ዘሪ ሊዘራ ወጣ ማቴ 13፥3 ገበሬ አንተ ፥ ልትዘራ ስትወጣ ወደ መሬት ልጅህ ፥ ወደ እኔ ስትመጣ ይህንን እይልኝ ይህንን ተረዳልኝ ሁሉም እንደሚያውቀው ፥ እኔ የምገኘው ... በሁሉ ማለፊያ ፥ በዓብይ መንገድ ዳር ነው። በዚያውም ላይ ሌላ ምልክት በጭንጫ እኔነት፥ እሾህ አሜካላ ፥ በብዙው በቅሎበት በምድር መካከል ፥ ታገኘዋለህኝ ፥ የእኔን መሬትነት። ጌታዬ ...! እሾህ አሜካላ ፥ በእኔ ላይ እያለ ፥ በእኔ እየኖረ መሬት ልቦናዬ ፥ በረድኤትህ ቅፅር ደግሞም ካልታጠረ ጭንጫ ልቦናዬ ፥ ካልተስተካከለ መልካም መሬትነት ፥ በእኔ ዘንድ ከሌለ ፍሬን እንደማልሰጥ ፥ ልቤ ስለሚያውቀው ይህንን እላለው ... እጠይቅሃለሁ ፥ እሞግትሃለው ፍሬ ማፍራትን የምትሻ ፥ ይችን ጉስቁል መሬት ከመዝራትህ በፊት ፥ አንተው አስተካክላት ፥ አንተው አበጃጃት እሾሁን ነቃቅለህ አሜካላውን አቃጥለህ በጸጋ ጎብኝተህ ፥ በረድኤትህ አጥረህ ከመንገድ ዳርነት ፣ በፍፁም ታደጋት ፍሬን የምትሰጥ ፥ መልካም መሬም አርጋት በከኃሊነትህ ፥ እንደገና ስራት በፈጣሪነትህ ፥ እንዳዲስ ፍጠራት ያኔ ዘር ብትዘራ ፥ ቃልህን ብትወረውር ፥ አስተውላለሁ... ቃልህን ጸንሸ ፥ የመንፈስን ፍሬ ፥ በእውነት እሰጣለሁ። ያሊያ ግን ... ጭንጫነቴን ሳታስወግድ ፥ ቅፅርን በእኔ ሳታኖር አሜካላንም እሾህን ፥ ከእኔ ሳትነቅል እንደይጠቅመኝ እያወቅህ ፥ ዘርን አትዝራብኝ ዘሪን በማድከምና ዘርን በማባከን ፥ አታስፈርድብኝ ደግሞም እውነቱን ልንገርህ አቋሜ ይሄውልህ ! መሬት ነህ ብለኸኝ በክብር ፈጥረኸኝ በጭንጫነቴ ላይ ፥ ዘር ሲበቅል ዐይቼ ልቤን ሐሴት ሞልቶት ፥ በጣም ተደስቼ ወዲያውኑ የሚደርቅ በእሾህ የሚታነቅ በወፍ የሚለቀም ለማንም የማይጠቅም ሲሆን ስለ ማዬት ፥ ... ራሴን እየወቀስኩ ፍፁም እየተከዝኩ ላም አለኝ በሰማይ ፤ እንደስካሁን ያለ ፥ ሕይወት ከምገፋ ጌታዬ ሰርዘኝ ፥ ከፍጥረትነት መዝገብ ፥ መሬት ልጅህ ልጥፋ ዮሴፍ ጌትነት 27/10/13 ዓ.ም 304 views15:14