Get Mystery Box with random crypto!

'ሞት በጥር፣በነሐሴ መቃብር፣ለሰሚው...? ተአምር!! 'እንኳን ለበዓሉ ዋዜማ አደረሰን' ...እ | ✞ ኪዳነ ምህረት እናታችን ✞

"ሞት በጥር፣በነሐሴ መቃብር፣ለሰሚው...? ተአምር!!
"እንኳን ለበዓሉ ዋዜማ አደረሰን"

...እመቤታችን፡ወላዲተ-አምላክ-ድንግል ማርያም፣ጥር 21 ቀን 49 ዓም.ከዚህ ዓለም በሞት ባረፈች ጊዜ እንዲህ ሆነ ይላል የቤተክርስቲያኗ መጽሐፍ ፦
★....አንድ አይሁዳዊ-ሰው ሲሞት እንደሚፈጸምለት ሥርዓተ-ቀብር መሠረት፣ ቅዱሳን ሐዋርያት ሥርዓተ-ጸሎት አድርሰው "ጌቴሴማኒ(ን)በተባለው ቦታ ባዘጋጁት መካነ መቃብር ቅዱስ ሥጋዋን ሊቀብሩ ይዘው ሲሔዱ፣አንድ ያልጠበቁት ነገር ተከሰተ፡፡ነገሩ እንዲህ ነው፦"ለጨለማው መንግሥት የሚሠሩ፣የዳብሎስ ሥራ አስፈጻሚዎች አይሁድ ለካ የተለመደውን ሠይጣናዊ ምክራቸውን መክረው ነሯል፡፡እንዲህ ብለው፦"ከዚህ ቀደም ልጇ ክርስቶስ ከሞት ተነሣ ፣ዐረገ ብለው በማስተማር ዓለምን በትምህርታቸው ሞሏት
☞..."( ...እነሆም፥ ኢየሩሳሌምን በትምህርታችሁ ሞልታችኋል፤ የዚያንም ሰው ደም በእኛ ታመጡብን ዘንድ ታስባላችሁ ብሎ ጠየቃቸው እንዲል)"
(የሐሥ 5:28)፣እኛንም አዋረዱን፣አሣፈሩንም፡፡ስለዚህ
ደቀመዛሙርቱ በሌሊት መጥተው ሠረቁትበሉ ብለው ገንዘብ በጅተው፣የክርስቶስን ትንሣኤ በገንዘብ ኃይል ሊያስቀሩ የሞከሩ ሞኞች(ሞት ያላሸነፈውን እውነት በገንዘብ ለማሸነፍ መሞከር ሞኝነት ነውና)(ማቴ 28:-11-15)፣ዛሬ ደግሞ እናቱ(እመ-አምላክ)ከሞት ተነሣች ብለው እንደቀድሞው ጉድ ከሚያደርጉን፣"ንዑ ናውኢ ሥጋሃ ለማርያም "ኑ ሥጋዋን በእሳት እናቃጥለው"አሉ፡፡(ምክንያቱም ከተቀበረ ከሞት ይነሣብናል፣ካቃጠልነው ግን ዐመድ ሆኖ ይቀራል ብለው ነው)ይህንንም ለማስፈፀም "ስሙ ታውፋንያ"የተባለን ሰው ከመካከላቸው መረጡ፡፡እርሱም እንዲህ የሚል ሀሳብ አቀረበ"ብዙ ሆነን ከሄድን ይጠረጥሩናል፣ነገር ግን እኔ ብቻዬን ያዘንኩ መስዬ ሥጋዋ ያረፈበትን ያልጋውን መያዣ(ሸንኮራውን)ጨብጬ አስቆማቸዋለሁ፡በዚህ ጊዜ እናንተ ታግዙኛላችሁ በማለት"ያን ንጹሕ ሥጋዋን ለማቀጠል ሲሞክር፣የታዘዘ መልክ በሰይፍ ቀጣው፡፡እጆቹም ተቆረጡ ይላል፡፡ "እንኳን በእመቤታችን ላይ የተነሱ ፀረ-ማርያሞችን (Anti-Mary)ይቅርና በሌሎች የእግዚአብሔር ወዳጆች ቅዱሳን ላይ ያልተገባ ነገር ያደረጉትን ክፉዎችን እግዚአብሔር ሲቀጣቸው መጽሐፍ ቅዱስ ያስነብበናል ፦
☞..."፩ኛ ነገ 13:-4"....በእርሱም ላይ የዘረጋት እጁ ደረቀች፣ወደ እርሱም ይመልሣት ዘንድ አልቻለም "ይላል፡፡የሆነው ሆኖ ይህ ክፉ ሞክራቸው ሣይሳካላቸው ቀርቷል፡፡ሥርዓተ ቀብሩ ግን ለጊዜው አልተከናወነም ፡፡ምክንያቱ ደግሞ በጌታችን በክርስቶስ ላይ እንደሆነው("...በዚያን ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ሁሉ ትተውት ሸሹ እንዲል።ማቴ 26:56) ቅዱሳን ሐዋርያት አይሁድን ፈርተው የተበተኑ ሲሆን ከቅዱስ ዮሐንስ በስተቀር ማለቴ ነው !የወላዲተ አምላክ ቅዱስ ሥጋዋ ግን የፍቅር ሐዋርያ ከሆነው ዮሐንስ ጋር ወደ ገነት በመነጠቁ ነው፡፡የእግዚአብሔር መልአክ ካሁኑንና ወንጌላዊውን ቅዱስ ዮሐንስን ጨምሮ ወደ ገነት ዐሳርጎ በዚያም በሕይወት ዛፍ ስር ሰማያውያን ካህናት እያጠኑት እንዲቆይ ተደርጓል(ወሱራፌል ዐጠኑ ሥጋሃ በማዕጠንተ-ወርቅ እንዲል ☞ቅ.ያሬድ)፡፡የቅዱስ ሥጋዋ የመቀበሩን ምስጢር በጊዜው ፣በዕለቱ እናየዋለን፡፡ከዚያ በፊት ግን፣አይሁድንና መሰሎቻቸውን ፣ታውፋንያንና ግብር አበሮቹን፡ጥያቄ እንጠይቃቸው፦

...አይሁድና አይሁዳውያን ሆይ!"በልጇ በክርስቶስ ላይና በቅዱስ ሥጋው ላይ የፈጸማችሁት ግፍ አልበቃ ብሏችሁ፣ዛሬ ደግሞ በእናቱ(በዙፋኑ፡፱ኝ ወራት በከተመበት)ላይ እንዴት ለመነሣሣት ሞከራችሁ? እስከመቼስ የሰይጣን መሣሪያዎች ትሆናላችሁ?
...ታውፋንያ ሆይ!"ያን የመለኮት ማደሪያ የሆነውን ቅዱስ ሥጋ-በእሳት ታቃጥለው ዘንድ፣እጆችህ እንዴት ታዘዙልህ? የእሳቱን ማኅደር በእሳት ታቃጥለው ዘንድ ልብህ እንዴት ጨከነልህ?
...አይሁድ፣መናፍቃን እንዲሁም በህብረት የምትሠሩ ሆይ!የእመቤታችንን የቅዱስ ሥጋዋን ሥርዐተ-ቀብር ለጊዜው እንዳስተጓጎላችሁ፣ዛሬም የእመቤታችን ፍቆሯ፣ልመናዋ፣በረከቷ፣ወደልጇ የምታቀርበው ምልጃናጸሎቷ...በሚወዷትና በሚያከብሯት፦በምእመናን፣በአገልጋዮች፣በቤተ-ክርስቲያን....ልብ ውስጥ እንዳያድር፣እንዳይቀበር..ትሠራላችሁና ተስፋ አትቆርጡም ?
...ደግሞ "ወላዲተ-አምላክ፣የንጉሡ እናት፣ ከሞት አልተነሳችም እያሉ የሚደሰኩሩ ምልምሎች አሰማርታችሗልና ለመሆኑ እርሷ "የሕይወት እናት"መሆኗን ዘንግታችሁት ነው?"....እርሷ እኮ ሞትን የገደለ ልጅ እናት ናት ምኑ ይሆን የከበዳችሁ?ሌላው ትዝብት ውስጥ የከተታችሁ ነገር ደግሞ፦በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሞትን አሽንፈው፣በሕይወት ተውጠው፣እግዚአብሔር ወደሚያውቀው ቦታ የወሰዳቸውን ሰዎች መዘንጋታችሁ ነው፡፡("በተአምኖ ፈለሰ ሄኖክ ከመ ኢይርአዮ ለሞት"<ሄኖክ ሞትን እንዳያይ በእምነት ተወሰደ፣ እግዚአብሔርም ስለወሰደው አልተገኘም (ዕብ 11:-5፤ዘፍ 5:-24) ፣ታላቁ የእግዚአብሔር አገልጋይ ኤልያስም ጓደኞቹ እየተመለከቱት በእሳት ሰረገላ ታግዞ ወደሰማይ ወጣ ይላልና (2ኛ ነገ 2:-1-11) ስለዚህ ምን አዲስ ነገር ተፈጠረና ነው የምታካብዱት?

...የሆነው ሆኖ የእመቤታችን ቅዱስ ሥጋዋ እንዳሰባችሁት በእሳት ሳይቃጠል፣እግዚአብሔር ወሰዶታል፡ሠውሮታልም፡፡እንደተሰወረ ግን አልቀረም፡ቅዱሳን ሐዋርያት በሱባዔ ያቸው ፍጻሜ ማግስት ቀደም ሲል ባዘጋጁት መካነ መቃብር በክብር አሳርፈዋል ፡፡ነገር ግን እናንተ እንደፈራችሁት፣ቅዱሳን ሐዋርያትና እኛ ደግሞ እንዳመነው እመቤታችን በልጇ በክርስቶስ ኃይል ከሞት ተነሥታ ዐርጋለች፡፡ዛሬ እመቤታችን በቅዱሳን ነቢያት ትንቢት በተነገረላት መሠረት!☞ንግሥትናትና በልጇ በንጉሡ-ክርስቶስ ቀኝ በክብር ተቀምጣለች(መዝ 44(45):-9 ) ይኸው ነው፡፡ስለዚህ፦

...በጎልጎታ ያለው የክርስቶስ መካነ-መቃብር ባዶ እንደሆነ ሁሉ ( "... እንደ ተናገረ ተነሥቶአልና በዚህ የለም፤ የተኛበትን ስፍራ ኑና እዩ።"ማቴ 28:-6 እንዲል..)፣
...በጌቴ ሴማኒ ያለው የእመቤታችንም መካነ-መቃብር ባዶ ነው፡፡በመሠረቱ የእመቤታችን ከሞት መነሣት የሚደንቅ አይመስለኝም ፡፡ምክንያቱም
1ኛ. እርሷ ሞትን የገደለው የንጉሡ የኢየሱስ እናት በመሆኗ!
2ኛ. የተነሣችውም የሞቱትን መቀስቀስ በሚችለው በክርስቶስ ኢየሱስ ኃይል በመሆኑ( "... አብ ሙታንን እንደሚያነሣ ሕይወትም እንደሚሰጣቸው፥ እንዲሁ ወልድ ደግሞ ለሚወዳቸው ሕይወትን ይሰጣቸዋል።"(ዮሐ 5:-21)እንዲል፡፡
3ኛ. እመቤታችን ልዩና እመሕይወት በመሆኗ
ነው፡፡

የወላዲተ-አምላክ በረከቷ ይደርብን፣ጸሎቷም ይጠብቀን አሜን፡፡


@kidanemihiret2116