Get Mystery Box with random crypto!

«የማህበረ ቅዱሳንና የሞዐ ተዋሕዶ ዲያቆናት ፣አባላትና ደጋፊዎች የመጅሊስ የበላይ ጠባቂ ሆኑ እንዴ | Mereb: መረብ

«የማህበረ ቅዱሳንና የሞዐ ተዋሕዶ ዲያቆናት ፣አባላትና ደጋፊዎች የመጅሊስ የበላይ ጠባቂ ሆኑ እንዴ? ወይስ ሳናውቀው መጅሊስ ለነርሱ ተላልፎ ተሸጠ ወይ?» ብለህ ልትገረም ሁሉ ትችላለህ።



አንድ ነገር «ሕጋዊ» ወይም «ሕገ ወጥ» ለመባል ጉዳዩ ተመዝኖበት ይህ አቋም የተያዘበት ሕግ ሊኖር ግድ ይላል። መመዘኛው ሕግ (ሕግ፣ ደንብ፣ መመሪያ ወዘተ) ከሌለ አንድ ነገር በባዶ «ሕገ ወጥ» ሊባል አይችልም። እንዲሁ አንድ ተግባር ላይ ያለአንዳች ማስረጃ «ሕገ ወጥ» የሚል ስያሜ ብቻ በመለጠፍ እንድትቀበል የሚገፋፋ አካል ካለ ያ አካል «ሕገ ወጥ» ወይም «ሕጋዊ» እያለ ያለው ከግለሰባዊ ፍላጎቱ ተነስቶ ነው ማለት ነው። የተጣሰ ሕግ ሳይሆን «ሕገ ወጥ» ብሎ መፈረጅ ራሱ ሕገ ወጥ ነው።

በየትኛውም ደረጃ ያለ ግለሰብ ፍላጎቱን ወይም አቋሙን እርሱ «ሕገ ወጥ» ብሎ ስለፈረጀ ብቻ ሕገ ወጥ እንዲሆንለት የሚሻ ከሆነ ያ አካል ስለሕግ ደንታ የሌለው፣ በሕግ ቃላት ሽፋን ፊውዳላዊ አሠራሩን እውን ለማድረግ እየተጋ ያለ አካል ነው ማለት ነው። የእርሱንም ንግግር እንዳለ ተቀብለው አብረው «ሕገ ወጥ» የሚሉ ሰዎች፣ የመንግስት አካላትም ሆነ ሚዲያዎች ካሉ ለህግና ተቋማዊ አሰራር ደንታ የሌላቸው፣ ወይም የግለሰቡ አቋም ከእነርሱ ፍላጎት ጋር ስለገጠመ ብቻ የሚናገሩ መሆናቸውን መረዳት አይከብድም።

ስለአንድ ተቋም እውቀቱና መረጃው የሌለው ማንኛውም አካል አቋም ከመያዙ በፊት ስለጉዳዩ ተቋማዊ ሕጉንና ደንቡን፣ የስልጣን ተዋረዱንና በሕግ የመወሰን መብት ከተሰጣቸው አካላት መካከል የብዙኃኑ አቋምና ውሳኔ ምን እንደሆነ ማየት ይገባል። በመጅሊስም ጉዳይ መሆን ያለበት ይኸው ነው።

መጅሊስ ጠቅላላ ጉባኤ፣ ሥራ አስፈጻሚና መሪ አለው። ከመሪው ይልቅ ሥራ አስፈጻሚዎች፣ ከሥራ አስፈጻሚዎች ደግሞ ጠቅላላ ጉባኤው ሥልጣናቸው ከፍተኛ ነው። ከጠቅላላ ጉባኤው ደግሞ ብዙሃኑ የደገፉት ሀሳብ ከተቃረኑት በተሻለ ተቀባይነት አለው። በግልጽ አነጋገር ከመጅሊስ መሪ ሐጂ ዑመር እድሪስ ይልቅ ሥራ አስፈጻሚዎች፣ ከሥራ አስፈጻሚዎቹ ይልቅ ደግሞ የጠቅላላ ጉባኤው የበለጠ ስልጣን አላቸው።

ይህን ሳያከብሩ ሐጂ ዑመር አሁን እያደረጉ እንዳሉት ከጠቅላላ ጉባኤው አብላጫ ድምጽ «በላይ ነኝ» ወይም በሥልጣን የሚበልጣቸውን «የጠቅላላ ጉባኤ ውሳኔ ሕገወጥ ነው። ሕጋዊው እኔ ነኝ» ሲሉ «በየትኛው ሕግ?» ብለህ ብትጠይቅ የሚያቀርቡት መረጃ የላቸውም። ያላቸው «የእገሌ ጎራ መሪ ነኝ፤ በርካታ ሚዲያዎች፤ ፖለቲከኞችና ድርጅቶች ይደግፉኛል፤ ተሰሚነት አለኝ፤ እኔ የምለውን የሚሰሙ ተከታዮች አሉኝ» የሚል ማን አለብኝነት ብቻ ነው።

በመጅሊስ ጉዳይ ተቋማዊውን አሠራር፣ የሕግ የበላይነትንና የሕዝበ ሙስሊሙን ፍላጎት ስታነሳ ጉዳዩን በሙፍቲ ግለሰባዊ ስብዕና መለካት የሚፈልጉ፣ ግራ ቀኙን ሰምተውና አመዛዝነው «እውነቱ የቱ ጋር ነው?» ብሎ አቋም ከመያዝ ይልቅ ሁለት ሦስተኛዎቹን የመጅሊስ ጠቅላላ ጉባኤ አባላት ዑለሞች ድምጽ ባላወቀ የሚያልፉ ሰዎች አሉ። የክልል እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤቶችን ውሳኔዎችን ተቃርነው፣ ከ2004 ጀምሮ በይፋ ሕዝበ ሙስሊሙ «መሪዎቼን በነጻነት የመምረጥ መብቴ ይከበርልኝ» ብሎ ሲያደርጋቸው የነበሩትን ትግሎችንና የተከፈለውን ዋጋ ጭምር ከቁብ ሳይቆጥሩ ጉዳዩን አለባብሰው ለማለፍ ይሞክራሉ።

በተለይ ደግሞ ያንን ትግል ደግፈው የነበሩ አንዳንድ ሚዲያዎችና ግለሰቦች ጉዳዩን ከተቋማዊ ጉዳይነት ይልቅ ቡድናዊና ግለሰባዊ በማድረግ በሚዲያ ብቻ በሚያውቋቸው ሙፍቲ ንግግር አስታክከው፣ በጥልቅት በማያውቁት የሙስሊሙ ጉዳይ በጭፍኑ ሰምጠው ከመግባት አልፈው ከእውነታው ተቃራኒ የመቆም አዝማሚያ ማሳየታቸው ከጅምሩም የሕዝበ ሙስሊሙን ትግል የደገፉት በጊዜው እነርሱ ሊጥሉት ይፈልጉት የነበረውን የኢሕአዴግን መንግስት «በማዳከም ረገድ ያግዘናል» በሚል ሀሳብ እንጂ ለእውነት፣ ለነፃነትና ለዲሞክራሲ ከመቆም እንዳልነበር ግልጽ እየሆነ ነው።

በእርግጥ «ሙፍቲን እንደግፍ» በሚል በቤተ ክርስቲያን አካባቢ ኮሚቴ ሲቋቋም «ይህ ጉዳይ የሙስሊሞች ነው፤ እኛን አይመለከትም» ብሎ አካሄዳቸውን የተቃወመ ክርስቲያን ወዳጄ ስለጉዳዩ ከወራት በፊት ቀድሞ መረጃውን አድርሶኝ ነበር። እሱን መሰል ቅን ወዳጆቼና ቤተ ክርስቲያናቸው እንድትጠናከርላቸው የሚሹ በርካታ ክርስቲያኖች ለራሳቸው የሚፈልጉትን ተቋማዊ አንድነት «ለመጅሊሱ ይጠላሉ» ብዬ ማሰብ አልችልም። እንደውም ሰሞኑን ጋዜጠኛ ፋሲል የኔ ዓለም ከዚሁ ጋር ተመሳሳይ አቋሙን ገልጿል። እንደሚከተለው ጽፎ ነበር...

«ለሙስሊም ወገኖቼ የማስተላልፈው አንድ ነገር ነው። የሃይማኖት ተቋማት መጠናከር ለአገር ሰላምና መረጋጋት የሚኖረው ጥቅም ከፍተኛ ነው። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ሲኖዶስ በመከፋፈሉ ቤተክርስቲያኗ እና ኢትዮጵያ ምን ያክል ተጎድተው እንደነበር የምታውቁት ነው። የእናንተ መጅሊስ ከሁለት መከፈልም ተቋሙንም ሆነ አገርን በከፍተኛ ደረጃ ይጎዳል። ስለዚህ የማንንም ጣልቃ ገብነት ሳትሹ፣ ችግራችሁን በራሳችሁ ለመፍታት ሞክሩ። እንኳንስ አንድን ተቋም አገር መምራት የሚችሉ ብዙ ሙስሊም ሊቆች አሉ። ተጠቀሙባቸው።»

ሆኖም ሰሞኑን በገሃድ እንደሚታየው ማኅበሩ አካባቢ ያሉ ጽንፈኛ ሰዎችና ሚዲያዎች የሙስሊሙ ተቋም መዳከም ለእነርሱ የጥንካሬ ምንጭ የሚሆን መስሏቸው ድንበር ተሻግረው በሙስሊሙ መጅሊስና ተቋማዊ መብት ጉዳይ «ዲያቆን» የሚለውን ማዕረጋቸውንና ገለልተኛ መስለው በሚዲያ ዘርፍ የወሰዱትን ስምሪት ረስተው እንደ አንድ ኡስታዝና ሙስሊም አክቲቪስት በሚዲያ ሲፈተፍቱ ማየት ያሳፍራል።

አንተ ሙስሊሙ ይሉኝታ ቀፍድዶህ በተቋምህ መጅሊስ ጉዳይ ባይተዋር ሆነህ ስትሽኮረመም እነሱ በአንተ ተቋም ይራኮታሉ። «የማህበረ ቅዱሳንና የሞዐ ተዋሕዶ ዲያቆናት ፣አባላትና ደጋፊዎች የመጅሊስ የበላይ ጠባቂ ሆኑ እንዴ? ወይስ ሳናውቀው መጅሊስ ለነርሱ ተላልፎ ተሸጠ ወይ?» ብለህ ልትገረም ሁሉ ትችላለህ።

በሃይማኖታቸው ሳይሆን በሰው ሃይማኖት መልካምና የተሻለ ነገርን ከመመኘት በዘለለ ጣልቃ በመግባት ለሕዝበ ሙስሊሙ ሳይሆን ለራሳቸው ማን እንደሚጠቅማቸው ስሌት በመስራት «ሙፍቲን እንደግፍ» ብለው በኮሚቴ ደረጃ ተዋቅረውና ተናበው እየሠሩ ያሉ አካላት ፍላጎታቸው ከምን አስተሳሰብ እንደመነጨ ይገባኛል። ፍላጎታቸው ከሃይማኖት ስለሚዘል «ጥቅማችንና ፍላጎታችን ያለበት ጉዳይ ሁሉ ጉዳያችን ነው» በሚል መርህ የሚመሩ፣ «ድንበራችን ጥቅማችን ያለበት ድረስ ነው» በሚል አተያይ የተቀረጹ ቡድኖች ናቸው። በሙስሊሙ መጠቀሚያነት ማራመድ የሚሹት ፖለቲካዊ ዓላማ እውን የሚሆነው ደካማ፣ ልፍስፍስና ሽባ መጅሊስ ሲኖር ነው። ይህን ፍላጎታቸው እውን እንዲሆን አውቆም ይሁን ሳይገባው በመጅሊስ መጠናከር ላይ እንቅፋት የሆነን አካል ባላቸው ስልጣን፣ በሚዲያና በተለያዩ መልኮች ይደግፋሉ። ሙፍቲም በመጅሊስ ጉዳይ «ከጎናችን ቁሙ» ብለው ለክርስቲያኖች ጭምር ጥሪ ማድረጋቸው «ጥሪ ቀርቦልናል።» በሚል በግልጽ የችግሩ አካል ሆነው ለመቆም የተመቻቸው ይመስላል።