Get Mystery Box with random crypto!

ቀልድ በኢስላም የኢስላም የተፈጥሮ ሀይማኖት እንደመሆኑ ተፈጥሮአዊ የሆነውን የሰው ልጅ የመሳቅና | ሂዳያ - هداية - Islamic Guidance

ቀልድ በኢስላም

የኢስላም የተፈጥሮ ሀይማኖት እንደመሆኑ ተፈጥሮአዊ የሆነውን የሰው ልጅ የመሳቅና የመዝናናት ዝንባሌ አይጋፋም። እንደውም በተቃራኒው ህይወትን ደስተኛና ውብ የሚያደርጉ ነገሮችን ይቀበላል። ሙስሊሞች ተግባቢ፣ ተጫዋችና ፈገግተኛ እንዲሆኑም ያዛል። ፈገግታው የጨለመ፣ ህይወትን ድርቅ ባለና በጨለመ እይታ የሚመለከት ስብእናንም አይወድም።

የሙስሊሞች የመጀመሪያው ተምሳሌት ነብዩ ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም ናቸው። የተለያዩ ሀሳቦች፣ ጭንቀቶችና ሀላፊነቶች ቢኖርባቸውም ይቀልዱ ነበር። ይሁን እንጂ ከእውነት ውጪ አይናገሩም። ከባልደረቦቻቸው ጋር ሲኖሩም ተአምራዊና ተፈጥሮአዊ ህይወትን በአንድነት ገፍተዋል። ቀልዳቸውን፣ ጨዋታቸውንና ወጋቸውን ይጋሯቸዋል። ህመማቸውን፣ ትካዜያቸውንና ሀዘናቸውን ይካፈሏቸዋል። ስለመልእክተኛው ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም ሲያወሩ ዘይድ ኢብኑ ሳቢት አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና እንዲህ ይላሉ፡- “እኔ ጎረቤታቸው ነበርኩ። ወህይ ሲወርድባቸው ይልኩብኛል፤ እጽፍላቸዋለሁ።ስለዱንያ ስናወራ አብረውን ያወራሉ። ስለ አኼራ ስናነሳ አብረውን ያነሳሉ። ስለምግብ ካወጋን አብረውን ያወጋሉ።” (ጠበራኒይ ዘግበውታል።)

ሌሎች ባልደረባዎቻቸው እንደሚሉትም መልእክተኛው ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም ከማንም በላይ አስቂኝ ሰው ነበሩ። “ከንዙል ዑምማል” የተሰኘው መጽሀፍ ላይ አንደተጠቀሰው አንዳንዴ ባለቤቶቻቸውን ሲያጫውቱና ዚያዝናኑ እናስተውላለን። ወጎቻቸውንና ተረቶቻቸውን ያደምጧቸዋል። ቡኻሪይ ከእናታች አኢሻ የዘገቡትን የኡሙ ዘርዕን ሀዲስ እዚህ ላይ ዋቢ ማድረግ ይቻላል።

አንዲት ባልቴት ወደርሳቸው መጥታ “የአላህ መልእክተኛ ሆይ ጀነት እንድገባ ዱዓ አድርጉልኝ!!” ስትላቸው የእገሌ እናት ሆይ ጀነትኮ ባልቴቶች አይገቡም አሏት። ንግግራቸውን በግርድፉ ተረድታ ኖሮ ስቅስቅ ብላ አለቀሰች። ከዚያ ሊነግሯት የፈለጉት ወደወጣትነት ተቀይራ እንደምትገባ እንደሆነ ሲነግሯት ተረጋጋች። የጀነት ሴቶችን የሚያወሳውን ቀጣዩን የቁርአን አንቀጽ አነበቡላት፡-

إِنَّا أَنشَأْنَاهُنَّ إِنشَاءً فَجَعَلْنَاهُنَّ أَبْكَارًا عُرُبًا أَتْرَابًا

“እኛ አዲስ ፍጥረት አድርገን (ለእነርሱ) ፈጠርናቸው። ደናግሎችም አደረግናቸው። ለባሎቻቸው ተሽሞርሟሪዎች እኩያዎች (አደረግናቸው)።” (አል-ዋቂአ 56፤35-37)
ሀዲሱንም ቲርሚዝይና ሌሎችም ዘግበውታል።

አንድ ሰውም ግመል ላይ እንዲጭኑት ሲለምናቸው የግመል ግልገል ላይ እንጂ እንደማይጭኑት ነገሩት። “የአላህ መልእክተኛ ሆይ የግመል ግልገል ምን ይረባኛል!” ሲል ግራ በመጋባት ጠየቃቸው። እርሳቸውም “ማንኛዋም ግመል ከግልገል ውጪ ትወልዳለች!?” በማለት መለሱ። ይህን ሀዲስ ቲርሚዚይና አቡዳውድ አውርተውታል።

በመሠረቱ ሳቅና ጨዋታ እንደሚፈቀድ ጥርጥር የለውም። ነገር ግን የሚከተሉትን መስፈርቶች ማሟላቱ የግድ ነው፡-

1. በውሸትና በመሠረተ ቢስ ፈጠራ ሰዎችን የምናስቅበት መንገድ መሆን የለበትም። እዚህ ላይ “ኤፕሪል ዘፉል” የተሰኘውን ከምእራብያውያን የተወረሰ ጨዋታን ማንሳት ተገቢ ነው። መሠረት የሌላቸው የቅጥፈት ወሬዎችን በማውራት የሚሠራ በመሆኑ ኢስላም ይቃወመዋል። የአላህ መልእክተኛ ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም እንዲህ ይላሉ፡-

“ሰዎችን ለማሳቅ ብሎ የሚዋሽ ሰው ወየውለት! ወየውለት! ወየውለት! ወየውለት!!!” (አቡዳውድ፣ ነሳእይና ቲርሚዚይ ዘግበውታል።)
2. ሌላን ሰው የሚያንቋሽሽ ቀልድ መሆን የለበትም። የሰው ክብር ላይ ማላገጥ አይፈቀድም። ይህ የሚከለከለው ባለቤቱ ባልፈቀደ ጊዜ ነው። የሚሾፍበት ሰው ከፈቀደ ግን ችግር የለውም። አሏህ እንዲህ ብሏል፡-

يَا أَيُّهَا الَّذِينَ آمَنُوا لَا يَسْخَرْ قَوْمٌ مِّن قَوْمٍ عَسَىٰ أَن يَكُونُوا خَيْرًا مِّنْهُمْ وَلَا نِسَاءٌ مِّن نِّسَاءٍ عَسَىٰ أَن يَكُنَّ خَيْرًا مِّنْهُنَّ وَلَا تَلْمِزُوا أَنفُسَكُمْ وَلَا تَنَابَزُوا بِالْأَلْقَابِ بِئْسَ الِاسْمُ الْفُسُوقُ بَعْدَ الْإِيمَانِ وَمَن لَّمْ يَتُبْ فَأُولَٰئِكَ هُمُ الظَّالِمُونَ

“እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ወንዶች ከወንዶች አይቀልዱ። ከእነርሱ የበለጡ ሊኾኑ ይከጀላልና። ሴቶችም ከሴቶች (አይሳለቁ)። ከእነርሱ የበለጡ ሊኾኑ ይከጀላልና። ነፍሶቻችሁንም አታነውሩ። በመጥፎ ስሞችም አትጠራሩ።''

https://t.me/abu_abdurahman5