2022-03-16 05:36:15
ከባለቤቴ ጋር በትንሽ ነገር ላይ ተከራከርን። አለመግባባቱ እየተካረረ ሲሄድ “አንቺ እዚህ ቤት ውስጥ ከኔ ጋር ኖረሽም ሆነ ሳትኖሪ ምንም የሚፈጠር ነገር የለም። አንዲት ሰራተኛ ባመጣ አንቺ ከምትሰሪው በበለጠ አሳምራ ሁሉንም ነገር መስራት ትችላለች” አልኳት። እንባ ባቀረሩ አይኖችዋ አየት አድርጋኝ ወደ ሳሎን ቤት አመራች። እኔም ወደ መኝታ ክፍሌ አምርቼ ተኛሁ። በመነገው ባለቤቴ ሞታ ተገኘች የቀብር ስነስርአቱ ከተፈጸመ በኋላ ከሚያስተዛዝኑኝ ሰዎች ጋር ሆነን ወደ ቤት ተመለስን። ለተወሰኑ ቀናት ሰዎች ከጎኔ ስላልጠፉ ምንም አልመሰለኝም ነበር። ከቀን ቀን የሚያስተዛዝነኝ ሰው እየተመናመነ ሲመጣ ብቸኝነት ተሰማኝ፡ ቤቱ የሚውጠኝ መሰለኝ። እንደ ምንም ብዬ አልጋዬ ላይ ጋደም አልኩ። ባለቤቴ ትተኛበት የነበረውን
ቦታ ባዶ ሆኖ ሳገኘው ለመጀመሪያ ጊዜ የሀዘን ስሜት ተሰማኝ።
ከእንቅልፌ ስነቃ የስራ ሰአት ረፍዷል። ለምን እንዳልቀሰቀሰችኝ ልቆጣት ዞር ስል ለካ
ከእንግዲህ ላትመለስ ጥላኝ ሄዳለች። ከተጋባን ጀምሮ ቁርስ ደርሷል እንዳይረፍድብህ እያለች ለስራ
የምትቀሰቅሰኝ እሷ ነበረች። ቁርስ ሳልበላ ወደ ስራ ቦታዬ አመራሁ። ቀኑ በዝግታ እያለፈ ቢሆንም የሆነ ነገር ቅር እንዳለኝ ይታወቀኛል። ምን ይሆን? ስል አሰብኩ። የባለቤቴ የስልክ ጥሪ ነው።
ሁሌም ስራዬ ላይ ሆኜ ትደውልልኝ ነበር።
“ውዴ እንዴት እንደናፈከኝ ልነግርህ አልችልም ደግሞ እንዳትቆይ በጊዜ እንድትገባ! ” ትለኛለች እንዲህ ስትለኝ
ልትቆጣጠረኝ ፈልጋ እየመሰለኝ እናደድባት ነበር። ዛሬ ግን ድምጿ ናፈቀኝ። ሰአቱ ደርሶ ወደ ቤቴ ተመለስኩ። ያኔ በር ላይ ቆማ በፈገግታ ትቀበለኝ ነበር። በሰላም
ነው እንዲህ ያመሸኸው? እያለች በፍቅር አይን አይኔን ታየው ነበር። ዛሬ ግን ያ ነገር የለም።
ብቸኝነቱና ጭለማው ያስፈራሉ። ኦ አምላኬ!!! ለካ እስከዛሬ በዚህ በሚያስፈራ በዝምታ የተዋጠ ቤት ውስጥ ብቻዋን ሆና ነበር የምትጠብቀኝ። የኔን ፍላጎት እንጂ የሷን አንድም ቀን ከግምት ውስጥ አስገብቼ አላውቅም። አሳዘነችኝ። ያኔ ነው
ማሰብ የነበረብህ እንጂ ጊዜው ካለፈ በኋላ ማዘን ምን ይጠቅማል ? ስል ራሴን ወቀስኩ። አምላኬ በድያታለሁ ይቅር በለኝ! በዚህ ሁኔታ ላይ እያለሁ ክፉኛ ታመምኩ።
ከአጠገቤ ሆና የምታበረታታኝ፡ በእጆችዋ
እያሻሸች ፍቅርን የምትለግሰኝ፣ የምታጽናናኝ፣ የምታስታምመኝ እሷ ነበረች። ዛሬ ግን የለችም! እንዴት ይከብዳል! ይህችን መልካም ሴት በከፍተኛ ሁኔታ ስበድላት መኖሬ ከነከነኝ፡ እራሴን ጠላሁ፡ ስቅስቅ ብዬ እያለቀስኩ እያለ ድንገት "የኔ ውድ ረፍዷል ተነስ" የሚል ድምጽ ከእንቅልፌ አነቃኝ። ለካስ ይህ ሁሉ ጉድ
የሚታየኝ በህልሜ ነበር።
በድንጋጤ ተውጬ አጠገቤ ሆና በፍቅር አይን አይኔን የምታየኝን ባለቤቴን እቅፍ አደረግኳት። እግዚአብሔር ይመስገን! ውድዋ ባለቤቴ በሕይወት አለችልኝ። ከዚህ ቀደም ለበደልኳት ሁሉ ይቅርታ ታደርግልኝ ዘንድ ተማጸንኳት። ከእንግዲህ ላላስከፋት ለራሴ ቃል ገባሁ።
.
ነገሮች ካለፉ በኋላ ከመጸጸት አሁኑኑ ከአንተ
የሚጠበቀውን ነገር ለማድረግ ጥረት አድርግ። የሰው ልጅ በተፈጥሮው ምሉእ አይደለም። የተወሰኑ ድክመቶች ይኖሩበታል። ያንን ድክመቱን እንደማጥቂያ መሳሪያ እየተጠቀምክ ይበልጥ አታቁስለው። በተለይ የሕይወት አጋርህ በሆነችው ባለቤትህ ላይ ልቧን የሚሰብሩ ቃላትን ከመጠቀም ተቆጠብ።
239 views02:36