2022-06-03 07:25:16
#ግንቦት_26 ልደቱ ለ አቡነ ሀብተማርያም ጻድቅ
† እንኳን ለአባታችን አቡነ ሀብተ ማርያም የልደት መታሰቢያ በዓል አደረሰን አደሰችሁ ::
ሰላም ለጽንሰትከ እማኅፀነ ቅድስት ዮስቴና፤
በብሥራተ ጻድቅ ባሕታዊ ሠናየ ዜና፡፡
ሀብተማርያም ጴጥሮስ ሐዋርያ ወልደ ዮና፤
መሐረኒ ምግባረ ጽድቅ ወጸግወኒ ልቡና፤
አፍቅሮ ቢጽ እኅሥሥ ዘምስለ ፍጽመት ትሕትና፡፡
#አቡነ_ሀብተማርያም
በመራ ውዕይ (ሸዋ ፥ ቡልጋ) ከአባታቸው ፍሬ ቡሩክና ከእናታቸው ቅድስት ዮስቴና ነው የተወለዱት፡፡ ወላጆቹ በተለይም እናቱ ከማግባቷ በፊት መንና ነበር፡፡ ጻድቁን እንደምትወልድ በበቃ ባሕታዊ ተነግሯት ጻድቁን ወልዳ በጽድቅ ኑሮ ኑራ አክሊላትን ተቀብላ በክብር አርፋለች፡፡
አቡነ ሀብተማርያም በሕፃንነታቸው ከእናታቸው ጋር ቆመው ሲያስቀድሱ ‹‹እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ›› ሲባል ይሰማሉ፤ በሕፃን አንደበታቸው ይዘው ሌሊት ሌሊት እየተነሱ ‹‹ማረን እባክህን›› እያሉ ይሰግዱ ነበር፡፡ ትንሽ ከፍ ብለው በእረኝነት ሳሉም ፍጹም ተሐራሚና ጸዋሚ ነበሩ፡፡ ጸጋው ስለ በዛላቸውም ልጅ ሆነው ብዙ ተአምራትን ሠርተዋል፤ ጓደኞቻቸው የሌላ ሰው እሸት እየነቀሉ ሲበሉ እርሳቸው ግን አይበሉም ነበር፡፡ የፈጣሪውን ስም ያቃለለውን አንድ እረኛም በአየር ላይ ሰቅለው አውለውታል፡፡
ወደ ት/ቤት ገብተው ትምህርትን ከቀሰሙ በኋላ ለአካለ መጠን ሲደርሱ ቤተ ሰቦቻቸው ሚስት አጩለት፤ እርሱ ግን ወደ አፋር ከአባ ሳሙኤል ዘንድ ሂዶ ለ12 ዓመታት ረድዕ ሆኖ ተቀመጠ፡፡ ከአፋርም ወደ ምኔት ወደሚባል ቦታ መጥቶ በታላቁ አባት በአባ መልከ ጼዴቅ እጅ መነኰሰ፤ ከአፋር ወደ ይነውፋ፥ ከይነውፋ ወደ ጉሐርብ ወደሚባል ሃገር ሂዶ ምናኔን፣ ትሩፋትንና ተጋድሎን ሠራ፡፡
ለአብነትም፤
† ባሕር ውስጥ ሰጥሞ 500 ጊዜ ይሰግዳል፤
† በየቀኑ 4ቱን ወንጌልንና 150 መዝሙረ ዳዊትን ይጸልያል፤
† በ40 ቀናት ቀጥሎም በ80 ቀን አንዴ ብቻ ይመገባል፤
† ምግቡ ደግሞ ሣርና ቅጠል ብቻ ነው፤
† በየዕለቱ ያለ ማስታጐል ማዕጠንት ያሳርጋል፤
† ዘወትር በንጽሕና ቅዱስ ሥጋውን ይበላል፥ ክቡር ደሙን ይጠጣል፤
† በልቡ ውስጥ በፍጹም ቂምን፣ መከፋትን አያሳድርም፡፡
† የብረት ሰንሰለት በወገቡ ታጥቆ ይሰግዳል ይጸልያልም፡፡
"ጽድቅና ትሩፋት እንደ ሀብተ ማርያም" የተባለላቸው ታላቅ አባታችን ናቸው ፡፡
ዲቁናን ከጳጳሱ አቡነ ይስሐቅ ዘንድ ተቀበሎ ወደ በዓቱ ተመለሰ፡፡
ኋላ ቆይቶም እንደገና ከአቡነ ይስሐቅ ዘንድ ቅስናን ተቀበለ፡፡ ወደ ጓና ወደ ምትባል ሀገርም ሂዶ ተቀመጠ፡፡ ቀጥሎም ጐላጐት ወደ ምትባል አገር ሂዶ ተቀመጠ፡፡ የአፄ ናዖድ የንስሐ አባት ነበረና ንጉሡን ያስተምረውና ይገስጸውም ነበር፡፡
ጌታችንም ለጻድቁ የእሳትና የብርሃን ሠረገላን ሰጥቶት በዚያ እየበረረ ወደ ኢየሩሳሌምና ወደ ተለያዩ ቦታዎች ይሔድ ነበር፡፡ ከብዙ የተጋድሎ ዘመናት በኋላም የክብር ባለቤት መድኀኒታችን ክርስቶስ አእላፍ መላእክትን አስከተትሎ መጥቶ እንዲህ አላቸው::
"*ስለ እኔ ረሃብና ጥምን ስለ ታገስክ: *ስለ ምናኔሕ: *ስለ ተባረከ ምንኩስናህ: *ስለ ንጹሕ ድንግልናህ: *ቂምና በቀልን ስላለመያዝህ: *ስለ ንጹሕ ክህነትህና ማዕጠንትህ: *ቅዱስ ወንጌልን በፍቅር ስለ ማንበብህ 7 አክሊላትን እሰጥሃለሁ::"
"በሰማይም ከመጥምቁ ዮሐንስ ጐን: 500 የዕንቊ ምሰሶዎች ያሉበትን አዳራሽ ሰጥቼሃለሁ:: በስምህ የሚለምኑ: በቃል ኪዳንህ የሚማጸኑትንም ሁሉ እንድምርልህ 'አማንየ በርእስየ' ብዬሃለሁ" አላቸው::
+ቅዱሳን መላእክትም "ሀብተ ማርያም ወንድማችን" ሲሉ አቀፏቸው:: ጌታ ግን በዚያች ሰዓት አንድም ሦስትም ሆኖ ታያቸውና አቅፎ 3 ጊዜ ሳማቸው:: ከፍቅሩ ጽናትም የተነሳ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለየች:: መላእክትም ዝማሬም ወሰዷት::
ከተሰጣቸው ቃል ኪዳኖች ውስጥ አምስት መቅሰፍቶች የማስወገድ ሥልጣን ተሰጧቸዋል፡፡ እነርሱም፤
፩ኛ. #መብረቅ፣
፪ኛ. #ቸነፈር፣
፫ኛ. #ረሃብ፣
፬ኛ. #ወረርሽኝ፣
፭ኛ. #የእሳት ቃጠሎ ናቸው፡፡
በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ትዕዛዝ ቦታውን ሲባርክ ሦስት አጋንንት በጸሎቱ ሥልጣን የታሠሩለት ታላቅ ጻድቅ ነው፡፡
በግንቦት 26 ተወልዶ፤ በ1490 ዓ.ም. በወርኀ ኅዳር 26 ባረፈ ጊዜም፤ ካህናት በመልካም ልብስ ገንዘው በዝማሬ በማኅሌት ከቅዱስ አባታችን ከአቡነ ተክለሃይማኖት አጽም ጋር በደብረ ሊባኖስ ቀበሩት፡፡
(ከወርቅ ንፁህ ከብርም የጠራ ከሁሉ የሚበልጥ የተመረጠ ሃብተማርያም መልአክ ዘበምድር ነው መልካሙ ዜናው እስከ አጽናፍ ተሰማ፡፡)
ክብርት በሆነችው ጸሎቱና ምልጃው ይማርን ይጠብቀን፡፡
1.4K views04:25