Get Mystery Box with random crypto!

ታኅሣሥ_፲፱ በዓለ ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት ፡፡ ቅዱስ ገብርኤል፤ #ሊቀ_መላእክት_በመላእ | ዳግም ምጽዓት

ታኅሣሥ_፲፱ በዓለ ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት ፡፡
ቅዱስ ገብርኤል፤
#ሊቀ_መላእክት_በመላእክት_ሁሉ_ላይ_የተሾመ_ነው_ሄኖክ_10፥14
#የአርባብ_የ10ሩ_ነገደ_መላእክት_አለቃ_ነው
#ከከበሩ_መላእክት_አንዱ_ነው_ሄኖክ_6፥7፤
#አካሉ እንደ ቢረሌ የሚመስል (ጽሩይ የሆነ) ፥ ፊቱም እንደ መብረቅ አምሳያ የሆነ፤ ዐይኖቹም እንደሚንበለበል ፋና፣ ክንዶቹና እግሮቹም እንደ ጋለ ናስ፣ የቃሉም ድምፅ እንደ ብዙ ሕዝብ ድምፅ ነው፡፡/ዳን.10፥5-9/
#መልአከ_ራማ_ዘራማ_ልዑል_ነው፤ (የራማ ልዑል ነው)
#አብሣሬ_ትስብእት_ነው፤
#መጋቤ_ሐዲስ_ነው፤ ቅዱሳንመላእክት
#በእግዚአብሔር_ፊት_የሚቆም_መልአክ_ነው_ሉቃ_1፥19፤
#ለቅዱሳን_እውቀትን_የሚገልጽላቸውና_ከአላውያን_የሚታደጋቸው_ነው_ /ድርሳነ_ገብርኤል/
#መልአከ_ሰላሞሙ_ወመልአከ_ኪዳኖሙ_መልአከ_አድኅኖ_መልአከ_ኀይል_መልአከ_ፍስሐ (የሰላም መልአክ ፥ የኪዳን መልአክ፥ አዳኝ መልአክ፥ ኀያል መልአክ ፥ የደስታ መልአክ ነው)
#ከሣቴ ጥበብ (ጥበብን የሚገልጽ ነው) /ት.ዳን./
#ናዛዜ_ኅዙናን_ (ያዘኑትን_የሚያጽናና_) መልአክ_ነው፨
✤ ገብርኤል ማለት የእግዚአብሔር ልጅ ማለት ነው፤ የወልደ እግዚአብሔርን መወለድ አብሥሯልና፨ አንድም የሁለት ቃለት ጥምር ነው እነዚህም ገብር እና ኤል ሲሆኑ ትርጕማቸውም ገብር አገልጋይ ማለት ሲሆን ኤል ማለት ደግሞ አምላክ ማለት ነው፤ በተገናኘ ገብርኤል ማለት የአምላክ አገልጋይ /የእግዚአብሔርን ልጅ የሚመስል የአምላክ አገልጋይ/ ማለት ነው፡፡
✼ ነቢዩ ዳንኤል “ዐይኖቼንም አነሣሁ” አለና አስከትሎ “እነሆም በፍታ የለበሰውን ጥሩም የአፌዝን ወርቅ በወገቡ ላይ የታጠቀውን ሰው አየሁ፡፡ አካሉም እንደ ቢረሌ ይመስል ነበር፤ ፊቱም እንደ መብረቅ አምሳያ ነበረ፤ ዐይኖቹም እንደሚንበለበል ፋና፣ ክንዶቹና እግሮቹም እንደ ጋለ ናስ፣ የቃሉም ድምፅ እንደ ብዙ ሕዝብ ድምፅ ነበረ፡፡… ይህንንም ታላቅ ራእይ አየሁ፤ ኃይልም አልቀረልኝም፤ ክብሬም ወደ ውርደት ተለወጠብኝ ኃይልም አጣሁ፡፡ የቃሉንም ድምፅ ሰማሁ፤ የቃሉን ድምፅ በሰማሁ ጊዜ ደንግጬ በምደር ላይ በግምባሬ ተደፋሁ” አለ፡፡(ዳን.10፥5-9) ነቢዩ ዳንኤል እንዲህ ብሎ የተናገረው የመላእክት አለቃ የቅዱስ ገብርኤልን አስፈሪ ግርማ በተመለከተ ጊዜ ነበር፡፡
፠ “እነሆ ከዋነኞቹ አለቆች” አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ”(ዳን.10፥13) ብሎ በተናገረው ንግግሩ በመላእክት ላይ የተሾሙ ሌሎች አለቆች እንዳሉ ማስተዋል እንችላለን፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በቅዱሳን መላእክት ዘንድ ስላሉት ነገዶች ሲገልጽ “… በሰማይ ያለውን በምደር ያለውን የሚታየውንና የማይታየውን መናብርትም ቢሆኑ አጋእዝትም ቢሆኑ መኳንንትም ቢሆኑ ቀደምትም ቢሆኑ ሁሉም በእጁ ሆነ፤ ሁሉም በእርሱ ለእርሱ ተፈጠረ” (ቈላ.1፥16) በማለት ይዘረዝራቸዋል፡፡ ከዚህ ተነሥተን መላእክት በተለያዩ ዐበይት ነገዶች የተከፈሉና ለእያንዳንዱም ነገድ የራሱ የሆነ አለቃ እንዳለው ማስተዋል እንችላለን፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም ከእነዚህ ዐበይት የመላእክት ነገዶች መካከል አንዱ በሆነው አርባብ በሚባለው ዐቢይ ነገድ ላይ የተሾመ ሲሆን ከ100ው ነገደ መላእክት መካከል ከበታቹ የሚመራቸው ዐሥር ነገደ መላእክት አሉት፤ ከተማቸውም በሰማየ ራማ ነው፡፡

✼ ቅዱሳን መላእክት በቅዱስ ሚካኤል ፊት አውራሪነት የሰው ልጆች ጠላት የሆነውን ዲያብሎስን ተዋግተው ድል ከመንሳታቸው አስቀድሞ፤ እንደ አምላክ ሊመለክ የወደደውን ሳጥናኤልን ቅዱስ ገብርኤል በመቃወም ‹‹ንቁም በበህላዌነ እስከ ንረክቦ (ነአምሮ) ለአምላክነ “አይዟችሁ ፈጣሪያችን እስክናገኘው፣ እስክናውቀው ድረስ በያለንበት ጸንተን እንቁም፡፡” (አክሲማሮስ ገጽ.35) በማለት መላእክትን ያረጋጋ መልአክ ነው፡፡

✼ ቅዱስ ገብርኤል በተወዳጁ መልአክ በቅዱስ ሚካኤል መሪነት የሰው ልጆች ጠላት የሆነውን ዲያብሎስን ተዋግተው ድል እንዲያደርጉ ወደ ጥልቁ እንዲጣል አድርጓል ራእ12፥7፤ ነቢዩ ኢሳይያስ በሰማያት የሳጥናኤል ትዕቢትና ውድቀት ምን እንደሚመስል ሲጽፍልን “አንተ በንጋት የሚወጣ አጥቢያ ኮከብ ሆይ እንዴት ከሰማይ ወደቅህ! ወደ አሕዛብ መልእክትን የላክ አንተ ሆይ እንዴት እስከ ምድር ድረስ ተቀጠቀጥህ! አንተም በልብህ ወደ ሰማይ ዐርጋለሁ ዙፋኔንም ከእግዚአብሔር ከዋክብት በላይ ከፍ ከፍ አደርጋለሁ፤… በልዑልም እመሰላለሁ አልህ፡፡ ዛሬ ግን ወደ ሲኦል ትወድቃለህ፤ ወደ ምድር ጥልቅም ትወርዳለህ” (ኢሳ.14፥16) በማለት ገለጠልን፤ ወደ ምድር የጣሉት በመላእክት አለቃ በቅዱስ ሚካኤል መሪነት እነ ቅዱስ ገብርኤል ናቸው፡፡

✼ ቅዱስ ገብርኤል ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ከሊቃነ መላእክት አንዱና በእግዚአብሔር ፊት የሚቆመው ታማኝ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ነው ብሏል (ሉቃ 1፥19)፤
✼ ታላቁ ነቢይ ሄኖክም ስለ ነገረ መላእክት በተናገረበት አንቀጽ እንዲህ ሲል መስክሯል ‹‹በአበቦች ላይ በገነትም በጻድቃን ላይ በኪሩቤልም ላይ የተሾሙ ከከበሩ መላእክት አንዱ ገብርኤል ነው፡፡›› ሄኖክ 6፥7፤ ‹‹በሦስተኛውም በመላእክት ሁሉ ላይ የተሾመ ቅዱስ ገብርኤል ነው›› ሄኖክ 10፥14 እያለ የመልአኩን ክብር ተናግሯል፡፡

** ቅዱስ ገብርኤል መንፈሳዊ እውቀቱን የሚያካፍላቸው መልአክ ብቻ አይደለም፤ ለእግዚአብሔር በመገዛታቸው ምክንያት ከአላውያን ገዢዎች ከሚደርስባቸው መከራም የሚታደጋቸው መልአክም ነው፡፡ ነገር ግን ያደረጋቸው ተዓምራቶች በመጽሐፍ ቅዱስ፣ በመልክኡ፣ በድርሳኑ፣ በተአምሩ፣ …. የተጻፉ ቢሆንም፤

✤✼ ታኅሣሥ 19 ካደረጋቸው ተራዳኢነት..
፠ አናንያና(ሚሳቅ)፣ አዛርያ(ሲድራቅ) እና ሚሳኤል(አብደናጎ) ያዳናቸው ያዳነበት ቀን ነው፡፡ አናንያና(ሚሳቅ)፣ አዛርያ(ሲድራቅ) እና ሚሳኤል(አብደናጎ) የፋርስ ባቢሎን ንጉሥ የነበረው ናብከደነፆር በዱራ(አዱራን) በሚባል ስፍራ ላይ ላቆመው ጣየዖት ምስል ስገዱ ሲላቸው …. የምናምነው አምላክ ያድነናል፤ ባያድነን እንኳን (አምላካችን በእሳት ሰማዕት እንድንሆን ፈቃዱ ቢሆነረ አንኳን) አንተ ላቆምከው ምስል አንሰግድም ብለውታል፡፡ ንጉሡም ወደ እቶን እሳት እንዲጣሉ አድርጓቸዋል፤ በመልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት ግን ከእቶን እሳቱ የልብሳቸው ዘርፍ እንኳን እሳት ሳይነካው ከእሳቱ ድነዋል፡፡እኛንም ያድነን አሜን::
እንዲሁም ታኀሣሥ 19፤

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ዘሀገረ_ቡርልስ_በዓለ_ዕረፍቱ_ እንዲሁም
#ኢትዮጵያዊው_አቡነ_ስነ_ኢየሱስ_ (#ገዳማቸው_በሰሜን_ጎንደር_ትክል_ድንጋይ_አካባቢ_የሚገኘው_) #በዓለ_ዕረፍታቸው_ነው_፡፡

/በቀጨኔ ደ.ሰላም መድኀኔዓለምና ደ.ት.ቅ.ገብርኤል ቤ.ክ ፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት ሕትመት እና ሚዲያ ንዑስ ክፍል የተዘጋጀ ::/
#share
T.me/dagmele19