Get Mystery Box with random crypto!

ክፍል 3 ኢያቄምና ሐና ሆይ የልጃችሁን ልቅሶዋን የልቧንም መዘንጋት ታዩ ዘንድ ኑ፡፡ ከሔዋን እስ | ሊቀ መዘምራን

ክፍል 3

ኢያቄምና ሐና ሆይ የልጃችሁን ልቅሶዋን የልቧንም መዘንጋት ታዩ ዘንድ ኑ፡፡ ከሔዋን እስከ ፋኑኤል ልጅ እስከ ሐና ያላችሁ ሁላችሁ ቅዱሳት ሴቶች የድንግልን ልቅሶዋን ታዩ ዘንድ ኑ፣ አንድ ልጇ ሙቷልና፡፡ የለመለመ የሥጋ ሞት ሕንፃ የተጀመረበት የአቤል ተከታዩ፣ ከጎኑ የፈሰሰው ደም ሔዋንን ከጥፋት ያዳናት የተገደለ መድኃኒታችን ነው፡፡ የናቡቴ ጓደኛው የተገፋው መድኃኒታችን ነው፡፡ አቤል ስለሚስቱ ሞተ፡፡ ናቡቴም ስለ ወይኑ ቦታ ሞተ፡፡ መድኃኒታችን ግን በቀኙ ያነጻት ዘንድ ስለቤተክርስቲያን ሞተ፡፡ ነፍሳችሁን ይወስዷታልና መውረዱንም አላወቁምና ስለ ወገኖቹ ኃጢአት እስከ ሞት ደረሰ ብሎ ስለ እርሱ የተናገረ አባቱን እንስማው፡፡ ሙሴም እርሱን ያውቁት ዘንድ አላሰቡትም፣ በሚመጣበት ቀንም አላወቁትም አለ፡፡ ዕዝራ በባሕር ጥልቅ ያለውን ማወቅ እንዳይችሉ ወልድንም ማወቅ እንዲሁ ሆነባቸው አለ፡፡ ጳውሎስም ብታውቁትስ ኖሮ የክብርን ጌታ እግዚአብሔርን ባልሰቀላችሁት ነበር አለ፡፡

በመሰደድ፣ ያለምንም በደልም በፍርድ አደባባይ በመቆም መከራ መስቀልን በመሸከም አብነት የሆናችሁ ሰማዕታት ሁላችሁ ኑ የመድኃኔዓለምን የሞቱን ዕለት አስባችሁ በጋራ አልቅሱለት፡፡ ሁሉ የእርሱ ከእርሱ ለእርሱ ተፈጥሮ ሳለ በምድር ላይ ምንም ሳይኖረው ራሱን እንኳን የሚያስጠጋበት ቤት ሳይኖረው አብነት የሆናችሁ ባሕታውያንና መነኮሳት ሁላችሁ ኑ በዛሬዋ ዕለት ስለሞተው አምላካችሁ መሪር ዕንባን አልቅሱለት፡፡ ሕግ ጠብቆ፣ ሥርዓት አክብሮ፣ ነዳያንን በመመገብና ያዘኑትን በማጽናናት 33 ዓመት በምድር ላይ ኖሮ አብነት የሆናችሁ እናንት በዓለም ሆናችሁ ሕግ ጠብቃችሁ፣ አሥራት በኩራቱን አውጥታችሁ፣ ድሆችን በመርዳት የምትኖሩ ክርስቲያኖች ሁላችሁ የመድኃኔዓለምን የሞቱን ዕለት ታስቡ ኑ፡፡
‹‹የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሎአልና›› ብሎ ቅዱስ ጴጥሮስ እንደጻፈልን (1ኛ ጴጥ 2፡21) እርሱ ንጹሕ ባሕርይ ሲሆን ወደ መጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ ዘንድ ወደ ዮርዳኖስ በመሄድ ለተጠመቅን ለእኛ ለተነሣሕያን ለሁላችን አብነት የሆነን መድኃኒታችን ስለእኛ ሞቷልና ሞቱን እናስብ ዘንድ ኑ በቤቱ ተሰብስበን እናልቅስለት፡፡ መታሰያውንም እናድርግለት፡፡ ጌታችን ሞቶ ተቀብሮ ካረገ በኋላ ለቅዱሳን ሐዋርያትና ለቅዱሳን አባቶቻችን ለእነ አቡነ መባዓ ጽዮን፣ ለእነ አቡነ ዘርዐ ቡሩክ እንደነገራቸው የሞቱን መታሰቢያ የሚያደርግ ኃጠአተኛ እንኳ ቢሆን ሲኦልን አያያትም፡፡ የመድኃኔዓለምን የሞቱን መታሰቢያ የሚያድርግ ቢኖር ሲኦል ራሷ አፍ አውጥታ ‹‹ይህችን ነፍስ ወደኔ አታምጡብኝ›› ብላ ትጮሃለች እንጂ ችላ አትቀበለውም፡፡

የጌታችን ወዳጆቹ ዮሴፍ ኒቆዲሞስ በድርብ በፍታና በመቶ ወቄት ሽቱ ገንዘው በሐዲስ መቃብር ሊቀብሩት ቢሉ ጌታችን ያን ጊዜ ዐይኑን ክፍቶ ‹‹በሰውነቴ መዋቲ ብሆን በመለኮቴ ሕያው ነኝ እንጂ ምነው እንደ እሩቅ ብእሲ ዝም ብላችሁ ትገንዙኛላችሁን?›› አላቸው፡፡ ይህን ጊዜም ዮሴፍ ኒቆዲሞስ በታላቅ ድንዳጤ ሆነው ‹‹አቤቱ ጌታችን ሆይ! እንግዲያስ ምን እያልን እንገንዝህ?›› አሉት፡፡ መድኃኒታችንም እንዲህ እያላችሁ ገንዙኝ አላቸው፡- ‹‹ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት ዘተወልደ እማርያም እምቅድስት ድንግል ተሣሃለነ እግዚኦ፡፡ ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት ዘተጠምቀ በዮርዳኖስ ወተሰቅለ ዲበ ዕፀ መስቀል ተሣሃለነ እግዚኦ፡፡ ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት ዘተንሥአ እሙታን አመ ሣልስት ዕለት ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት ወነበረ በየማነ አቡሁ ዳግመ ይመጽእ በስብሐት ይኰንን ሕያዋነ ወሙታነ ተሣሃለነ እግዚኦ› እያላችሁ ገንዛችሁ ቅበሩኝ አላቸው፡፡›› ከዚህም በኋላ መድኃኒታችን ለወዳጆቹ ለ12ቱ ሐዋርያት፣ ለ72ቱ አርድእት፣ ለ36ቱ ቅዱሳት አንስት ‹‹እስከ ሦስት ቀን እነሣላችኋለሁ እዘኑ አልቅሱ፣ እህል ውኃ አትቅመሱ በሏቸው›› ብሎ ለዮሴፍና ለኒቆዲሞስ አክፍሎት አስተማራቸው፡፡

ዳግመኛም መድኃኔዓለም ክርስቶስ ከዕርገቱ በኋላ ለቅዱሳን ሐዋርያት የሞቱን መታሰቢያ እንዲያደርጉ ነግሯቸዋልና፡፡ ሕማሙንና ሞቱንም እንዲዘክሩ አዟቸዋልና አሁንም ያንን ሁሉ የመድኃኔዓለምን ሞቱን ያላሰበና የሞቱን መታሰቢያ በዓል ያላከበረና እርሱንም የማይወደው ቢኖር ዕድል ፈንታው ጽዋ ተርታው ከአይሁድ ጋር ነው፡፡

የአምላካችንን የመድኃኔዓለምን ሞቱን በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ተባብረን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ከእርሱ ለመተባበር ያብቃን!

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት እና #ከገድላት_አንደበት)
ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ልጆች
                •➢ ሼር // SHARE

  •✥• @Z_TEWODROS •✥•
  •✥• @Z_TEWODROS •✥•
•✥• @Z_TEWODROS •✥•