2022-05-15 15:03:48
#በተድባበ_ማርያም_ብቻ_የሚገኙ_ቅርሶች፦
ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ለእመቤታችን ከሳላቸውና ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚገኙት ከ4ቱ ምስለ ፍቁር ወልዳ ስዕለ አድኅኖዎች ውስጥ አንዷ ስዕለ አድኅኖ ባለ 3 ተከፍች የገበታ ስዕልና ጥንታዊና ስነ ጥበባዊ ቅርሶች ይገኛሉ፡፡
የንጉሥ ዳዊት ወንበር፣
ሥዕርተ ሐና (የእመቤታችን እናት የእናታችን የቅድስት ሐና ፀጉር) በገዳሙ ይገኛል። ይህ ጸጉር የተቀመጠበት የሽክላ ገንቦ እጅግ ጥንታዊና በስነ ጥበባዊ ይዘቱ የሚያስገርም ትእይንት ይፈጥራል።
በ4ኛው መ/ክ/ዘመን ወንድማማቾቹ ቅዱሳን ነገሥታት አብርሃ ወአጽብሐ ያነጹት ስውር ቤተ መቅደስ፣
አዛዥ ጌራና አዘዥ ዘራጉኤል በእጃቸው ያመለከቱት ታላቁ ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም ያስተማሩበት ድጓ፣
የጥንታዊያን ነገሥታትና ጳጳሳት ከወርቅና ከብር የተሰሩ በወቅቱም ለገዳሟ የተበረከቱ የክብር አልባሳትና የነገሥታት ዘውድ እንድሁም አጼ ገላውዴዎስ ታቦተ ተድባበ ማርያምን ይዘው ዘምተው አላዊው ግራኝ አህመድን ሲያሸንፉት ከአላዊው ግራኝ የማረኳቸው አልባሳትና አንድ ሰው ተንገዳግዶ የሚያነሳው የግራኝ የበቅሎው ቃጪል
የበግ ምስልና የተቁለመለመ የበግ ቀንድ ያለበት መስቀል በዚያ ይገኛል፡፡ የዚህ መስቀል ብርሀን የሚያስገርምና ዓይንን የሚያንፀባርቅ ሲሆን ከምን አይነት ማዕድን እንደተሰራ አይታወቅም፡፡
ከጥንታዊያን ነገሥታትም መካከል ዐፄ ካሌብ ወደ ደቡብ አረቢያ የናግራንን ክርስቲያኖች ለመርዳት ሲዘምቱ ፓትርያርክ ዘሙሴ እሱም የኦየሩሳሌምን ገዳም ያቀናና በመጨረሻም በአባ ጴንጠሌዎን ገዳም ገብቶ ያረፈ አባት ጋር ዘምተው ድል አድርገው ሲመለሱ ይዘው የሄዱትን ጋሻ በስዕለት ለተድባባ ማርያም አስገብተውት በቦታው ይገኛል፡፡
የዕብራይስጥ ሲኖዶስና የአረማይክ ቅዳሴ እግዚእ በቦታው ላይ ይገኛል፡፡
በዚህ ገዳም ከ1000 ያላነሱ የብራና ጥንታዊያን መጻሕፍት ይገኛሉ፤ እነዚህም መጻህፍት ክፊሎቹ በጥንታዊት የአክሱም ዘመን መንግስት የተጻፉ ሲሆኑ ሌሎቹ ደግም በመካከለኛው ዘመን የተጻፉ ናቸው፡፡
በአረማክ ቋንቋ የተጻፉ የሰሌዳ መጻሕፍት፣
በዐረብኛና በግእዝ የተጻፉ በርካታ ጥንታዊያን መጻሕፍት፣
ወንጌል ዘወርቅ እየተባለ የሚጠራ ትልቅ የወርቅ ጉብጉብታ ያለበት የወንጌል መጽሐፍ ቅዱስ፣
ገድለ ጊዮርጊስ ወልደ አሚድ፣
ገድለ አዳም ከታላቅነቱ የተነሳ ሁለት ሰው ከቀኝ ከግራ ሆኖ የሚዘው ባለ ገበታ የብራና መጽሐፍ፣ እና ሌሎች በርካታ ጥንታዊያን መጻሕፍት በቅርስነት ተመዝግበው በተድባበ ማርያም የሚገኙ የመንፈሳዊ እሴት ማንጸባረቂያዎች ናቸው። በተጨማሪም ገዳሟ ሌሎችንም በርካታ ቅርሶችን በክብር ጠብቃ ይዛለች።
#መስቀል_በተድባበ_ማርያም፦
በርካታ ጥንታዊ የእጅና የመጾር መስቀል ይገኛሉ። ከእነዚህም መካከል፦
የመጀመሪያው የኢትዮጵያዊ ጳጳስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን የቀደሰበትና ለተድባበ ማርያም የሰጡት "ነዋ በግዑ" የእጅ መስቀል እና "ዘይቄድስ ኩሎ" የተባለ ቅብዓ ሜሮን፣
የመጥመቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ መስቀል፣
የእጨጌ ዮሐንስ በትረ ሆሣዕና እና የእጅ መስቀል፣
የአቡነ አኖሪዎስ የእጅ መስቀል፣
የአቡነ ቄርሎስ የእጅ መስቀልና ሌሎች ከወርቅ የተሰሩ ጥንታውያን መስቀሎች ናቸው፡፡
#በገዳሟ_ከሚገኙ_አጽመ_ቅዱሳን_መካከል፦
ሄሮድስ የጨፈጨፋቸው ሕጻናት ዓጽም በከፊል፣
የቅዱስ ጊዮርጊስ አውራ ጣት
በአጠቃላይ የ28 ሰማእታት ዓጽም የሚገኝ ሲሆን እንዲሁም በልዩ ስፍራ የሚገኘው መካነ መቃብር የዐፄ ገላውዴዎስን ጨምሮ የ6 ነገሥታትና የ4 እጨጌዎች ተሰብስቦ ይገኛል፡፡
ከ9ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ እሰከ 11ኛው ድረስ የጨለማው ዘመን በመባል ይታወቃል፡፡ ይህም የግእዝ ሥነ ጽሁፍ የተዳከመበት ዮዲት ከተከታዮቿ ጋር በመሆን ባደረሰችው ወረራ ሰነ ጽሁፍ የጠፉበት የትርጉም ስራዎች እንደቆሙ ተደረገበት ወቅት ነበር፡፡
ከ9-15ኛው ክፍለ ዘመን በዘጠነኛው መቶ ክፍለ ዘመን 40 ዓመታት መሉ ቤተ ክርስቲያንን ስታቃጥል መጸህፍትንና ሌሎችንም የቤተ ክርስትያን ንዋያተ ቅድሳት ሁሉ ተደምሰሱ፡፡ አያሌ የቤተክርስቲያን ሊቃውንት (ካህናት) አብረው ተቃጠሉ፡፡ በዚህም ጊዜ በኢትዮጵያ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በዕጅጉ ተዳክሞ ነበር። ነገር ግን በዚህች ጥንታዊት ገዳም ምንም አይነት ወረራ አልደረሰባትም።
በ15ኛው ክፍለ ዘመንም ግራኝ የተነሳበት በመሆኑ ቱርክ እየተላላከ ባስመጣው መሣሪያና በድብቅ ያስለጠነውን ወታደር አሳልፎ ኢትዮጵያን መውረር ሲጀምር 15 ዓመት ያህል ያለማቋረጥ በኢትዮጵያ ላይ የቱርክ ጥይት እንደ እሳት ሲነድ ከዮዲት ጉዲት ወራራ ተርፈው የቀሩና ከእርሷም በኋላ የተተኩት የቤተክርስቲያን ቅርሶች በግራኝ ወራራ ጨርሰው ሲወድሙ የግራኝ ወራራ በቤተክርስቲያንና በምዕመናን ሕይወት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሲያስከትል አያሌ ገዳማትና አድባራት ሲቃጠሉና ሲመዘበሩ ይህቺ ታላቅ የታሪክና የቅርስ ባለቤት የሆነችው ርእሰ አድባራት ወገዳማት ተድባበ ማርያም ምንም አይነት ቃጠሎና የቅርስ ዝርፊያ አልደረሰባትም፡፡
ከዚህም አልፎ በአጼ ሱስንዮስ ዘመነ መንግስት ካቶሊካዊያን በየገዳማቱና በየአድባራቱ እንዲሁም በየቤቱና በየለቅሶው ቤት በየገበያው እየዘሩ የካቶሊክን ሃይማኖት ለማስፋፋት ሲጥሩ የኢትዮጵያ ቅዱሳን ዓጽም ካረፈበት እየወጣ መቃጠል ሲጀምር ብዙ ካህናትና መነኮሳት ሊቃውንትና ምእመናን ልጅ አዋቂ ሳይባል የተዋህዶ ሃይማኖት ልጆች የሆኑ ሁሉ ባሉበት እየታደኑ አሰቃቂ ድርጊት ሲፈጸምባቸው የርእሰ አድባራት ወገዳማት ተድባበ ማርያም ሊቃውንትና ካህናት መነኮሳት ግን እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ በፆምና በፀሎት ፀንተው መከራውንና ችግሩን በመቋቋም ተዋህዶ ሃይማኖታቸውን አቅንተው እስከ አሁኗ ሰዓት ድረስ ታሪካቸውንና ቅርሳቸውን በመጠበቅ ይገኛሉ፡፡
ስለዚህ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሊቃውንት እንዲሁም ምእመናንና ምእመናት ሁላችሁም ይህንን አስደናቂ የሆነውን የርእሰ አድባራት ወገዳማት ተድባበ ማርያም ታሪክ አንብቦ (ሰምቶ) በመረዳት ልዑልና ቅዱስ እግዚአብሔር ፍቅዶላቸሁ ከያላችሁበት ወደ ቦታዋ ድረስ በመሄድ በረከት እንድታገኙ አደራችን የፀና ነው፡፡
☞ ምንጭ ማህበረ ፊልጶስ ወአባ ሳሙኤል ዘዋልድባ
1.8K views12:03