2023-05-06 22:37:23
.
የመገፋት ህመም : የማጣትን ፍቺ
ልንገርሽ እንጂ እኔ : የት አውቀሽው አንቺ
ብዙ ነገ እየሳልኩ : አብሬ ካንቺ'ጋ
ሳስብሽ አመሸሁ : እያለምኩሽ ነጋ
ሀሳቤን ሰርቀሽው : ቀኔ አላማረበት
ቀልቤን ሰውረሽው : አዋዋል ጠፋበት
ከእኔ'ጋ ነሽ እያልኩ : አብረሽኝ ከጎኔ
አንቺ ሩቅ ሄደሻል : እዛው ስቀር እኔ
የቀረበሽ ልቤ : አንቺን በወደደ
የማያውቀው ነፍሴ : በእሳትሽ ነደደ
መላ አካሌ አፍቅሮሽ : እኔን ጥሎ አበደ
እፋረድሻለሁ : በይ ካሽኝ እያልኩኝ
ለብቻየ ስቀር : ብዙ እንዳልነበርኩኝ
ለማን ዳኛ ልክሰስ : ማንስ ይሰማኛል
ጉዳቴን ያሰበስ : ምንድን ይክሰኛል
ጉዳዬን የሰማ : ያ ሁሉ ዳኛ ሰው
ክሴን አቃለለ : ብሶቴን መለሰው
እንግዲህ ምን ላድርግ...
ፍትህ ንብረት አይደል : አልገዛ አልዋሰው
የሰማኝ በሙሉ : የነገርኩት ዳኛ
አንችን ነፃ አረገሽ : እኔን ጥፋተኛ
ከእንግዲህ ለማንም : አልከስም በቅቶኛል
እስካሁን የሰማኝ : እስኪ ምን ጠቅሞኛል
አንቺ ጉልበተኛ : አንቺ ባለጊዜ
እኔ ሟች ደካማ : የዋጠኝ ትካዜ
አንቺን ማን ተሟግቶ : ችሎ ያሸንፍሻል
የቀረበሽ ሁሉ : ላንቺ ያዳላልሻል
ቁመናሽ እሳት ነው : አይን ጥርስሽ ገመድ
ውበትሽ አሳሳች : አሳሳቅሽ ወጥመድ
ማለፍ ቢሳናቸው : ይሄንን ፈተና
እኔን 'በዳይ' ማለት : ቀለላቸውና
እሷን ተበዳይ ሰው : እኔን ወንጀለኛ
ብለው ፈረዱብኝ : ከአንድም ሶስት ዳኛ
አምርሮ ቢያነባ : እንባዬ ቢፈስም
በያገኘው ችሎት : እልፍ ጊዜ ቢከስም
የፍርድን ጥም ሽቶ : ከጫፍ ጫፍ ቢያስስም
ገሳጭ ሰው ነው እንጂ : አይዞህ ባይ አይደርስም
በቃኝ አልካሰስ : ይቅርብኝ ልጎዳ...
ልተወው ግዴለም
ብቻ አውቄዋለሁ : በሰዎች ደጅ እንጂ...
ፍትህ በአገር የለም
አትፍሰስ ይበቃል : ከእንግዲህ እንባዬ
ጩኸቴ አላዋጣም : ይርታት ዝምታዬ
እንግዲህ ገብቶኛል...
ላገኘሁት ሰሚ : አልከስ አልዘልፍሽም
በየአደባባዩ : ስምሽን አልጠራሽም
በየችሎቱ በር : ነይ ግቢ አልልሽም...
ስምሽን ባጠፋ : ብፎክርም እንኳን : አትደናገሪ
ጩኸቴ ምንም ነው : ዝም ስል ግን ፍሪ:
በአቤኒ የተፃፈ
ከወደዱት ለወዳጅዎ ያጋሩት!
@bewketuseyoum19
@bewketuseyoum19
22 viewsAchilles, 19:37