2021-12-08 08:53:55
የማንነትህ መለኪያ ተቀባይነት አይደለም
“የብዙ ሰዎች ተቀባይነት የማጣት ፍርሃታቸው ምንጩ በሰዎች ለመወደድ ያላቸው ጥማት ነው፡፡ ሰዎች በአንተ ላይ ካላቸው አመለካከት ተነስተህ የማንነትህን ተመን አታውጣ” - Harvey Mackay
የምንኖርባት አለም በእነሱ ተቀባይነትን እንድናገኝ የግድ እነሱን ማስደሰት እንዳለብን ግፊትና ተጽእኖ የሚያሳድሩብን ሰዎች የሞሉበት አለም ነች፡፡ ስለዚህም፣ ሳናስበውም የስሜታችንን ከፍታና ዝቅታ የሚወስነው ሰዎች በእኛ ላይ ያላቸው አመለካከት ስለሚሆን፣ እኛ መኖራችንን እናቆምና የሰዎች አመለካከት በእኛ ውስጥ መኖር ይጀምራል፡፡
ማንነታቸውን በሰዎች ባላቸው ተቀባይነት ላይ የመሰረቱ ሰዎች ያላቸው አመለካከት የሚከተለው ነው፡- “የማንነቴን ዋጋ ለማወቅ ሰዎች እንዲቀበሉኝ የማደርገውን የግል ጥረቴንና በሰዎች ያለኝን ተቀባይነት መደመር ነው” (ጥረት + የሌሎች አመለካከት = ማንነት)፡፡ የዚህ የተዛባ ስሌት ችግር ተቀባይነት የማጣትና የመገፋት ስሜት ነው፡፡ “ሰዎች ስለ እኔ ምን ያስቡ ይሆን? ሰዎች እኔ በሌለሁበት ምን ያወሩ ይሆን? ሰዎች ካልተቀበሉኝ፣ ካልወደዱኝና ካላቀረቡኝ ምን ይውጠኝ ይሆን? ይህኛው ነገርና ያኛው ነገር ቢኖረኝ ኖሮ ልክ እንደ እገሌ ሁሉም ሰው የሚቀበለኝ ሰው እሆን ይሆን? እነሱ የሚያደርጉትን ነገር ባደርግ ይቀበሉኝ ይሆን? ሰዎች የማይቀበሉኝ ማንነቴ ላይ ችግር ስላለብኝ ይሆን? … ” አእምሮ የሚያዞረው ጥያቄ ማለቂያ የለውም፡፡
የሚከተሉትን የተቀባይነት እውነታዎች አትዘንጋቸው፡-
ሁሉም ሰው ሊቀበልህ አይችልም
ከሁሉ በፊት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ልትቀበለው የሚገባህ እውነታ፣ ሁሉም ሰው ካለምንም ቅድመ-ሁኔታ፣ እንዲሁም ሙሉ ለሙሉ ሊቀበልህ የሚችልበት ጊዜ ሊመጣ እንደማይችል ነው፡፡ ይህንን እውነታ አምኖ መቀበል ይህ ነው የማይባልን መረጋጋት በውስጥህ እንደሚፈጥርልህ አትጠራጠር፡፡ በተጨማሪም፣ ይህንን እውነታ አምኖ መቀበል ሰዎች አንተን የመቀበልና ያለመቀበል መብት እንዳላቸውና ያንንም መብት ልትሰጣቸው እንዲሚገባህ አምነህ እንድትቀበል ውስጥህን ያሳምነዋል፡፡
በሚቀበሉህ ላይ አተኩር
ሁሉም ሰው ካለምንም ቅድመ-ሁኔታ ሙሉ ለሙሉ ሊቀበልህ እንደማይችል አምነህ ከተቀበልክ በኋላ በመቀጠል የሚገፉህንና የማቀበሉህን ሰዎች ሁኔታ ተወት በማድረግ የሚቀበሉህና አንተን ማግኘት የሚፈልጉት ላይ ማተኮር ይገባሃል፡፡ የማይፈልጉህንና የሚሸሹህን ስትከታተል የሚፈልጉህንና ለአንተ ግድ የሚላቸውን ሰዎች እንዳታጣ ልታስብበት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ በማይቀበሉህ ሰዎች ላይ ማተኮር ለድርብ-ክስረት የሚያጋልጥህ ጉዳይ ነው - የሚወዱህን ሰዎች ከማጣትና ከስሜት ቀውስ የሚመጣ ክስረት፡፡
በሰዎች አመለካከት ላይ አትደገፍ
ሰው ተለዋዋጭ ፍጥረት ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች እንዲሁ የወረተኝነትና በአንድ ሃሳብ ያለመጽናት ዝንባሌ እንዳላቸው ጥያቄ የለውም፡፡ አንዳንድ ሰዎች ግን ተለዋዋጭ የሚሆኑት ክፉና ወረተኛ ስለሆኑ ላይሆን ይችላል፡፡ የወቅቱ እውነታ፣ የሚለዋወጠው ሁኔታቸውና እይታቸው፣ እንዲሁም ሌሎች ከቁጥጥራቸው ውጪ የሆኑ ጉዳዮች በላያቸው ላይ ስለሚለዋወጡ እነሱም ከመለወጥ ውጪ ምርጫ እንዳይኖራቸው ይገደዳሉ፡፡ ስለሆነም፣ ዛሬ የደገፈህና አብሮህ የሆነ ሰው ነገ ከአቅሙ በላይ በሆነ ምክንያት ሊለወጥ ስለሚችል ይህንን ሊለወጥ የሚችል የሰው ሁኔታ ተስፋ በማድረግ የማንነትህን ዋጋ ከዚያ ጋር ማያያዝ የስህተት ሁሉ ስህተት ነው፡፡
ለውንድም ለእህቶቻቹህ #ሼር (share) ያድርጉላቸው፡፡https://t.me/PropheticMovementET
11.0K viewsView, edited 05:53