2022-07-31 22:19:35
የሙሐረም ወር ቱሩፋት
ከአቡ ሁረይራ (ረዲዬሏሁ ዐንሁ) ረሱል (ሶለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም) እንድህ ማለታቸው ተላልፏል:-
«ከረመዳን በመቀጠል በላጭ የሆነው ፆም የአላህ ወር የሆነው የሙሐረም (ወር ፆም) ነው።
ከግደታ ሶላት በመቀጠል በላጭ የሆነው ሶላት የለይል ሶላት ነው።» [ሙስሊም]
➼ ይህ ሐዲሥ ከረመዳን ፆም በመቀጠል የሙሐረም ወር ፆም በላጭ እንደሆነ ግልፅ የሆነ መረጃ ነው።
➼ እንድሆም የሐዲሡ ግልፅ መልእክት የሙሐረምን ወር ሙሉ መፆምን ያመላክታል ነገር ግን ከፊል ዑለሞች ሁሉንም መፆም ሳይሆን ከሙሐረም ወር ብዙ ቀናቶችን በመፆም ማነሳሳት ነው በሐዲሡ የተፈለገው ብለዋል።
ኢብኑል ጀውዚይ (ረሒመሁሏህ) ለጧኢፉል መዐሪፍ ገጽ 39 ላይ የሚከተለውን አስፍረዋል:-
«ከሙሐረም ወር በማከታተል ከፆሙት መካከል ዑመር፣አቡ ጦልሐ፣ዓኢሻ እና ሌሎችም ይገኙበታል ኢብኑ ዑመር፣ሐሰኑል በስሪና ሌሎች ደግሞ የሙሐረም ወርን ሙሉውን ይፁሞ ነበር»
ማሳሰቢያ:- በዚህ ሐዲሥ የተፈለገው ከሙሐረም አስረኛውን (የዐሹራን) ቀን መፆም ሳይሆን ከሙሐረም ወር ሁሉንም ወይንም አብዘሀኛውን ቀነሰቶች መፆም ነው። ስለዐሹራ ፆም ሌላ እራሱን የቻለ ሐዲሥ አለ የአላህ ፍቃድ ከሆነ በሌላ ፅሑፍ እመለስበታለሁ።
➼ የሙሐረም ወር የሂጅራ አቆጣጠር የሚጀምርበት የአመቱ መጀመሪያ ወር ነው።
➼ የሙሐረም ወር አሏህ በቁርኣን ውስጥ ከጠቀሳቸው አራት የተከበሩ ወራቶች መካከል አንዱ ነው።
{ إِنَّ عِدَّةَ الشُّهُورِ عِندَ اللَّهِ اثْنَا عَشَرَ شَهْرًا فِي كِتَابِ اللَّهِ يَوْمَ خَلَقَ السَّمَاوَاتِ وَالْأَرْضَ مِنْهَا أَرْبَعَةٌ حُرُمٌ ۚ ذَٰلِكَ الدِّينُ الْقَيِّمُ ۚ فَلَا تَظْلِمُوا فِيهِنَّ أَنفُسَكُمْ ۚ }
«የወሮች ቁጥር አላህ ዘንድ በአላህ መጽሐፍ ውስጥ ሰማያትንና ምድርን በፈጠረበት ቀን ዐሥራ ሁለት ወር ነው፡፡ ከእነሱ አራቱ የተከበሩ ናቸው፡፡ ይህ ቀጥተኛው ሃይማኖት ነው፡፡ በእነርሱ ውስጥም ነፍሶቻችሁን አትበድሉ፡፡» [ተውባ (36)]
እነዚህን የተከበሩ አራት ወራቶች ረሱል (ሶለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም) በሚከተለው ሐዲሥ ጠቅሰዋቸዋል «… አመት አስራ ሁለት ወር ነው። ከእነሱ አራቱ የተከበሩ ናቸው:- ሶስቱ የተከታተሉ ናቸው ዙል ቂዕዳ፣ዙል ሒጃና ሙሐረም እና ረጀብ የሙደሮች ወር ያ በጁማዳ እና በሸዕባን መካከል ያለው…» [ቡኻሪና ሙስሊም]
➼ ረሱል (ሶለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም) ከላይ ባሳለፍ ነው ሐዲሥ የሙሐረምን ወር ወደ አላህ በማስጠጋት የአላህ ወር ብለው ጠርተውታል ይህ የዚህን ወር ደረጃ ትልቅነት የሚያሳይ ነው ምክኒያቱም ከፍጥረቶቹ ወደአላህ በመጠጋት የሚጠሩት ነገሮች ከፍጥረቶቹ ውስጥ ለየት ያለ ደረጃ ያላቸው ፍጥረቶች ናቸው። ለምሳሌ ከዕባን بيت الله የሷሊሕን ግመል ناقة الله በማለት በክብር ወደ እሱ እንዳስጠጋቸው እሄም ወር ከሌሎቹ ወር በመለየት ወደአላህ በማስጠጋት ረሱል (ሶለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም) ጠርተውታል።
➼ ከላይ በሳለፍነው የቁርአን አንቀፅ ውስጥ አሏህ «በእነርሱ(በእነዚህ በተከበሩ አራት ወራቶች) ውስጥም ነፍሶቻችሁን አትበድሉ፡፡» ይለናል :- ይህ ማለት
በእነዚህ በአራት ወራቶች ውስጥ ወንጀልን አትፈፅሙ ወንጀል በየትኛውም ወራት ሐራም ቢሆንም ግን በእነዚህ የተከበሩወራቶች የሚፈፀም ወንጀል ቅጣቶ በሌሎቹ ወራቶች ከሚፈፀሙ ወንጀሎች ከበድ ያለነው።
ታላቁ ሙፈሲር ኢማም ኢብኑ ከሢር እንድህይላሉ:-
« በማንኛውም ወራቶች በደልን መፈፀም ወንጀል ቢሆንም በሌሎች ወራቶች ከሚፈፀም በደል በበለጠ በተከበሩት ወራቶች የሚፈፀም በደል ሀጢአቱና ወንጅሎ የከበደ ነው።…» [ተፍሲር ኢብኑ ከሢር (4/89)]
➼ በዚህ በተከበረ ወር እራሳችንን ከሀራም አርቀን በቻልነው መልካም ስራ ለመስራት ቆርጠን እንነሳ በተለይ ከላይ ባሳለፍነው ሐዲሥ እንዳየነው በዚህ ወር ፆም ወደአላህ እጅግ የተወደደ መልካም ስራ ስለሆነ በቻልነው ያክል ለመፆም እንሞክር በጥቅሉ ነገ ሞት መጥቶ በእኛና በመልካም ስራ መካከል ሳይጋርደን በስተፊት ዛሬ በዱኒያ ላይ የተሰጠንን እድል መልካም ስራ በመስራት ሳያልፍ እንጠቀምበት
አላህ ሆይ የመልካም ስራ በሮችን ክፈትልን ወዳንተ የሚያቀርበንን መልካም ስራ በፈፀም ላይ አበርታን
ወንድማችሁ ኢብኑ ሙሐመድ ዘይን (ሙሐረም 01/1444)
•┈┈•┈┈•⊰✿◇✿⊱•┈┈•┈┈•
t.me/IbnuMuhammedzeyn
131 views19:19