Get Mystery Box with random crypto!

ዐማራነት ስንል ሰው-ነት፣ ህግነት እና ህገመንግስትነት ማለታችን ነው። ይህን ስንል ዐማራ፣ የተጎዳ | Tadele Tibebu - ታደለ ጥበቡ

ዐማራነት ስንል ሰው-ነት፣ ህግነት እና ህገመንግስትነት ማለታችን ነው። ይህን ስንል ዐማራ፣ የተጎዳ ሰው ሲያገኝ እኔን ይድፋኝ ብሎ የሰውን ችግር እንደራሱ የሚያይ የሞራል ልዕልና ያለው ህዝብ ነው።

"እንኳን ሰው ወፍ አለምዳለሁ" የሚል እንግዳ ተቀባይ (hospitable)፣ ለሃይማኖቱ ቀናኢ፣ ሠላማዊ፣ ፍቅር፣ ለጋሽ፣ ቸር፣ አቃፊ፣ አልቦና ጠምቆ የሚያጠጣ፣ አምርቶ አገር የሚቀልብ፣ ፈትሎና ሸምኖ አገር የሚያለብስ በጣም የዳበረ ባህል (rich culture) ያለው ህዝብ ነው። እንኳን ለሀገርና ለወገን ደሙን እያፈሰሰ አጥንቱን እየከሰሰ ላለ ሠራዊት ቀርቶ በዐማራ ባህል መሽቶበት ማረፊያ የጠየቀ እንግዳ ወይም መንገደኛ የእግዚአብሔር እንግዳ ነው። የደከመው ያርፍበታል፣ የተጠማ ይጠጣበታል፣ የተራበ ይበላበታል፣ የታረዘ ይለብስበታል፣ የተከዘ ይጽናናበታል። ከአልጋ ወርዶ፣ እልፍኝ ለቆ እንግዳ መቀበል የዐማራ ህዝብ ማህበራዊ ቅርሱ ነው። ዶናልድ ሌቪን Wax and Gold በተባለው መጽሐፉ ስለ ዐማራ እንግዳ ተቀባይነትና አክባሪነት ሚከተለውን ጽፏል፣

"በዐማራ ዘንድ የእግዜር እንግዳን ተቀብሎ ከራስ በላይ አስተናግዶ ማሳደር የተለመደ ማኅበራዊ መገለጫ ነው። የእግዜር እንግዳ ሲመጣ እግሩን ይታጠባል፤ ቡና ይጠጣል፤ ጠላ ይጠጣል፤ ጥሩ ምግብ ይበላል፤ በባለቤቶቹ መኝታ ላይ ተነጥፎለት እስከመተኛት መስተንግዶ ይደረግለታል። እሱ ብቻ ሳይሆን የጭነት ወይም የኮርቻ ከብት ይዞ እንደሆን እንክብካቤን ያገኛሉ። እንግዳ ወዳድ በመሆናቸው 'ብሉ እንጅ፤ ጠጡ እንጅ' የሚሉ አገላለጾችን ይጠቀማሉ። ይሄ መስተንግዶ ለዘመድ፣ ለወዳጅ ለጓደኛ ለማንኛውም ሰው ሊደረግ የሚችል ነው። (Wax and Gold፣ 246)

ዐማሮች እጅግ በጣም እንግዳ ወዳድ በመሆናቸው ሲያስተናግዱ እንግዳ በልቶ የጠገበ፤ ጠጥቶ የረካ ስለማይመስላቸው በፈገግታ፣ በትህትና፣ በፍቅርና በአክብሮት "አፈር ስሆን፣ ብሉ እንጅ፣ ጠጡ እንጅ" የሚል አገላለጽ ይጠቀማሉ። ይህም የመንፈሳዊ ሥልጣኔ (moral civilization) መገለጫ ነው።

የዛሬ ዓመት የሀገር መከላከያ ሠራዊት ከትግራይ ሲወጣ የዐማራ ሕዝብ እጅ እየነሳ፣ እያጎረሰ፣ እየዳበሰ፣ ሲቀበላቸው እንባቸውን መቆጣጠር አቅቷቸው ሲያለቅሱ አይተናል።

ዐማራ ጀግናን ማጀገን ያውቅበታል እና ክብር ለሚገባው ክብር ሰጥቷል፡፡ ፍቅር ለሚገባው ፍቅር አሳይቷል፡፡ በመከራውም ቀን አብሮት ሊዘልቅ ቃሉን አጽንቷል፡፡ ዐማራ በልኩ ተገኘ። ደግነቱን አሳዬ፡፡ ጀግናው ወታደርም ስለ ፍቅር አንጀቱ ተላወሰ፡፡ እንባ ከዓይኖቹ አፈሰሰ፡፡

በወቅቱ አንድ የመከላከያ ሠራዊት አባል በውስጥ መስመር እንዲህ የሚል መልእክት ነበር የላከልኝ፤

"የደቡብ ተወላጅ ነኝ። በትግራይ ምድር ለግዳጅ ከ6 ወር በላይ ቆይቻለሁ። በእነዚህ ወራቶች ራሱ ህዝቡ ወግቶናል፣ በውሃ እና በምግብ ላይ መርዝ እየጨመሩ ገድለውናል። በተሳሳተ መንገድ እየመሩ አስከብበውናል። ከዛ ሁሉ ከባድ ትግል ወጥተን ወደ አማራ ክልል ስንገባ ህዝቡ በነቂስ ወጥቶ በመንገድ ዳር ቆሞ እያጨበጨበ ተቀበለን። ምሳ ወይንም ቁርስ ልንበላ በወረድንበት ሁሉ ህዝቡ በየቤቱ እንጀራ እያዋጣ ነው የመገበን። በትግራይ ምድር ከባዱን ፈተና ያሳለፉ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባላት ውስጣቸው ተነክቶ ሲያለቅሱ አይቻለሁ። በርግጥ ቢያለቅሱ አይገርምም። ከኋላው ሲወጋ የነበረ ሠራዊት፣ እንኳን ደህና መጣችሁ፣ አፈር ስሆን፣ በሞቴ ብሉልኝ ጠጡልኝ
ሲባል ባያለቅስ ነበር የሚገርመው። ባጠቃላይ የዐማራ ህዝብ ላደረገልን አቀባበል፣ ግብዣና ላሳየን ፍቅር እኔና ጓደኞቼ ማመስገን እንፈልጋለን። ይሄን መልእክት አደራ አድርስልን"

ዐማራ ዛሬም ለወገን ጦር ደጀንነቱን አጠናክሮ ቀጥሎበታል። ሩሲያዊው እስክንድር ቡላቶቪች እንዳለው "ዐማራን እግዚአብሔር ይሁነው"