Get Mystery Box with random crypto!

መሆን ይገባዋል፡፡ ለውጡ የመጣው የኢትዮጵያን ጥቅም ለማስከበር ብቻ መሆኑን የተረዱ፣ በተለይ በዓ | የጠ/ሚ ዶ/ር አብይ አህመድ እውነተኛ ደጋፊዎች

መሆን ይገባዋል፡፡

ለውጡ የመጣው የኢትዮጵያን ጥቅም ለማስከበር ብቻ መሆኑን የተረዱ፣ በተለይ በዓባይና በአፍሪካ ቀንድ ላይ ከፍተኛ ፍላጎት ያላቸው አካላት በቀጥታና በተዘዋዋሪ መንገዶች የጥፋት ናዳቸውን ሲጎርፉት ነበር። ታላላቅ የምዕራባውያን ሚዲያዎችና ተቋማትም የመንግሥቶቻቸውን ዐቅም ተማምነው በሀገራችን ላይ ዘምተዋል። ኢኮኖሚዋንና ዓለም አቀፍ ገጽታዋን ለማጥፋት የሚችሉትን ሁሉ ሲያደርጉ፣ ወዳጆቻችንን እንዲርቁን በእጅ አዙር ጠፍረው ለመያዝ ሲሞክሩ ነበር። ዳሩ ግን የእነሱ ጥረትና ሙከራ ያንቀላፋውን ኢትዮጵያዊ አንድነትና ቁጣ ቀሰቀሰው እንጂ አልጣለውም፡፡ የዐድዋ ድልም በእኛ ዘመን ተደገመ፤ ያንዣበበው ሀገር የመበታተን ጥቁር ደመናም ተገፈፈ። ይህም የኢትዮጵያ አምላክ ምንጊዜም ከእኛ ጋር መሆኑን ያየንበት የዘመናችን ትንግርት ነበር፡፡
ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ ኢትዮጵያ ላይ የወረደውን ዓይነት ዓለም አቀፍ ጫናና ተጽዕኖ ብዙ ሀገራት መቋቋም ተስኗቸው ፈራርሰዋል። የኢትዮጵያ አምላክ ግን ለጠላቶቻችን ንክሻ አሳልፎ አልሰጠንም፡፡
ተንገዳግደን እንድንቆም፣ ሸብርክ ብለን እንድንጸና፣ ደክመን እንድንበረታ ዐቅምና ብርታት ሆኖናል፡፡ ይሄው ዛሬም ኢትዮጵያ ዓለምን እያስደነቀችም እየታዘበችም ቀጥላለች፡፡ መጪውን ዘመን በዚህ ክንደ ብርቱ መከታዋ ላይ ሆና ለመሻገር በተስፋ አርቃ ትመለከታለች። በታሪክ የሰማነውን የኢትዮጵያን ጽናት በዓይናችን ላሳየን፤ በኛም ዘመን ታሪክ ለሠራልን፣ ለኢትዮጵያ ፈጣሪ ለኢትዮጵያ አምላክ ምስጋና ይድረሰው።
እንደ ኢትዮጵያ ያለ በዘመናት መካከል ካገጠሙት ችግሮች በላይ ቆሞ በልዕልና የሚያሸበርቅ ሀገር ማነው? የቋንቋ፣ የባህልና የሃይማኖት ብዝኃነትን ከአንድነት ጋር አገናዝበው ለረጅም ዘመን የዘለቁ ሀገራትስ ስንት ናቸው? በከርሰ ምድራቸውና በገጸ ምድራቸው ላይ በሀብት የተሞሉ፣ አየርና ውኃቸው የተባረከላቸው፣ የልብ ጀግንነትንና የአእምሮ ብሩህነትን በጥምረት የታደሉ፣ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ሀገራት ስንት ናቸው? ሁሉም ዓይነት የጥቁር ሕዝቦች መልክና ገጽታ እንደ ፈርጥ ተሠራጭተው የሚያብረቀርቁባት ሀገር ከኢትዮጵያ ሌላ ማናት? በነጻነትና በሉዓላዊነት የአፍሪካ ተምሳሌት የሆነችስ ሀገር ከኢትዮጵያ ሌላ ከወዴት ይገኛል? ከጥንት እስከ ዛሬ የሌሎች ሀገር ስደተኞችንና መጻተኞችን በሀገራቸው እንደራሳቸው ልጆች ያስተናገዱ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ሀገራትስ እነማን ናቸው?

የውስጥ ፈተናውንና የውጪ ጫናውን ተቋቍመው በዓለም የስፖርት መድረክ ላይ በድል ላይ ድል የሚቀዳጁ ኢትዮጵያውያን አይደሉምን በስፖርት አደባባይ የእናት ሀገራቸውን ሰንደቅ ከፍ አድርገው እያውለበለቡ፣ ድል ባደረጉበት ሜዳ ላይ እጆቻቸውን ወደ ሰማይ ዘርግተው ፈጣሪያቸውን የሚያመስግኑ ኢትዮጵያውያን አይደሉምን? በርጋታ ካሰብንና በጥሞና በረከታችንን ከቆጠርን፣ እኛ ኢትዮጵያውያን ከምሬት ይልቅ አመስጋኞች ልንሆንባቸው የሚገቡ እጅግ ብዙ ሌሎች ምክንያቶችና መንሥኤዎች አሉን። ለዚህም ነው ልቡናችን በተረዳቸውም ሆነ አስበን ባልደረስንባቸው ብዙ ጉዳዮች ላይ ቆመን ፈጣሪን ልናመስግንና ልናከብር የሚገባን።

የዛሬዎቹ የኢትዮጵያ ችግሮች የከፍታዋ መሰላሎችና የእመርታዋ ድልድዮች እንጂ የውድቀቷ መቃብሮችና የመደናቀፊያ መሰናክሎች አይሆኑም። እነዚህ ሁሉ የክፋት ኃይላት የሚረባረቡብን፣ መጪውን ብሩህ ዘመን አይተው እንጂ ተስፋ ቢስ ድሆች መሆናችን አስጨንቋቸው አይደለም፡፡ በወርቅ የተሞላ ቤት እንጂ ባዶ ቤት የጠላትን ልብ አይስብምና፡፡ ቢያንስ ለጠላቶቻችንና በጎአችንን ለማይመኙ አካላት የታያቸው ዐቅማችንና እንደ ሀገር ያለን ዕምቅ ሀብት ለእኛም ሊታየን ይገባል። ምክንያቱም ወደ ፊትና ወደ ከፍታ በፍጥነት የመውጫ መንገዱ አመስጋኝነትና ያለንን በጎ ነገር በአድናቆትና በክብር ለመቀበል መቻል ነው። ባለፈችበት ወጣ ገባ መንገድ ሁሉ ሀገራችንን ጠብቋታልና ቸር አምላክ ዛሬም ምስጋና ይግባው።

ከከርሰ ምድሩ እስከ ጠፈሩ፣ ከእምነቱ እስከ ታሪካዊ ሀብቱ፣ ከአየር ንብረቱ እስከ ባህል ብዝኃነቱ፣ ከጀግንነቱ እስከ ነጻነት ወዳድነቱ፣ ፈጣሪ የለገሠንን የተከማቸ ረቂቅ ብልጽግና በማሰብ እናመስግነው። እርስ በርስም ከመጠላላትና ከመጋጨት ወጥተን አንዳችን ሌላችንን ማድነቅና ማመስገን ባህላችን ይሁን፡፡ ባልፈውና በጎደለው እያማረርንና ብሶት እያወራን መጪውን ትውልድ አናድክመው። ይልቁንም አንዳችን ሌላችንን፤ የዛሬዎቹ የትናንቶቹን፣ እናመስግን፡፡ ከሁሉም በላይና በፊት ደግሞ በዘመናት መካከል የረዳንን ፈጣሪ ቆም ብለን እናመስግን። ወዳጆቻችን ሲለወጡ፣ አጋዦቻችን ፊታቸውን ሲያዞሩ፣ ጎረቤቶቻችን ባዳ ሲሆኑ አይተናል፡፡ የማይለወጠው የኢትዮጵያ ኃይል፣ ረድኤት፣ ጋሻና መከታ ፈጣሪ ብቻ ነው፡፡

በዓመቱ ካሉት 365 ቀናት አንዲቷን ቀን ምስጋናችንን በጋራ ለፈጣሪ ለማቅረብና ውለታውን ለማሰብ ብንወስን የሚበዛ አይመስለኝም፡፡ ከቀኑስ ለአንዲት ደቂቃ ያህል የምናደርገውን ሁሉ አስቀምጠን በያለንበት ቆም ብለን፣ የፈጣሪን ውለታና ቸርነቱን አስበን፣ የኢትዮጵያን አምላክ ማመስገን አለብን፡፡ መጪውን ዓመትና ዘመን በምሬትና በብሶት፣ በጥላቻና በቂም፣ በበቀልና በቁርሾ ከምንቀበለው ይልቅ፣ በአድናቆትና በምስጋና፣ በመረዳዳትና በይቅርታ ልንቀበለው ይገባል፡፡
የጽንፈ ዓለም ሁሉ ፈጣሪና የመልካምነት ሁሉ ምንጭ የሆነውን ፈጣሪ እንደ ሀገርና እንደ ሕዝብ፣ እንደ መሪና እንደ ዜጎች፣ በየቋንቋችንና በየእምነታችን ከልባችን እናመስግነው። ከክፉ ወረርሽኝ ጠብቆናል፣ ከአንበጣ መንጋ ታድጎናል፤ ድርቅ መቅሰፍት እንዳይሆን ከበር ቆሞልናል፤ ከቅርብና ከሩቅ የተነሣብንን የማፈራረስ አደጋ ቀልብሶልናል፤ የጀመርናቸውን ታላላቅ ፕሮጀክቶችና የታላቁን ግድብ የውኃ ሙሌት እውን እንዲሆን ረድቶናል፤ ሀገራችንና ሕዝባችንን ከጥንት እስከ ዛሬ ድረስ በምሥጢራዊ አሠራሩ ጠብቆልናል፡፡ ክብር ምስጋን ለእርሱ፣ ከዘላለም እስከ ዘላለም ይሁን ብለን፣ ለአንድ ደቂቃ በያለንበት ቆመን ለኢትዮጵያ አምላክ ምስጋና እንድናቀርብ ጥሪዬን አስተላልፋለሁ።

ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር!!
ፈጣሪ ኢትዮጵያና ሕዝቦቿን ይባርክ!
ሀምሌ 20 ቀን 2014 ዓ.ም.

የቴሌግራም ቻናል https://t.me/abdisira
የፌስ ቡክ ግሩኘ https://facebook.com/groups/1214264802267291/