2022-08-12 07:55:40
#የዓርብ_ውዳሴ_ማርያም_ትርጓሜ
ድንግል ሆይ! የደናግል ኹሉ መመኪያቸው አንቺ ነሽ፡፡ ከእናንተ መካከል “መመኪያነቷ እንዴት ነው?” ብሎ የሚጠይቅ ሊኖር ይችላል፡፡ እኛም እንዲህ ብለን እንመልስለታለን፡-
፩ኛ) ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ሲል ይመልስልናል፡- “ወበከመ አውፅአ ብእሲ ብእሲተ ዘእንበለ ብእሲት ከማሁ አውፅአት ብእሲት ብእሴ ዘእንበለ ብእሲ ወሀሎ ዕዳ ላዕለ ትዝምደ አንስት፤ ወበእንተዝ ኮነት ፈዳዪተ ዕዳሃ ለሔዋን - ለወንዶች የሚከፈል ዕዳ በሴቶች ላይ ነበረ፤ ያለ እናት ሔዋን ተገኝታ ነበርና፡፡ ስለዚህም የሔዋንን ብድራት ለአዳም ትከፍለው ዘንድ ድንግል ያለ ዘርዐ ብእሲ (ያለ ወንድ ዘር) ክርስቶስን ወለደችው፡፡ አዳም ያለ እናት ሔዋንን ስላስገኘ እንዳይመካ ድንግል ያለ አባት ክርስቶስን ወለደችው፡፡ ድንቅ በሚኾን አንድነት ይህ አንድ የፍጥረት እኩልነት ይታወቅ ዘንድ” /ሃይ.አበ.፷፮፥፳፱/፤
፪ኛ) ቀድሞ ወንዶች ሴቶችን በእናንተ ምክንያት ከገነት ወጣን እያሉ ርስት አያካፍሏቸውም ነበር፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ፡- “ብእሲ ወብእሲት አሐደ እሙንቱ በክርስቶስ - ወንድም ሴትም የለም፤ ኹላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና” ብሎ እስኪያስተምር ድረስ /ገላ.፫፡፳፰/ በሔዋን ምክንያት ከገነት ብትወጡ በእመቤታችን ምክንያት ገነት መንግሥተ ሰማያት ገብታችሁ የለምን? ብለው የሚመኩ ኹነዋልና፤
፫ኛ) ደግሞ ለደናግላን አስበ ድንግልናቸውን (የድንግልናቸውን ዋጋ) ስለምታሰጣቸው ሊቁ “ምክሆን ለደናግል” ብሏታል፡፡
ቅድመ ዓለም የነበረ እርሱ ሰው ኹኗልና (ካንቺ ተወልዷልና) የእኛን ሥጋ ነሥቶ የርሱን ሕይወት ሰጥቶ ከርሱ ጋራ አስተካከለን፡፡ በቸርነቱ ብዛት እንድንመስለው አደረገን /ፊል.፫፥፲-፲፩/፡፡ ከብዙ ሴቶች አንቺ ትበልጫለሽ፡፡ ክብር የክብር ክብር ካላቸው ከብዙ ሴቶች አንቺ ትበልጫለሽ /ሉቃ.፩፥፳፰/፡፡ ንጉሥ በከተማው እንዲኖር ዘጠኝ ወር ካምስት ቀን ማኅፀንሽን ዓለም አንድርጎ ኖሮብሽልና አምላክን የወለድሽ ድንግል ማርያም ሆይ! ልዑል እግዚአብሔር የከተመብሽ ረቂቅ ከተማ ነሽ፡፡ በኪሩቤል በሱራፌል አድሮ የሚኖረው እርሱን በማኽል እጅሽ ይዘሽዋልና ልዑል እግዚአብሔር የከተመብሽ ረቂቅ ከተማ ነሽ፡፡ በቸርነቱ ብዛት ፍጥረቱን ኹሉ በዝናም አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ የሚመግበው እርሱ ጡትሽን ይዞ ጠባ፡፡ አንድም ለሰውን (ለመንፈሳውያን) ኹሉ ሥጋውን ደሙን ሰጥቶ የሚመግበው እርሱ ጡትሽን ይዞ ጠባ፡፡ ይኸውም ፈጣሪያችን መድኃኒታችን ነው፡፡ እንሰግድለት እናመስግነውም ዘንድ በሐዲስ ተፈጥሮ በጥንተ ተፈጥሮ ፈጥሮናልና ለዘለዓለሙ ይጠብቀናል /ዮሐ.፮፥፴፯/፡፡ ሰጊድ (አምልኮ) ከሚገባው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፬. ድንግል ማርያም ዕፍረተ ምዑዝ (መዓዛው የጣፈጠ) የተባለ ጌታችንን የወለደች ሙዳየ ዕፍረት (የሽቱ መኖርያ) /፩ኛ ሳሙ.፲፥፩ አንድምታው/፤ ዳግመኛም የማየ ሕይወት (የሕይወት ውኃ የክርስቶስ) ምንጭ ናት /መኃ. ፬፥፲፪ አንድምታው/፡፡ የማኅፀኗ ፍሬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰውን ኹሉ አድኗልና፡፡ ከእኛ መርገመ ሥጋን መርገመ ነፍስን አጠፋልን፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ፡- “በመስቀሉ ደም ሰላም አድርጎ በምድር ወይም በሰማያት ያሉትን ኹሉ ለራሱ እንዲያስታርቅ ፈቅዶአልና” እንዲል /ቈላ.፩፡፲፱-፳/ በመካከል ኾኖ በመስቀሉ አስታረቀን፡፡ ልዩ በኾነ ትንሣኤውም ሰውን ዳግመኛ ወደ ገነት መለሰው፡፡ ከእናንተ መካከል፡- “ልዩ በኾነ ትንሣኤ ሲል ምን ማለቱ ነው?” ብሎ የሚጠይቅ ሊኖር ይችላል፡፡ እኛም እንዲህ ብለን እንመልስለታለን፡- ከእነ አልዓዛር ትንሣኤ የተለየ መኾኑን ለማሳየት ነው፡፡ ምክንያቱም፡-
፩ኛ) እነ አልዓዛር አስነሺ ይሻሉ፤ እርሱ ግን “ላኖራት ሥልጣን አለኝ፤ ደግሞም ላነሣት ሥልጣን አለኝ” ብሎ እንደተናገረ /ዮሐ.፲፥፲፰/ የተነሣው በገዛ ሥልጣኑ ነውና፡፡ በተለያየ ሥፍራ “አብ አንሥኦ (አብ አስነሣው)፤ መንፈስ ቅዱስ አንሥኦ (መንፈስ ቅዱስ አስነሣው)” ቢልም አንድ ነው፡፡ ምክንያቱም ዕሪናቸውን መናገር ነውና፡፡
፪ኛ) የእነ አልዓዛር ትንሣኤ በብሉይ ሥጋ ነው፤ የእርሱ ግን በሐዲስ ሥጋ ነው፡፡
፫ኛ) የእነ አልዓዛር ትንሣኤ ሞትን ያስከትላል፤ የእርሱ ግን ሞትን አያስከትልም፡፡
፬ኛ) የእነ አልዓዛር ትንሣኤ ትንሣኤ ዘጉባኤን ይጠብቃል፤ የእርሱ ግን አይጠብቅምና፡፡
አዳምን ዳግመኛ ወደ ገነት ከመለሰ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፭. አንዳንድ ተረፈ ንስጥሮሳውያን እንደሚሉት ንጽሕት ድንግል ማርያም ላቲ ስብሐትና “ወላዲተ ሰብእ” አይደለችም፤ የታመነች አምላክን የወለደች ናት እንጂ፡፡ የመናፍቃን መዶሻ የተባለው፣ በተለይም የቅድስት ድንግል ማርያምን ወላዲተ አምላክነት የካደውን ንስጥሮስን የረታው ቅዱስ ቄርሎስ እሳተ መለኮት አምላክን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅፀኗ የተሸከመች፣ በጀርባዋ ያዘለች፣ በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ የፈጠረውን ፍጥረት የሚመግበው አማኑኤልን የድንግልና ጡቶቿን ወተት የመገበችውን የወላዲተ አምላክን ክብር ያልተረዱትን ንስጥሮሳውያን መናፍቃንን ሲወቅስ “ወለዛቲ እንተ መጠነዝ ዐባይ ጾረት መለኮተ እፎ ይከልእዋ እምክብራ ለወላዲተ አምላክ ወላዲተ አምላክኬ ቅድስት ድንግል - ይኸንን ያኽል ታላቅ ኾና መለኮትን የተሸከመችቱን የአምላክ እናት ክብርን እንደምን ይነፍጓታል፤ ይከለክሏታል፡፡ የአምላክ እናት ማለት ድንግል ማርያም ናታ” በማለት የተሰጣትን ክብር በማድነቅ አስተምሯል /ተረፈ ቄርሎስ/፡፡
እንዲህም ስለኾነ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የታመነች የምሕረት አማላጅ ናት፡፡ የዚህ ዓለም ሰዎች አማልዱኝ ቢባሉ ነገር አጽንተው ይመለሳሉ፤ እርሷ ግን “ማእምንት ሰአሊተ ምሕረት - የታመነች የምሕረት አማላጅ ናት” /ዮሐ.፪፥፩-፲፩/፡፡ ሰአሊተ ምሕረት ሆይ! ኃጢአታችንን ያስተሠርይልን ዘንድ ከልጅሽ ዘንድ አማልጅን፡፡ ኃጢአታችንን ከሚያስተሠርይልን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
ሊንኩን ተጭነው ሙሉውን ያንብቡ
https://mekrez.blogspot.com/2013/08/blog-post_1585.html?m=1
@beteafework @beteafework
@beteafework @beteafework
@beteafework @beteafework
300 views04:55