Get Mystery Box with random crypto!

አማራውን በቋሚ የቀውስ አዙሪት የማድቀቅ ሴራ ሊቆም ይገባል!!! በአገራችን ተንሰራፍቶ የኖረውን | አንሙት አብርሃም

አማራውን በቋሚ የቀውስ አዙሪት የማድቀቅ ሴራ ሊቆም ይገባል!!!

በአገራችን ተንሰራፍቶ የኖረውን አፓርታይዳዊ የህወሃት የበላይነት ለማስወገድ የአማራ ህዝብ የደም መስዕዋትነትን ከፍሏል፡፡ይህ የደም መስዕዋትነት በአማራ ክልል ከተሞች የበርካታ አማራ ወጣቶችን ደም ያፈሰሰ ነው፡፡
ለአብነት ያህል በባህርዳር ከተማ በአንድ ጀምበር ብቻ ከ75 በላይ ወጣቶች ደማቸው ፈሶ ከጣና ጋር እንዲደባለቅ ሆኗል፡፡ በተመሳሳይ በጎንደር ከተማ የለውጥ ፈላጊ ወጣቶች ደም በየአስፋልቱ ሲጎርፍ በወቅቱ በፎቶ ጭምር ተደግፎ የወጣ መረጃ ነው፡፡ በአጠቃላይ ያለ አማራ ህዝብ የደም መስዕዋትነት ለውጥ የተባለው ነገር ጨርሶ የሚታሰብ አልነበረም፡፡

በዚህ መንገድ የመጣው ለውጥ መሰል ነገር እንዲፀናም የአማራ ህዝብ ግንባር ቀደም አጋርነቱን ለማሳየት የልጆቹ ደም በፈሰሰባቸው የአማራ ክልል ከተሞች ባደረገው ትዕይንተ-ህዝብ ዘር ሳይቆጥር ለውጥ የሚያመጣን ሁሉ ደግፏል፡፡
የአማራ ህዝብ ይህን ድጋፉን ያሳየው ጠላቶቹ እንደሚየስቡት ተላላ ስለሆነ አልነበረም፡፡ ይልቅስ ለውጥ የተባለውን ነገር በደሙ ያመጣው የለውጡ ግንባር ቀደም ባለቤት ስለሆነ፣ ለውጡ እንዳይስተጓጎል ካለው ጥንቃቄ ነበረ፡፡

ነገር ግን የአማራ ህዝብ ለለውጡ ስምረት ሲል ያደረገው ከፍተኛ የአጋርነት ስሜትና ሆደሰፊነት እንደ አላዋቂ ተላላነት አስቆጠረው፡፡ ይህም ለውጡን እንመራለን ብለው ስልጣን በያዙ ሰዎች አፍ በአደባባይ እስከመነገር ደረሰ፡፡
በአማራ ህዝብ የደም መስዕዋትነትና ሁለንተናዊ አጋርነት የመጣውን ለውጥ ለመምራት ወንበር ላይ የወጣው የኦሮሞ ገዢ ቡድን ወንበሩ ላይ በቅጡ ተደላድሎ ሳይቀመጥ ነበር የአማራን ህዝብ በተላላነት መዝለፍና ማቃለል የጀመረው፡፡ ዘለፋና ማቃለሉ አማራን በማንነቱ ለይቶ ወደ መጨፍጨፍ፣ ማፈናቀልና ማሳደድ ጥላቻ ወለድ ጭካኔ የተቀየረውም ወዲያው ነበረ።

ሆኖም የአማራ ህዝብ በትንሽ በትልቁ የማይበረግግ ጠንካራ የስነ-ልቦና ውቅር ያለው ህዝብ በመሆኑ ትናንት አጋር ያለውን አካል ለመንቀፍም የማይቸኩል፣ ከሁሉም በላይ ከራሱ አስበልጦ ሃገሩን የሚወድ የሃገር ምንነትን በውል የተገነዘበ፣ ታሪካዊ ዳራውም ጊዜያዊ ችግርን ተቋቁሞ ሃገረ-መንግስት ጠብቆ የማቆየት ልዕልና ያለው በመሆኑ እየተደረገበት ያለውን በደል ለሃገረ-መንግስቱ ህልውና ያገዘ መስሎት በትዕግስት ተሸክሞ አራት አመታትን አስቆጥሯል፡፡

ሆኖም ፖለቲካ ማለት አማራን ማሳደድ የሚመስለው የኦሮሞ ገዢ ቡድን አሁንም የአማራን ህዝብ ትዕግስት ከፍርሃት በመቁጠር የአማራን ህዝብ አንገት ለማስደፋት ያግዘኛል ያለውን አስነዋሪ ስራ ሁሉ በባለውለታው የአማራ ህዝብ ላይ መፈፀሙን ቀጠለ፡፡ በቤኒሻንጉል የአማራ ህዝብ በጅምላ ተገድሎ በስካቫተር ሲቀበር፣ ወለጋ በተባለው የኦሮሚያ ክልል አማራው በየደቂቃው እየሞተ በየእለቱ ሲፈናቀል ምንም አይነት የተጠያቂነት ስራ ያልሰራው መንግስት በአማራ ህዝብ ላይ በሚፈፅመው ግፍ ዋነኛ ባለሚና እንደሆነ ማረጋገጫ ነው፡፡

አገዛዙ አማራውን በቋሚ ቀውስ አዙሪት የማሰቃየት ተልዕኮ ይዞ እየሠራ ነው፡፡ በመሆኑም ከወያኔ ዘመን በቀጠለ ሁኔታ በአማራ ህዝብ ላይ የያዘው አስከፊ እና አስጸያፊ ዓላማ የተገለጠ ስራ ማድረጉ ፀሃይ የመታው ነውር ሆኗል፡፡ የአማራ እንቂዎችን፣ ወጣቶችን ፣ ተቆርቋሪዎችን እያሳደደ በማሰር አማራውን ያለመሪ የማስቀረቱን ተግባር ተያይዞታል፡፡
ኦሮሞ መር የሆነው ስርዓት በአማራ ህዝብ ላይ እያደረሰ ያለውን ዘር ማጥፋትን እና ዘር ማፅዳትን የጨመረ አስከፊ በደል ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ጭምር እየታዘበ ነው፡፡
ይህ አልበቃ ብሎ የአማራ ህዝብ ሞቶ ባመጣው የስርዓት ለውጥ፡ መድረሻ እንዲያጣ ሁለንተናዊ ጥቃት እየደረሰበት ነው፡፡ አማራነቱን የሚገልፅ መታወቂያው የመሳደድ፣ የመገደል እና የመጉላላት ምንጩ ሆኗል፡፡

የአማራ ህዝብ በምድር ትራንስፖርት ወደ ሃገሩ ዋና ከተማ መግባት እንደማይችል ስለሚያውቅ እጥፍ ድርብ ክፍያ ከፍሎ በአየር ትራንስፖርት መጓዝን መርጧል፡፡ ከአማራ ክልል እቃ ጭነው ወደ አዲስ አባባ የሚመጡ የከባድ መኪና ሾፌሮች ግማሽ የመሞት ግማሽ የመትረፍ እድል ይዘው ይጓዛሉ፡፡ ይህ ቅር አትበለው እንዲቀር አድርገው ሴራ ነው፡፡

ደክሞ ባቆማት ሃገር ዋና ከተማ እንዳይገባ ከመከልከል አልፎ በአዲስ አበባ ከተማ ሠርቶ የመኖር መብቱ በዚሁ ጨካኝ አገዛዝ ክልከላ ተጥሎበታል፡፡
በአመዛኙ የአማራ ወጣቶች የተሰማሩበት በአዲስ አበባ ዙሪያ የሚሠሩ የባለሶስት እግር ባጃጅ የትራንስፖርት አገልግሎት ከነጭራሹ ስራ እንዲያቆም ተደርጓል፡፡
በተመሳሳይ በአዲስ አበባ የበግ ንግድ እና የሽመና ስራን ጨምሮ በርካታ የአማራ ተወላጆቸን ከስራ በማስተጓጎል ከኦሮሚያ እና ከአዲስአበባ የማስወጣት ፀረ-ህዝብ ደባ እየተፈፀመ ይገኛል፡፡
ሸገር በሚል ስም በአዲስ አበባ ዙሪያ ሊገነባ የታሰበው ፕሮጀክትም ስራውን የጀመረው የአማራ ተወላጆችን ቤት አፍርሶ ከነልጆቻቸው ሜዳ ላይ አውጥቶ በመበተን ነው፡፡

በአዲአበባ የሚከበሩ በዓላት አማራን ማሳደጃ እና ማጥቂያ ከተደረጉ ውለው አድረዋል፡፡ በቅርቡ ከህግ ውጭ በምኒልክ አደባባይ እንዳይከበር ገዢው የኦሮሞ ኃይል በከለከለው የአድዋ በዓል የሽመና እና አልባሳት አምራቾችን ከማሠር እና ማጉላላት አልፎ በዓሉን ለማክበር በምኒልክ አደባባይ የተገኙ ዜጎች ላይ ነውረኛ ተግባሮችን ፈፅሟል፡፡

በአጠቃላይ ስልጣን የያዘው የኦሮሞ ገዢ ቡድን አማራው አንገቱን እንዲደፋ፣ መሪ እንዳይኖረው፣ ደክሞ ያፈራውን ንብረት እንዲያጣና ጠንካራ የስነ-ልቦና ውቅሩ በድህነት እና ተስፋ ማጣት እንዲኮላሽ፣ በእጁ የያዘውን ሁሉ እንዲጥል እየሰራ ይገኛል፡፡
ይህ መንግስትነትን የማይመጥን እኩይ አካሄድ ውጤቱ እንደታሰበው የአማራን ህዘብ ብቻ ለይቶ ማድቀቅና ማዋረድ አይሆንም፡፡ ይልቁንስ ሠፊው የአማራ ህዝባችን በጨቋኙ አገዛዝ ላይ ለላቀ ትግል እንዲነሳ የሚያደርግ እንጂ ከቶውንም አንገት እንዲደፋ ሊያደርገን አይችልም፡፡

ስለሆነም የአገዛዙ ክፋት እና ጥቃት ሰለባ የሆኑት ኢትዮጵያውያን ሁሉ አገዛዙ የገባበትን ጨካኝ ፀረ-ህዝብ ተግባር ለማስቆም የተለየ ጥረት እንዲያደርግ እንጠይቃለን፡፡
ሰፊው የኦሮሞ ህዝብ በስሙ ወንበር የያዘ አምባገነን ስብስብ በህዝቦች መካከል ጥላቻ እና ጠላትነትን እየዘራ መሆኑን በማሰብ በቃ እንዲሉት ወንድማዊ እና እህታዊ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡
ሰፊው የአማራ ህዝባችን እንደከዚህ ቀደሙ ሁሉ የአምባገነኑን ግፎች ለማስቆም እና ሁለንተናዊ ጥያቄዎቹን ለማስመለስ ለመታገል አንድነቱን አፅንቶ እንዲቆም ጥሪ እናቀርባለን፡፡

የህዝብ ትግል ያሸንፋል!

የአማራ ወጣቶች ማህበር
የአማራ ተማሪዎች ማህበር
የአማራ ጤና ባለሙያዎች ማህበር


መጋቢት ፬/፳፻፲፭ ዓ.ም