2022-09-01 18:40:49
ለመላትሒከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
ሕማመ ተጾፍዖን ለመቀበል ለተዘጋጁ ጉንጮችህ ሰላም እላለሁ። ኀሊናን ደስ ለሚያሰኙ አዕናፍህም ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
አቤቱ ሠራዊተ መላእክት እየተንቀጠቀጡ በፊትህ የሚቆሙ አንተ በቀያፋና ሐና አደባባይ ቆምህ። አቤቱ የኔ ጥፋት በአንተ ዘንድ ተፈላጊ አይደለምና እንደሰማሁትና እንደማውቀውም ሁሉ በመስቀልህ ቤዛነት አድነኝ።
ለአፉከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
አቤቱ እንደከረመ የወይን ጠጅ የሐሞትን መራራነት ላጣጣመ አፍህ ና ከናፍርህም ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
አቤቱ አምላካዊ ተአምራት የማድረግ ስልጣን በአንተ እጅ በመሆኑ። ዳግም በምትመጣባት በዚያች ዕለት ሑሩ እምኔየ የምትለውን የፍርድ ውሳኔ እንዳታሰማኝ በቸርነትህ እማፀናለሁ።
ለአስናኒከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
በቀራንዮ አደባባይ በመስቀል ላይ ሣለህ ስለዓለም ነፃ መውጣት የሰበከ አንደበትህና መለኮታዊ አስናኖችህ ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
ቃልህ የማይታበል የማይለወጥ ነውና መልአከ ሞት ነፍሴን በፊትህ ባቆማት ጊዜ አቤቱ ገጸ ምሕረትህን አትመልስብኝ።
ለቃልከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
አባት ሆይ፤ ይቅር በላቸው በማለት በታላቅ ቃል በመስቀል ላይ ለተናገረ ቃልህ ሰላም እላለሁ። በመስቀል ላይም በሰቀሉህ ጊዜና ጎንህንም በጦር በወጉ ጊዜ አንዳችም የተቃውሞ ትንፋሽ ላልተነፈሰ እሳት ትንፋሽህም ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
ከዚያ እስከዚህ ድረስ የሰራሁትን ኃጢአቴን ይቅር በል። አቤቱ ቅዱስ ስጋህን ከበላሁ ክቡር ደምህን ከጠጣሁ ቡኃላ ነፍሴ ጥፋት እንዳያገኛት በፍጹም ትጋት ደጅ እጠናለሁ።
ለጕርዔከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
ክቡር ልዑል ለሚሆን ጕርዔህ ሰላም እላለሁ። በገመድ እየሣቡ ለጎተቱት ክሣድህም ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
በቀራንዮ አደባባይ የተሰቀልከው ለሰው ልጅ ደህንነት እንደመሆኑ መጠን ስለእናትህ ስለድንግል ማርያም ብለህ ምሬሃለሁ ይቅር ብየሃለሁ በለኝ። ከአንተ በቀር ቸር ይቅር ባይ የለምና።
ለመታክፍቲከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
በጎልጎታና በቀራንዮ አደባባይ አርዑተ መስቀልን ተሸክመው ለተንገላቱ መተክፍትህ ሰላም እላለሁ። ዙፋኑን በዘባነ ኪሩቤል ለአዘጋጀ ዘባንህም ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
በቀል የሌለብህ አምላክ እንደመሆንህ በቅዱሳኖች በወዳጆችህ አማላጅነት እማፀናለሁ። ስማችሁን የጠራ እምርላችኃለሁ ስትል ቃል ኪዳን ገብተህላቸዋልና።
ለእንግድዓከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
የአዳምን ዘር ለማዳንና በጠቅላላው ለዓለም ቤዛ ለመሆን ሐፃውንተ መስቀልን ለታቀፉ ክንድህና ደረትህ ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
ለሰውነቴ መልካሙን የዕረፍት ጊዜ ስጣት። አቤቱ ሰውነቴን፤ ነፍሴን የሚፃረሯትን ጠላቶቼን ሁሉ፤ የሚያደርጉትን አያውቁምና አባቴ ሆይ ይቅር በላቸው ብለህ እንዳስተማርከን ይቅርታ ታደርግላቸው ዘንድ እማጸናለሁ።
ለአእዳዊከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
ለቤዛ ዓለም ስትል ለፈሰሰው ደምህ፤ ለተቸነከሩና በደም ለተጠመቁ እጆችህ ሰላም እላለሁ። በሌሊት የሚዘዋወረውን ድንገተኛ ጠላትና በቀን የሚጻረረውን የቀትር ኃያለ አጋንንት ለሚያዳሽቀው መለኮታዊ ግርማህም ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
በጎ ነገርን አሰጀምረህ የምታስፈጽም ቸር አምላክ ነህ። አቤቱ ከጎንህ የፈሰሰው ደመ መብረቅ ከላይ ወደታች በተቈለቈለ ጊዜ ድምፀ ጉህናው ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ አስተጋባ።
ለኵርናዕከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
በቅዱስ መስቀል ላይ በተሰቀልክ ጊዜ በግራና በቀኝ ተዘርግተው ለተንሰራፉ ክንድህና ውርቾችህ ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
አቤቱ ደዌ መከራ ከሌለበት፤ ተድላ ደስታ ከአለበት ኤዶም ገነት ታገባኝ ዘንድ እለምንሃለሁ።
ለእራኀከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
የእናታችን የሔዋንን በደሏን ይቅር ትልላት ዘንድ መከራን ለተቀበሉ መዳፎችህና ዓለማትን ሁሉ በመለኮታዊ ጥበብ ለፈጠሩ ዓሥሩ ጣቶችህ ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪየ ክርስቶስ ሆይ፤
የኃጥአን ነፍስ መጠጊያ አንተ ነህ፤ለዓለምም የምታበራላቸው እውነተኛ ፀሐይ አንተ ነህ።
ለአጽፋረ እዴከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
የዓሠርቱ ቃላተ ኦሪት ትእዛዛት ለተጻፉባቸው ንዑዳት ክቡራት ለሚሆኑ ለእጆችህ አጽፋር ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
ክቡር ዳዊት እንደተናገረው ጠላቶቼ ሰውነቱ ዱር ለዱር ተቅበዘበዘ እያሉ እንዳይዘባበቱብኝ በየጊዜው በየሰዓቱ በየዕለቱ ልመናዬን ሳቀርብልህ ፈጥነህ ተቀበለኝ እንጂ ቸል አትበለኝ።
ለገቦከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
ኀዘን ትካዜን ለሚያስወግድ መለኮታዊ ጎንህ ሰላም እላለሁ። በዓለሙ ሁሉ በጭንቅና በመከራ ላይ የሚገኙትንም ለሚያረጋጋ አምላካዊ ከርስህም ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
መድረቅ መጽነፍ የሌለበት ባሕረ ምሕረት እንደምሆንህ የቸርነትን ቃል መቼ ታሰማኝ ይሆን? እያልኩ ሁል ጊዜ አምላኬ አምላኬ እላለሁ።
ለልብከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
ናዝራዊ የተባልክ ለአንተ ለእግዚአብሔር ነቢይ ወመንፈሳዊ ለተባልክ ለአንተ ለመድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ልቡና ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
ስለትሕትና ሕጻን ወአረጋዊ እየተባልክ የምትመሰገን አንተን በመስፍኑ በጲላጦስ አደባባይ እንደወንጀለኛ አገልጋይ ባሪያ የሌዊና የይሁዳ ልጆች የሚሆኑ ካህናት እንዴት ሊገርፉህ ተበረታቱ አቤቱ ለትዕግሥትህ አንክሮ ይገባል።
ለኵልያቲከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
እንደ አጥቢያ ኮከብ በግራ በቀኝ ሆነው ለሚያበሩ ሁለት ኵልያቶችህ ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
በአካል ሦስት በባሕርይ አንድ እግዚአብሔር እየተባልክ ትመካለህ። አቤቱ አንተ ክርስቶስ ለኃጥአን ስንዃ ሕይወታቸው ነህና፤ አቤቱ ስንልህ በከንቱ እንዳንጠፋ ጠብቀን።
ለኀሊናከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ዳግመኛ ከሰሜን እስከ ደቡብ በዓራቱም ማዕዝነ ዓለም የብርሃኑ ጸዳል ለሚንጸባርቀው ኀሊናህ ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
በዘባነ ኪሩቤል ላይ ዙፋንህን ዘርግተህ የተቀመጥህ አንተ ነህ። የአብን ፈቃድ ትፈጽም ዘንድ ከሰማየ ሰማያት ወደዚህ ዓለም የመጣህ አንተ ነህና ክቡር ምስጉን አምላክ ነህ።
ለአማዑቲከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
የኃጥኡን ሰው ውሳጣዊና አፍአዊ ሰውነቱን ለሚቀድሰው ንዑድ ክቡር ለሚሆን ውስጣዊ ገንዘብህና ለአማዑትህም ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
ከዚህ ዓለም ጥፋትና ጥል ፡ ጭቅጭቅና ንዝንዝ ሁሉ አድነኝ። በሰማይና በምድር፤ በባሕርና በየብስም ቢሆንም ያለአንተ ቸር ሰው ወዳጅ ንጉሥ የለምና።
ለሕንብርትከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
በአምሳለ ቅዱስ መስቀል ማዕተብነ፤ በግብረ መንፈስ ቅዱስ ለተማተበው ሕንብርትህ ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
አቤቱ ከችግርና ከፈተና አድነኝ፤ አባትህም በምስሐ ደብረጽዮን በሚያደርገው ታላቅ የምሳ ግብዣ ላይ ይዘኸኝ ግባ ከአንተ በቀር ሌላ የማውቀው ዘመድ የለኝምና።
ለሐቌከ
መድኃኔ ዓለም ሆይ፤
የሲኦልን በር የናሱን መዝጊያ ቀጥቅጠህና ሰባብረህ የብረቱንም ቁልፍ እንደ ሰም አቅልጠህ ነፍሳትን ከሲኦል በአወጣህበት ሰዓት መለኮታዊ ዝናርን ለታጠቀ ወገብህንና ኃይለአርያምን ለተጎናጸፉ አቍያጾችህም ሰላም እላለሁ።
ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤
መሐሪ ይቅር ባይ አንተ እግዚአብሔር እንደመሆንህ መጠን በምሄድበት መንገድ ሁሉ ቀናውን ጎዳና ምራኝ። የጽድቁንና ዕውነተኛውን መንገድ ፈጽሞ ለማወቅ አልችልምና።
ለአብራኪከ
111 viewsአሜን, edited 15:40