2022-05-02 11:21:16
ሦስቱ ያባቴ ምክሮች (ከሞት ነጋዴው የተቀነጨበ)
***
ልጅ እያለሁ እጅግ በጣም ራስ ወዳድና ሁሉንም ነገር ለኔ ባይ ነበርኩኝ” አሉና ጀመሩ ጨዋታ ቢጤ... እኝህ ማናቸው የቻይናው ፕሬዝዳንት? ‘ሺ ጂንግ ፒንግ’ የሚሏቸው ሰውዬ። አልፎ አልፎ እንዲህ በል ሲላቸው በንግግራቸው መሀል ስላሳለፉት የልጅነት ጊዜ ያወራሉ። አሁንም ለግማሽ ክፍለ-ዘመን ወደኋላ በትዝታ ተመልሰው ልጅ ሳሉ የሰሯቸውን ተንኮሎች በዝምታ ሲያሰቡ ቆዩና ቀጠሉ ንግግራቸውን።
“ራስ ወዳድ ከመሆኔ የተነሳ ሁልጊዜም ጥሩ ጥሩውን ለራሴ ነበር የምወስደው። ይኽ ባሕሪዬ ቀስ በቀስ ጓደኛ እያሳጣኝ መጣ። በመጨረሻም ጓደኞቼ ሁሉ ሸሽተውኝ ጓደኛ አልባ ሆንኩ። እኔ ግን ጥፋቴ ምን እንደሆነ አልገባኝም ነበር። ጓደኞቼ ስለሸሹኝ ኮነንኳቸው እንጂ ምን እንዳጠፋሁ ራሴን አልጠየኩም። ችግር እንዳለባቸው አሰብኩ እንጂ ችግር እንዳለብኝ አልፈተሽኩም። ቢሆንም አባቴ ሕይወትን በመልካም መንገድ እንዴት መምራት እንደምችል በተግባር አስተማረኝ።
“የአባቴ የሕይወት ትምህርት ሦስት ደረጃዎች ነበሩት።
“አንድ ቀን አባቴ ለሁለታችን የሚሆን ምግብ አዘጋጀና በሁለት ሳህን ከፍሎ የምግብ ጠረጴዛ ላይ አስቀመጠው። የተዘጋጀው ምግብ ፓስታ በእንቁላል ነበር። አባቴ ፓስታውን ሲያስቀምጠው በአንደኛው ሳህን ከፓስታው በተጨማሪ የተቀቀለ አንድ እንቁላል ከአናቱ አድርጎበታል። በሌላኛው ሳህን ግን ከፓስታው በላይ እንቁላል የሚባል ነገር የለበትም። ከዚያ አባቴ ወደ እኔ እየተመለከተ፣
“ልጄ! የትኛውን ትፈልጋለህ? አንዱን ሳህን ምረጥና አንሳ...” አለኝ።
በጊዜው፣ እንቁላል እንዲህ በቀላሉ የሚገኝ ምግብ አልነበረም። ድህነቱ፣ ገንዘብ ማጣቱ በሁላችንም ቤት ጫን ያለ ስለነበረ አዲስ ዓመት ካልመጣ ወይም ዓመትባል ካልደረሰ በቀር እንቁላል መብላት ዘበት ነው። ታዲያ እኔ፣ አንዱን ሳህን መርጬ እንድወስድ አባቴ ሲጠይቀኝ ፈጥኜ እንቁላል ያለበትን ሳህን መረጥኩ። እንዴ ማን ይሞኛል? እንቁላል ተገኝቶ ነው? በሰዓቱ እንቁላል ያለበትን ሳህን ሳነሳ ቅንጣት ታህል አላመነታሁም ነበር። ደስ እያለኝ ፓስታ በእንቁላሌን መብላት ጀመርኩ።
አባቴ ሁለተኛውን ሳህን አንስቶ መመገብ ሲጀምር ግን ዐይኔን ማመን አቃተኝ። አባቴ ከሚበላበት ሳህን ውስጥ ሁለት የተቀቀሉ እንቁላሎች በፓስታው ተሸፍነው ኖሯል። አቤት አንዴት እንደተናደድኩ! ቆጨኝ በጣም! ቸኩዬ በመወሰኔ ራሴን ወቀስኩት። ምናልባትም በሕይወት ዘመኔ እንደዚያ ቀን የተበሳጨሁበት ጊዜ ያለ አይመስለኝም። ይኼን ጊዜ አባቴ እየሳቀ፣
“የእኔ ልጅ… ዐይኖችህ የሚያዩት ነገር ሁሉ እውነት እንዳልሆኑ መቼም እንዳትረሳ! ደግሞ በሰዎች ላይ ብልጣብልጥ ለመሆን ስትሞክር ትጎዳለህ!!” አለኝ።
በሌላ ቀን አባቴ በተመሳሳይ ምግብ አዘጋጅቶ ሲያበቃ እንደተለመደው ፓስታውን በሁለት ሳህን አቀረበው። አንደኛው ሳህን አናት ላይ አንድ የተቀቀለ እንቁላል አስቀምጦበታል። ሌላኛው ላይ ግን ካናቱ ምንም እንቁላል አላደረገበትም። ከዚያ እንደተለመደው አባቴ ወደ ምግብ ጠረጴዛው እየጠቆመ፣
“በላ ልጄ! ምረጥና የምትፈልገውን ሳህን ውሰድ..እየጠቆመ፣
ካለፈው ሥህተቴ በመማር በጥንቃቄ መምረጥ እንዳለብኝ አሰብኩና ቀልጠፍ ብዬ ካናቱ እንቁላል የተደረገበትን ትቼ ሌላኛውን መረጥኩ። ከዚያ በፍጥነት ፓስታውን ገላለጥኩና ሳህኑን ዐየሁት። በጣም ደነገጥኩ! ሳህኑ ውስጥ አንድም እንቁላል የሚባል ነገር የለውም። አባቴ በድጋሚ እየሳቀ፣
“ልጄ… ሁልጊዜ በልምድህ ላይ ብቻ የምትተማመን ከሆነ ትከስራለህ። አንዳንዴ ሕይወት ራሷ ልታሞኝህ ወይም ቁማር ልትጫወትብህ ትችላለች። ዳሩ ግን በዚህ ብዙ ልታዝን ወይም ልትቆጣ አይገባም… ትምህርት እንደሚሆንህ ቆጥረህ ብቻ እለፈው። እንዲህ ያለውን እውቀትየተቀቀለው መጽሐፍት ላታገኝ እንደምትችል አስታውስ!!” ብሎኝ፣ ያቺ ቀን አለፈች።
ለሦስተኛ ጊዜ አባቴ ምግብ አዘጋጀ። እንደተለመደው ፓስታና እንቁላሉ በሁለት ሳህኖች ቀርቧል። ባንዱ ሳህን የተቀቀለው እንቁላል ከፓስታው በላይ ተቀምጧል። በሌላኛው ሳህን ደግሞ ፓስታ ብቻ። እንግዲህ የውስጡን አላውቅም… ከላይ ግን እንቁላል የለውም። አባቴ የተለመደ ጥያቄውን አቀረበልኝ። ወደ ምግብ ጠረጴዛው በአገጩ እየጠቆመ፣
“ልጄ ምን ትጠብቃለህ? ምረጣ!! የትኛው ሳህን ይሁንልህ?” አለኝ።
አሁን እኔ ከሁለቱ ሥህተቶቼ በደንብ ትምህርት አግኝቻለሁ።
“አባቴ አንተ የቤቱ አባወራ ነህ! ለቤተሰባችን ሰርክ የምትለፋ፣ ደከመኝ ሳትል ቀን-ከሌት እኛ እንዳይርበን የምትሠራ አባት ነህ። መጀመሪያ መብላት ያለብህ አንተ ነህ… ለስኩለት። ስለዚህ ቅድሚያ አንተ አንሳ…” ስል መለስኩለት።
አባቴ በጭራሽ አላቅማማም። ከአናቱ እንቁላል የተቀመጠበትን ሳህን አንስቶ መብላት ጀመረ። እኔም ሁለተኛውን ሳህን አንስቼ ፓስታዬን ለመብላት አቀረቀርኩ። እርግጠኛ ነበርኩ፣ ሳህኑ ውስጥ እንቁላል እንደማይኖር። ከፓስታው በታች ሁለት እንቁላሎችን ሳገኝ ግን ዐይኔን ማመን አልቻልኩም። ቀና ብዬ ሳየው አባቴ ፈገግ ብሎ በፍቅር ዐይኑ እያስተዋለኝ ነበር። ከዚያም እንዲህ ሲል መከረኝ፣
“የኔ ውድ ልጅ! ለሌሎች ሰዎች መልካም መልካሙን ስታደርግ ተፈጥሮ ራሷ መልካም መልካሙን ወደ አንተ ታመጣለች! ይኼንን መቼም እንዳትዘነጋ!!” አለኝ።
ከዚያን ጊዜ በፊትም ሆነ ከዚያን ጊዜ በኋላ አባቴ ብዙ ጊዜ መክሮኛል! ገስፆኛል! ገርፎኛል! አብዛኞቹን ማስታወሴን እጠራጠራለሁ። ነገር ግን እነዚህን ሦስት ምክሮቹን በፍጹም አልረሳቸውም! እስክሞትም ድረስ የምረሳቸው አይመስለኝም። እነሆ ሕይወቴም በዚህ ምክንያት የተስተካከለ ሆኗል። ከአባቴ ምክር በኋላ ስኬት መንገዷን ወደእኔ አድርጋለች።
መልካም ቀን
ከተመቻችሁ ፔጁን ላይክ &ሼር በማድረግ ያጋሩ ።
297 views08:21