Get Mystery Box with random crypto!

+++ እስራኤልን የሚያድን አዳኝ +++ መጽሐፍ ቅዱስ 'እስራኤልም ወደ እግዚአብሔር ጮኹ እግዚአብሔ | ብራና ሚዲያ BRANA MEDIA

+++ እስራኤልን የሚያድን አዳኝ +++
መጽሐፍ ቅዱስ "እስራኤልም ወደ እግዚአብሔር ጮኹ እግዚአብሔርም የሚያድናቸው አዳኝ የካሌብን የታናሽ ወንድሙን የቄኔዝን ልጅ ጎቶንያልን አስነሣላቸው።" ይላል። (መሳ: 3:9) መስፍኑ ጎቶንያል እግዚአብሔር ያስነሥሣው አዳኝ የሚያድን መባሉን ትመለከታላችሁን? ማዳን የማነው? የእግዚአብሔር ! መስፍኑ ጎቶንያልን የሚያድን አዳኝ አድርጎ ያስነሣው ማነው? እግዚአብሔር! ጎቶንያል የሚያድን አዳኝ መባሉ የእግዚአብሔርን አዳኝነት ያስተሐቅራልን? በፍጹም! ታድያ ድንግል ማርያምን በጸጋ የተሞላች መድኃኒት ክርስቶስን የወለደች በጀርባዋ ያዘለች ጡቶቿንም ያጠባች በማዳኑም ጉዞ ያልተለየች የደስታ መፍሰሻ ምክንያተ ድኂንም በመሆኗ የምታድን አዳኝ ብንላት ችግሩ ምንድነው? ከጎቶንያል የሚልቅ ጸጋ አልተሰጣትምን? እርሷ መድኃኒት ቤዛ የምታድን መባሏን የምትቃወሙ መጽሐፍ ቅዱስ ሙሴን ቤዛ ጎቶንያልን አዳኝ የሚያድን ሲልስ ምን ትሉ ይሆን? ስህተት ነውን?

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደቀመዝሙሩ ጢሞቴዎስን "ለራስህና ለትምህርትህ ተጠንቀቅ በእነዚህም ጽና ይህን ብታደርግ ራስህንም የሚሰሙህንም ታድናለህ።" በማለት ይመክረዋል:: (1ጢሞ 4:16) ጢሞቴዎስ ታድናለህ ሲባል ማንን ነው የሚያድነው? ሰዎችን አይደለምን? እንዴት ነው የሚያድነው? በእምነት የሚያጸና በምግባር የሚያቀና መልካም አኗኗርን እንድንኖር የሚያደርግ ለመንግሥተ ሰማያት የሚያበቃ ትምህርት በማስተማር አይደለምን? ሰዎችን ወደ መድኃኒት ክርስቶስ በትምህርትም በኑሮም የሚመሩ አዳኞች የሚያድኑ ታድናላችሁ አድኑ ተባሉ::

ሐዋርያትን ጌታችን ወደ ዓለም ሲልካቸው በሰጣቸው የማዳን ጸጋ ሰዎችን ከርኩሳን መናፍስት ከእኩያን አጋንንት እንዲታደጉ እንዲያድኑ በማዘዝ ነው "ሂዱ አጋንንትን አውጡ ሕሙማንን ፈውሱ(አድኑ)።" እንዲል:: (ማቴ 10:8) በዚህ ሐዋርያዊ ተልእኳቸው በደዌ ሥጋ በአጋንንት እስራት የተያዙትን በተአምራት በደዌ ነፍስ በኃጢአት የተያዙትን በትምህርት አድነዋል:: እንደ እነርሱ ያሉ የእነርሱን ፍኖት የተከተሉ እውነተኞች ቀሳውስትም በጸሎታቸው የተቀደሰውን ቅብአት እየቀቡ ስመ እግዚአብሔርን እየጠሩ በደዌ ሥጋ በደዌ ነፍስ(በኃጢአት) የተያዙትን እንዲያድኑ ታዘዋል በዚህም የሚያድኑ ተብለዋል። ( ያዕ 5:14-15)

++እግዚአብሔር ሕይወትን ለማዳን ከናንተ በፊት ሰድዶኛል +++ ቅደስ ዮሴፍ
(ዘፍ 45:5))

ዮሴፍ የንጽሕና ምሳሌ ነው:: የጴጥፋራ ሚስት ለኃጢአት ብትጋብዘው እምቢ ብሏታልና:: (ዘፍ 39:7-17)

ዮሴፍ ይቅርታ የማድረግ ምሳሌ ነው በከንቱ የጠሉትን ለእስማኤላውያን በሃያ ብር የሸጡትን በጉድግጓድ የጣሉትን ወንድሞቹን ሊበቀል እየቻለ ይቅርታ አድርጎላቸዋልና:: (ዘፍ 45:1)

ዮሴፍ የበረከት ምክንያት ነው "እግዚአብሔር የጴጥፋራን ቤት ውስጡንም ውጭውንም ስለ ዮሴፍ ባረከው የእግዚአብሔርም በረከት በውጭም በግቢም ባለው ሁሉ ላይ ሆነ።" እንዲል (ዘፍ 39:5) በዚህም " የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው።"፤ "በረከት በጻድቅ ራስ ላይ ነው" ፤ "በጻድቃን በረከት ከተማ ከፍ ከፍ ትላለች" የሚሉትም ቃላት እውነተኞች መሆናቸውን አወቅን:: (ምሳ 10:6፣10:7፣ 11:11) ዮሴፍ ከተደረገበት ነገር አንዱ በክፋት አንዳች ክፉ ሳይገኝበት በገዛ ወንድሞቹ በከንቱ መጠላቱ ከዚያም ባለፈ መጀመርያ ለእስማኤላውያን ነጋዴዎች ኋላም ለግብፃውያን መሸጡ ነው:: ዮሴፍ ወንድሞቹ ከሸጡት በኋላ ብዙ ፈተናዎችን አልፎ እግዚአብሔር ረድቶት ምሥጢርን ገልጦለት በግብጽ ቤተ መንግሥት ታላቅ ለመባል በቃ:: ዓለም በሙሉ እህል ፍለጋ ከረጢቱን ይዞ ወደ እርሱ ተመመ:: ወንድሞቹም መጡ በክፋት ሳይጠላቸው ሊበቀላቸው እየቻለ ሳይበቀላቸውም "እኔን በመሸጣችሁ አትዘኑ እግዚአብሔር ሕይወትን ለማዳን ከናንተ በፊት ሰድዶኛልና።" አላቸው ይላል መጽሐፍ ቅዱስ:: (ዘፍ 45:5) "እግዚአብሔር በቅዱሳኑ ድንቅ ነው" እንዲልም እግዚአብሔር ማዳን እየተቻለው ፈቃዱን የፈጸሙ ቅዱሳኑን ምክንያት አድርጎ ማዳኑን እንደሚፈጽም ከዚህ ታሪክ እንማራለን:: (መዝ 67:35) ዮሴፍ "ሕይወትን ለማዳን ተላክሁ።" እንዳለ አትሰሙምን ? ዮሴፍ እኮ የእግዚአብሔር ሕይወትን ለማዳንም የላከው እግዚአብሔር ነው:: እነሆ ከዮሴፍ የምትበልጥ ከዚህ አለች እርሷ የዮሴፍን የአብርሃምን ፈጣሪ ክርስቶስን የወለደች ናትና:: (ሉቃ 1:28) የዮሴፍን ፈጣሪ ክርስቶስን የወለደች ብርሃን የወጣባት ምሥራቅ ናትና:: (ኢሳ 9:2 :6 ዮሐ 4:12-15) በረከትን የሚያድል የበረከት አባት ክርስቶስን ወልዳለችና። (ሉቃ 2:1-15) "ዮሴፍ ሕይወትን አዳነ" ብሎ መጽሐፍ ከነገረን እመቤታችን በተሰጣት ጸጋ ሕይወታችንን ከመተተኞችና ከክፉዎች ታድናለች ብንል ችግሩ ምንድነው?

ሰዎቹ ተሸክመውት ያለውን መጽሐፍ አያስተውሉትም እንጂ ቅዱሳን ሐዋርያት "እንዲሁ ጌታ እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ለማዳን ትሆን ዘንድ ለአሕዛብ ብርሃን አድርጌሃለው ብሎ አዞናል።" ብለው የተልእክኳቸው ዓላማ ምን እንደሆነ እንደተናገሩ ይመሠክርላቸዋል። (የሐዋ 13:47) ሐዋርያት ለምን ወደ ዓለም ተላኩ? ሰዎችን የክርስቶስን ቃል አስተምረው መክረውና ገሥጸው በትምህርታቸው ለክብር ለማብቃት ነው:: በዚህም "ለማዳን የተላኩ" "ብርሃናት" ተባሉ። (ማቴ 10:1-16) ሐዋርያት ለማዳን ተልከናል ሲሉ ራሳቸውን ከክርስቶስ ጋር እያፎካከሩ ነውን ? አይደለም !! ቅዱሳን እንዲሁም እመቤታችን "መድኃኒት ቤዛ የሚያድኑ ለማዳን የተላኩ " ለምን እንደተባሉ መርምሮ በቀና አእምሮ መረዳት መልካም ነው ::

የእናቱ የእመቤታችን አማላጅነት የልጇ ቸርነት አይለየን !!

ቢትወደድ ወርቁ
ኅዳር 23 ቀን 2015 ዓ.ም