Get Mystery Box with random crypto!

​​ኅዳር 27 ቅዱስ ጢሞቴዎስ ሰማዕት በዚህችም ቀን በንሑር ከሚባል አገር ቅዱስ ጢሞቴዎስ በሰማዕ | ዝማሬ ዳዊት - Zimare Dawit

​​ኅዳር 27
ቅዱስ ጢሞቴዎስ ሰማዕት


በዚህችም ቀን በንሑር ከሚባል አገር ቅዱስ ጢሞቴዎስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ እግዚአብሔርን የሚፈራ ሁልጊዜ በጾም በጸሎት ተጠምዶ የሚኖር ነው ስሟ ሞራ የሚባል ሚስት አለችው እርሷም የአጎቱ ልጅ ናት በሥራዋ ሁሉ ደስ የምታሰኘው መልካም ሴት ናት።

እንደዚህም በፍቅርና በስምምነት ሲኖር ከከሀዲ ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ ዘንድ የጣዖታት ቤቶች ይከፈቱ ዘንድ አብያተ ክርስቲያናት እንዲዘጉ ትእዛዝ ወጣ። ቅዱስ ጢሞቴዎስም ይህን ሰምቶ እጅግ ደስ አለው። እርሱ ስለ ክርስቶስ ፍቅር ደሙን ያፈስ ዘንድ ይህን ዘመን ይጠብቀው ነበርና ለሚስቱም ሊሠራው ያሰበውን ነገራት እርሷም የእግዚአብሔር ፈቃድ ይሁን አለች።

ከዚህም በኋላ መንገዱን ያቀናለት ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ጌታችንም በዚያች ሌሊት በሕልሙ ተገልጾለት ወዳጄ ጢሞቴዎስ ሆይ ሰላም ላንተ ይሁን እነሆ ከጻድቃኖቼ ቁጥር ውስጥ ቆጥሬሃለሁ አሁንም ተነሣ ሚስትህንም ይዘህ ወደ ብህንሳ ከተማ ሒዳችሁ ጣዖታትን በሚያመልኩ ሁሉ ሕዝብ ፊት በስሜ ታመኑ አለው። በነቃ ጊዜም ለሚስቱ ነገራት እርሷም ይህንኑ የሚመስል ሕልሟን ነገረችው።

ከዚህም በኋላ ተነሥተው በአንድነት ሔዱ ወደ መኰንኑ ወደ ቊልቊልያኖስም ደረሱ መሰንቆና እንዚራ እያስመታ ለጣዖታቱ በዓልን ሲያከብር አገኙት ያንጊዜ ወታደሮቹ ይዘው በመኰንኑ ፊት አቆሙት ሚስቱም ተከተለችው መኰንኑም ለጣዖት መስገድን እያግባባ በርኅራኄ ቃል ተናገረው ቅዱሱ ግን እርሱንና የረከሰች ሃይማኖቱን ሰደበ ስለዚህም መኰንኑ ተቆጥቶ ከሚስቱ ጋር ወደ ወህኒ ቤት እንዲአስገቡት አዘዘ።

ከጥቂት ቀኖች በኋላም ከሚስቱ ጋር አውጥተው ደማቸው እንደ ውኃ እስቲፈስ በአለንጋዎች እንዲገረፉአቸው አዘዘ ያለ ርኅራኄም ገረፏቸው ሚስቱም በዚህ ሥቃይ ምስክርነቷን ፈጸመች።

ዳግመኛም ለጣዖታት መስገድን እሺ ይለው ዘንድ ቅዱስ ጢሞቴዎስን ማባበል ጀመረ እምቢ ባለውም ጊዜ የነዳጅ ድፍድፍ ሥጋውን ቀብተው ከእሳት ማንደጃ ውስጥ እንዲጨምሩት አዘዘ በጨመሩትም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ወርዶ ከዚህ ቃጠሎ አዳነው ።

ከዚህም በኋላ ሁለተኛ ወደ ወህኒ ቤት መለሱት ተአምራትንም የሚያደርግ ሆነ በአንዲት ዕለትም በዚያ ሲጸልይ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደርሱ መጥቶ ቃል ኪዳንን ገባለት ሰላምታንም ሰጠው።

በማግሥቱም ከእሥር ቤት አውጥተው ወደ በንሑር ከተማ ወስደው ቅድስት ራሱን ቆረጡ ያን ጊዜ ንውጽውጽታ ሆነ አየርም መላእክትን ተመላች አማንያን ሰዎችም መጥተው ሥጋውን ወስደው በመልካም አገናነዝ ገንዘው ቀበሩት። የመከራውም ዘመን በአለፈ ጊዜ ቤተ ክርስቲያን ሠሩለት ሰኔ ሃያ ሰባት ቀንም አከበርዋት ሥጋውንም በውስጥዋ አኖሩ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

ለሁሉም ኦርቶዶክሳዊ ሼር አድርጉ
@ortodoxmezmur
@ortodoxmezmur
@ortodoxmezmur