግፊትና ጫና ማሳደር ከረሱላችን ፈቃድ ጋር አይገጥምም።
عَنْ عَبْدِ اللَّهِ بْنِ السَّائِبِ، قَالَ: شَهِدْتُ مَعَ رَسُولِ اللَّهِ - صلى الله عليه وسلم - الْعِيدَ، فَلَمَّا قَضَى الصَّلَاةَ، قَالَ: " إِنَّا نَخْطُبُ، فَمَنْ أَحَبَّ أَنْ يَجْلِسَ لِلْخُطْبَةِ فَلْيَجْلِسْ، وَمَنْ أَحَبَّ أَنْ يَذْهَبَ فَلْيَذْهَبْ " أخرجه أبو داود والنسائي وابن ماجه.
«ዐብዱላህ ኢብኑ አስ-ሳኢብ እንዲህ አሉ፦ ከአላህ መልእክተኛ ጋር በዒድ ተገኝቻለሁ፤ ሰላታቸውን እንደጨረሱ እንዲህ አሉ፦ "እኛ ኹጥባ እናደርጋለን፤ ለኹጥባው መቀመጥ የፈለገ ይቀመጥ፤ መሄድ የፈለገም ይሂድ።"»
[አቡ ዳዉድ (ቁ 1155)፣ አን-ነሳኢይ (ቁ 1571)፣ ኢብኑ ማጀህ (ቁ 1290)]
ሰዎች ግዴታ ያልሆነባቸውን ተግባር እንዲሰሩ ለማድረግ የሚቀየር ህግ ሊኖር አይችልም። መርዋን ኢብኑ'ል-ሐከም የተባለው ኸሊፋ የዒድን ኹጥባ ከሰላቱ በፊት ያስቀደመው "ሰዎች እንደ ቀድሞው ( ኹጥባውን ለማድመጥ) አይቀመጡልንም!" በሚል መነሻ ቢሆንም ከአቡ ሲዒድ አል-ኹድሪይ እና ከሌሎች ተቃውሞ ገጥሞት ነበር። (አል-ቡኻሪ ቁ 956 እና ሙስሊም ቁ 889)
ኢብኑ ተይሚያ ለዚህ የመርዋንና የመሰሎቹ ተግባር ምላሽ ሲሰጡ ያለማድመጣቸው መንስኤ የራሱ ማጓደል እንደሆነና መልእክተኛው ያደርጉ እንደነበረው ለህዝቡ መድህን የሚጠቅም ምክር በማስተላለፍ ፈንታ ስልጣኑን የሚያስጠብቅበትን ንግግር በመደስኮሩ ወይም ለዲናቸው አስቦ ቢሆን እንኳ የሚጠቅማቸውን ቁም ነገር ባለማስተማሩ እንደሆነ ጠቅሰው ከዚያ ባሻገር ደግሞ አላህ ስለስራው እንጂ ስለሌሎች ስራ እንደማይጠይቀው አወስተዋል።
[ኢቅቲዷኡ'ስ-ሲራጢ'ል-ሙስተቂም (2/104)]
2/ ኹጥባውን ማዳመጥ "ግዴታ አይደለም" ማለት እንደፈለጉ በማውራትና ግርግር በመፍጠር የሚያደምጡትን "ማወክ ይቻላል" ማለት አይደለም። ስለዚህ ወይ ማዳመጥ፤ ወይ ደግሞ ሳይረብሹ ውልቅ ማለት!
3/ ኹጥባው ብዙሃኑ በሚረዱት ቋንቋ ቢሆን ምናልባት ብዙ ሰው ለማድመጥ የተሻለ ፍላጎት ያድርበት ነበር።
በአቡ ሐኒፋ መዝሀብ ኹጥባ በዐረብኛ መሆኑ በጥቅሉ ግዴታ አይደለም∷ አንዳንድ የሻፊዒያ መዝሀብ ሊቃውንትና ሌሎች ታዋቂ ምሁራን ይህንን አቋም ይጋራሉ∷ ሁሉም ታዳሚ ዐረብኛ የማይረዳ ከሆነ ደግሞ በሻፊዒያህና በሐናቢላህ መዝሀብም ጭምር በሚያውቁት ቋንቋ መኾጠቡ ይፈቀዳል∷
የኹጥባ አላማ መልእክትን ማስተላለፍ ነውና የዐረብኛ ቋንቋ ተናጋሪ ባልሆኑ አገራት በአገርኛው ልሳን ኹጥባውን ማስተላለፍ መፈቀዱ አለም አቀፉ የፊቅህ ጉባዔ፣ የሳውዲው ቋሚ የፈትዋ ኮሚቴና ሌሎች የዘመናችን የዒልም ተቋማትና በርካታ ምሁራን የመረጡት አቋም ሆኗል∷
4/ ሰዎች ኹጥባውን እንዳይሰሙ ተፅእኖ የሚያደርጉ ምክንያቶች አሉ፤ ለምሳሌ፦
- የድምፅ ማጉያ ሲስተም በአንዳንድ ቦታዎች አለመስተካከሉ
- የኹጥባው መርዘም
- ከኹጥባው በፊት ሌሎች ንግግሮች መኖራቸው (መልእክተኛው ከሰላት በፊት የሚያደርጉት ወይም የሚያስደርጉት ንግግር አልነበርምና!)
5/ የዒድ ሰላት በየቦታው የሚሰገድበትን ሰዓትና ደቂቃ አስቀድሞ በሚዲያ ማሳወቅ ብዙ አገሮች ላይ የሚሰራበት ጥሩ ልምድ ነው። ሰዎች አስቀድመው እንዲዘጋጁና ሰላቱ እንዳያመልጣቸው ያግዛል።
6/ ህዝቡ አስተናጋጆችን ቢታዘዝ ብዙ የሰልፍና የቦታ ችግሮች ባልኖሩ ወይም ቢኖሩም ባልተወሳሰቡ ነበር።
7/ አስተናጋጆች በተቻላቸው መጠን ትእግስትንና መልካም ባህሪን የተላበሱ ሊሆን ይገባል፤ ንግግራችውም በትህትና ቢሞላ መልካም ነው - በተለይ በድምፅ ማጉያ መልእክት የሚያስተላልፉ ወንድሞች!
መልካም ዒድ
تقبل الله منا ومنكم صالح الأعمال ustazilyas
@afzanmedia
72 views04:36