2021-10-17 20:21:47
From D.MEHRET DEBEBE
የራስህን ሩጫ ሩጥ
ሚዳቋ በጠዋት ተነስታ ለግጦሽ ትሰማራለች፡፡ በዕለቱ ሊበላት ከሚፈልግ አንድ አንበሳ በፈጠነ ሁኔታ ካልሮጠች ተበልታ አንደምትሞት ታውቀዋለች፡፡ አንበሳም ቢሆን በራሱ በጠዋት ተነስቶ ለአደን ይሰማራል፡፡ የእለቱ ራት እንዳያደርጋት ሚዳቆዋ ስትሮጥ አንበሳው ከእሷ በፈጠነ ሁኔታ ሮጦ ካልደረሰባትና ካልያዛት በረሃብ እንደሚሞት ያውቀዋል፡፡
ሚዳቋዋ ራሷን በንቃት በመጠበቅ አንበሳው ሊበላት ሲመጣ ከእርሱ በፈጠነ ሁኔታ ሮጣ ከማምለጥ ይልቅ፣ “ፈጣሪ ለምን በሰላም እንዳልኖር አንበሳ የሚባል ፈጠረ . . . አንበሶች ግን ምን አይነት ክፉዎች ናቸው? ምናለበት ቢተውንና አርፈን ብንኖርበት . . . ሌሎች ሚዳቆ ዘመዶቼ ግን እንዴት ጨካኞች ናቸው ገና አንበሳ ሲመጣ ለማንም ግድ ሳይሰጣቸው ሮጦ ማምለጥ ነው ትዝ የሚላቸው . . .” እያለች ቆማ ብትነጫነጭ በአንበሳው ከመበላት አታመልጥም፡፡
አንበሳም በበኩሉ የቻለውን ያህል ሮጦ ሚዳቆዋን አባሮ ከመብላት ይልቅ፣ “ፈጣሪ እንደዚህ ከምለፋ ምናለበት እየረጋገጥኩት የማልፈውን ይህንን ሳር-በሊታ አድረጎ ቢፈጥረኝ . . . ሚዳቆዎች ግን ምን አይነቶ ናቸው? እነሱ የትም የምይንቀሳቀስ ሳር እየበሉ፣ እኛን ግን ያሯሩጡናል . . . አንበሳ ዘመዶቼን ግን ታዘብኳቸው፣ ለራሳቸው ተሯሩጠው አድኖ ከመብላት ውጪ ለሌላው አንበሳ ረሃብ ትዝም አይላቸው . . .” እያለ ሲነጫነጭ ቢውል በረሃብ ከመሞት አያመልጥም፡፡
አንዳንድ ሰዎች ማን ምን እንዳደረገላቸውና እንዳላደረገላቸው . . . ማን ምን እንዳደረገባቸውና እንላደረገባቸው . . . ይህቺ አለም ምን ያህል ፍትህ እንዳልሆነች . . . ሁሉም ሰው የራሱ ጉዳይ ብቻ ግድ እንደሚለው . . . እና የመሳሰሉትን ሲያሰላስሉና ሲያወሩ መኖር እንደሚያስቀድም፣ ወደኋላ እንደሚያስቀርና አንዳንዴም እንደሚያስበላ ከገባቸው ቆይተዋል፡፡ ስለዚህም የራሳቸው ሩጫ ላይ ያተኩራሉ፡፡
እንደዚህ አይነት ሰዎች የዚህች አለም ጉዳይ በደንብ የገባቸው ሰዎች ናቸው፡፡ እነሱ ካልሮጡ ማንም እንደማይሮጥላቸው፣ እነሱ ካልሰሩ ማንም እንደማይሰራላቸው፣ እነሱ ቀዳዳቸውን ካልደፈኑ ማንም እንደማይደፍንላቸው . . . በሚገባ ያውቁታል፡፡ በዙሪያቸው ያለው አለም ፍትህ-ጎደል የመሆኑን ጉዳይ በሚገባ ቢያውቁትም፣ የራሳቸውንና የቤተሰባቸውን ቀዳዳ የመድፈን ሙሉ ሃላፊነቱ የራሳቸው እንደሆነ በሚገባ ያውቁታል፡፡ ስለሆነም፣ በዙሪያቸው ያለው ፍትህ-ጎደል ሂደት ቢታወሳቸውም የራሳቸውን ሩጫ ከመሮጥ አይገታቸውም፡፡
ምንም ያህል ብትጠይቅ አንዳንዴ የማይመለሰ ጥያቄ ሊኖርህ እንደሚችል ይግባህ፡፡ ምንም ያህል ብትጮህ አንዳንድ ጊዜ ማንም የማይሰማው ጩኸት እንዳለህ ተገንዘብ፡፡ ምንም ያህል ቆመህ ብትጠብቅ አንዳንዴ ማንም ሰው ሊደርስልህ የማይችልበት (ወይም የማይፈልግበት) ሁኔታ እንዳለ ተረዳ፡፡ ጨዋው ሰው የራሱን ጣጣ ከጨረሰ በኋላ ወደ አንተ ዘወር ሲል ጊዜው ያልፋል፡፡ ሌላው ደግሞ ለማንም ደንታ የማይሰጠው አይነት ስለሆነ ትዝም አትለውም፡፡
ያለህ አስተማማኝ መንገድ ጠዋት ተነስተህ ልክ እንደሚዳቆዋ ሊይዝህ ከሚፈለግ ሁኔታ ለማምለጥ፣ ልክ እንደ አንበሳው ደግሞ መያዝ የሚገባህን ለመያዝ መሮጥ ነው፡፡
መልካም ምሽት
ሼር
@tebasemidea
@tebasemidea
419 views ☞net, 17:21