Get Mystery Box with random crypto!

​​#ነሐሴ_26 #አቡነ_ሃብተ_ማርያም_ጻድቅ እኒህ ጻድቅ የሃገራችን ኮከበ ገዳም ናቸው:: 'ጽድ | ውዳሴ ማርያም/wdasemaryam

​​#ነሐሴ_26
#አቡነ_ሃብተ_ማርያም_ጻድቅ

እኒህ ጻድቅ የሃገራችን ኮከበ ገዳም ናቸው:: "ጽድቅና ትሩፋት እንደ ሃብተ ማርያም" እንዲሉ አበው:: ባሕር ከሆነ ጣዕመ ሕይወታቸው ጥቂቱን ለበረከት እንካፈል::

ጻድቁ መካነ ሙላዳቸው ሽዋ (የራውዕይ) ውስጥ ሲሆን አባታቸው ፍሬ ቡሩክ እናታቸው ደግሞ ቅድስት ዮስቴና ትባላለች:: በተለይ ቅድስት ዮስቴና እጅግ ደመ ግቡ ምጽዋትን ወዳጅ ቡርክት ሴት ነበረች:: እንዲያውም ከጻድቁ መወለድ በፊት መንና ጭው ካለ በርሃ ገብታ ነበር::

ግን የበቃ ግኁስ አግኝቷት "ከማሕጸንሽ ደግ የሥላሴ ባርያ አለና ተመለሽ" ብሏት እንደ ገና ተመልሳለች:: ጻድቁን ወልዳ አሳድጋም እንደ ገና መንና በተጋድሎ ኑራ 7 አክሊላትን ተቀብላ ዐርፋለች::

ወደ ጻድቁ ዜና ሕይወት ስንመለስ አቡነ ሃብተ ማርያም ገና ሕጻን እያሉ ከእናታቸው ጋር ቆመው ሲያስቀድሱ "እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ" ሲባል ይሰማሉ:: ይሕችን ጸሎት በሕጻን አንደበታቸው ይዘው ሌሊት ሌሊት እየተነሱ "ማረን እባክህን?" እያሉ ይሰግዱ ነበር::

የ5 ዓመት ሕጻን እንዲህ ሲያደርግ ማየቱ በእውነት ይደንቃል:: ትንሽ ከፍ ብለው በእረኝነት ሳሉም ፍጹም ተሐራሚና ጸዋሚ ነበሩ:: ጸጋው ስለ በዛላቸውም ልጅ ሆነው ብዙ ተአምራትን ሰርተዋል:: የፈጣሪውን ስም ያቃለለውን አንድ እረኛም በዓየር ላይ ሰቅለው አውለውታል::

ከዚያ ግን ለአካለ መጠን ሲደርሱ ወደ ት/ቤት ገብተው መጻሕፍትንም አጥንተው መንነዋል:: በአባ መልከ ጼዴቅ እጅ ከመነኮሱ በሁዋላ የሠሩትን ትሩፋትና የነበራቸውን ተጋድሎ ግን የኔ ብጤ ደካማ ሰው ሊዘረዝረው አይችልም::

ባሕር ውስጥ ሰጥመው 500 ጊዜ ይሰግዳሉ::
በየቀኑ 4ቱን ወንጌልና 150 መዝሙረ ዳዊትን ይጸልያሉ:: (መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ታላቅ ጸሎት ነው)
በ40 ቀናት ቀጥሎም በ80 ቀን አንዴ ብቻ ይመገባሉ::
ምግባቸው ደግሞ ሣርና ቅጠል ብቻ ነው::
በየዕለቱ ያለ ማስታጐል ማዕጠንት ያሳርጋሉ:: (ካህን ናቸውና)
ዘወትር በንጽሕና ቅዱስ ሥጋውን ይበላሉ ክቡር ደሙን ይጠጣሉ::
በፍጹም በልባቸው ውስጥ ቂምን መከፋትን አላሳደሩም::

በእነዚህና በሌሎች ትሩፋቶቻቸው ደስ የተሰኘ ጌታም ለጻድቁ የእሳትና የብርሃን ሠረገላን ሰጥቷቸው በዚያ እየበረሩ ኢየሩሳሌም ይሔዱ ነበር:: ከብዙ የተጋድሎ ዘመናት በሁዋላም የክብር ባለቤት መድኃኒታችን ክርስቶስ አዕላፍ መላእክትን አስከተትሎ መጥቶ አላቸው::

"1.ስለ እኔ ረሃብና ጥምን ስለ ታገስክ
2.ስለ ምናኔሕ
3.ስለ ተባረከ ምንኩስናህ
4.ስለ ንጹሕ ድንግልናህ
5.ቂምና በቀልን ስላለመያዝህ
6.ስለ ንጹሕ ክህነትህና ማዕጠንትህ
7.ቅዱስ ወንጌልን በፍቅር ስለ ማንበብህ 7 አክሊላትን እሰጥሃለሁ::"

"በሰማይም ከመጥምቁ ዮሐንስ ጐን 500 የእንቁ ምሰሶዎች ያሉበትን አዳራሽ ሰጥቼሃለሁ:: በስምህ የሚለምኑ በቃል ኪዳንህ የሚማጸኑትንም ሁሉ እንድምርልህ 'አማንየ! በርእስየ!' ብዬሃለሁ" አላቸው::

ቅዱሳን መላእክትም "ሃብተ ማርያም ወንድማችን" ሲሉ አቀፏቸው:: ጌታ ግን በዚያች ሰዓት አንድም ሦስትም ሆኖ ታያቸውና አቅፎ 3 ጊዜ ሳማቸው:: ከፍቅሩ ጽናትም የተነሳ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለየች:: በዝማሬም ወሰዷት::

አምላከ አበው ወሰማዕት ጣዕመ ፍቅራቸውን ክብራቸውን: ጸጋ በረከታቸውንም ይክፈለን::

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
@wdasemaryam