✞ እንኩዋን ለታላቁ ሊቅ "ቅዱስ ያሬድ" ዓመታዊ የልደት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞ ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ቅዱስ ያሬድ :- ከእግዚአብሔር ያገኘነው አባታችን : ክብራችን : ሞገሳችን ነውና በምን እንመስለዋለን? አንደበቱ ጣፋጭ [ጥዑም] : ልቡናው የቅድስና ማሕደር : ሕሊናው የምሥጢራት ሠረገላ ነው:: እስከ አርያም ተነጥቆ የማይፈጸም ምሥጢርን የተመገበ ማን እንደርሱ! ሊቀ ሊቃውንት እዝራ ሐዲስ እንደሚሉት :- "ቅዱስ ያሬድ ለኢትዮዽያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከራስ ጸጉሯ እስከ እግር ጥፍሯ: ሙሉ አካሏ ነው" የሊቁ ዜና ሕይወት በጥቂቱ :- ቅዱስ ያሬድ የተወለደው በ፭፻፭ [505] ዓ/ም አክሱም አካባቢ ሲሆን እናቱ ክርስቲና [ታኡክልያ] አባቱ ደግሞ ይስሐቅ [አብድዩ] ይባላሉ:: ሊቁ በሕጻንነቱ ምሥጢር [ትምሕርት] አልገባው ብሎ ይቸገር ነበር:: ትምሕርት እንቢ ያለው ሰነፍ ስለ ነበር አይደለም:: በጥበበ እግዚአብሔር እንጂ:: ምን ትምሕርት ባይገባው ጾምና ጸሎትን ያዘወትር ነበር:: ልቡናው ደግሞ በእመቤታችንና በልጇ ፍቅር የታሠረ ነበር:: አንድ ቀን ግን መምሕሩ የነገሩት ቀለም አልያዝሕ አለው:: ሲፈትኑትም ባለመመለሱ ተገረፈ:: ዱላው በጣም ስለ ተሰማው ቅዱሱ ከመምሕሩ ኮብልሎ ማይ ኪራሕ አካባቢ ሲደርስ ደክሞት አርፎ እግዚአብሔር ትጋትንና ተስፋ አለመቁረጥን ከትል አስተማረው:: ትሏ ፮ [6] ጊዜ ወድቃ በ፯ [7] ኛው ፍሬዋን ስትበላት ተመልክቷልና:: ከዚህ በሁዋላ ቅዱስ ያሬድ ወደ መምሕሩ ተመልሶ: ይቅርታ ጠይቆ ትምሕርት ጀመረ:: ሊቁም ትጋትንና ጸሎትን ከሰጊድ ጋር አበዛ:: እግዚአብሔር ደግሞ በድንግል እናቱ አማካኝነት የምሥጢር ጽዋን አጠጣው:: ካህኑ ያሬድ እንዲያ አልገባህ ያለው ምስጢር ተገልጦለት በጥቂት ጊዜ ብሉይ ከሐዲስ ወሰነ:: በምሥጢር ባሕርም ይዋኝ ጀመር:: ያን ጊዜ ሰማያዊ ዜማ አልተገለጠም ነበርና በጸሎት ላይ ሳለ ተደሞ መጣበት:: ፫ [3] መላእክት በወፎች አምሳል መጥተው አነጋገሩት:: ድንገትም ነጥቀው ወደ ሰማያት: ወደ ልዑላኑ መላእክት ዘንድ አደረሱት:: ሊቁ በሰማያት ልዩ ምሥጢር: ልዩ ምስጋናና ልዩ ዜማን አዳመጠ:: ይሕንን ምስጋና ብዙ ቅዱሳን ቢሰሙትም ቅዱስ ያሬድ ግን ይዞት እንዲወርድ ተፈቀደለት:: ሊቁ ወደ ምድር ተመልሶ በታላቅ ተመስጦ አክሱም ጽዮን ውስጥ በሃሌታ አመሰገነ:: ሕዝቡና ንጉሡም ከጣዕሙ የተነሳ አደነቁ:: ቅዱስ ያሬድ ለተወሰነ ጊዜ በአክሱምና ደብረ ዳሞ ሲያገለግል ቆይቶ: ከመሬት ክንድ ከስንዝር ከፍ ብሎ ለእመቤታችን አንቀጸ ብርሃንን ደርሶላት ከሃገሩ ወጣ:: ቅዱስ ያሬድ በቀሪ የሕይወቱ ዘመናት :- ፩. ፭ "5" ያሕል መጻሕፍትን ጽፏል:: ፪. በጣና ቂርቆስ: በዙር አባና በሌሎችም ቦታዎች ወንበር ዘርግቶ ብዙ ደቀ መዛሙርትን አፍርቷል:: ፫. በሰሜን ተራሮች አካባቢ በትጋሃ መላእክትና በተባሕትዎ ኑሯል:: በ፭፻፸፮ [576] ዓ/ም በተወለደ በ፸፩ [71] ዓመቱ ተሰውሯል:: አባቶቻችን :- - ጥዑመ ልሳን - ንሕብ - ሊቀ ሊቃውንት - የሱራፌል አምሳያ - የቤተ ክርስቲያን እንዚራ - ካህነ ስብሐት - መዘምር ዘበድርሳን - ማኅሌታይ - ልዑለ ስብከት እያሉ ይጠሩታል:: የቅዱሱ ጸሎትና በረከት ሃገራችንን ከክፉው ሁሉ ይጠብቅልን:: " እንዲህ ያለው ሰው ከአሥራ አራት ዓመት በፊት እስከ ሦስተኛው ሰማይ ድረስ ተነጠቀ:: እንዲህ ያለውንም ሰው አውቃለሁ:: በሥጋ እንደ ሆነ ወይም ያለ ሥጋ እንደሆነ አላውቅም:: እግዚአብሔር ያውቃል:: ወደ ገነት ተነጠቀ:: ሰውም ሊናገር የማይገባውን: የማይነገረውን ቃል ሰማ::" [፪ቆሮ.፲፪፥፪-፭] (12:2-5) † ወስብሐት ለእግዚአብሔር † [ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ] 165 viewsHaile Desalegn, 13:34