2022-06-14 00:51:36
#ጥያቄ ፦
ጠያቂያች ወለተ ጊዮርጊስ እንዲ የሚል ሀሳብ አዘል ጥያቄ በውስጥ መሰር ወርወር አድርገውልናል:: ወቅቱ አንተ የእነ እንታ ዘር አንተ የእነ እንትና ዘር እየተባባሉ እርስ በእርሳቸው በጎራ የሚሻኮቱበት እንደሠሆኑ መጠን ዘረኝነትን አስመልክታችሁ አጠር ያለህ ትምህርት ብታስተምሩን የሚል ነው::
ለጠያቂያችን ለወለተ ጊዮርጊስ የሕይወትን ቃል ያሰማልን እያልን ከክታበ መለከት ካገኘናት ጽሁፍ ለጊዜው ትሆነን ዘንድ ይዘንላችሁ ቀርበናል ተከታተሉን::
( ዘር መቁጠርና መዘዙ )
የሰው ዘር መገኛ መሠረቶች አዳምና ሔዋን መሆናቸውን ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል:: እኛ የሰው ዘሮች በምልዐት የሰፈርንባት ከመነሻችን ከአዳም መጀመሪያ ሆነን እግዚአብሔር በሰጠን ቡራኬ እየበዛን እስካለንበት ዘመን ደርሰናል::በዘመናችን በተለይ በተለይ በቅድስት ኢትዮጲያ ዲያቢሎስ ያሰለጠናቸው ሰዎች አንደበታቸውን በተቆጣጠረው መንፈስ እየተመሩ የመለያየት መንፈስ እንዲፈጠር በማድረግ ብዙ ጥፋቶችን እየፈጸሙ ነው በዚህ መዘዝ በከንቱ የሚፈሰው ደም ለወደፊቱ አጥፊዎቹ ከስህተታቸው ካልታረሙ የሚያፈሱት የደም ጎርፍ እነርሱኑ አጥፊዎቹን እንደ ባህር ማስጠሙ አይቀርም::
ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ በመለያየት ላይ የነበሩትን የግሪክና የአይሁድ ሰዎችን ሲገስጽ እንዲ ብሏል:: "አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም ባርያ ወይም ጨዋ ሰው የለም ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና" ገላ3÷28
እንግዲህ የተቀደሰው ሐዋርያ እንደነገረን እንኳን ኢትዮጲያዊ ዜጋ ቀርቶ አይሁዳዊና የግሪክ ሰው መላው የሰው ዘር የተፈጠረው በእግዚአብሔር ፈቃድና ቸርነት ሰለሆነ እንደ አንድ ሰው ተቆጥሮ በሰላምና በስምምነት በፍቅር ተከባብሮ በአንድነት መኖር ይጠበቅበታል::
ይህ ጥቅሙ ለህሊና ጤንነት ነው :: በጠብና ባለ መስማማት ምን ትርፍ ይገኛል ::ለመሆኑ በጤነኛ አእህምሮ ስናስበው በተፈጥሮ እኛን የሚመስለውን ሰው በአሰቃቂ ሁኔታ በስለት እንዲወጋ ማድረግ ፣ ማፈን ፣ ዐይኑን እጁን እግሩን ስንቆራርጠው ድርጊቱን ለመፈጸም የገፋፋንን መንፈስ እንዴት ለመመርመር ተሳነን ? እንዴትስ ይህን ድርጊት መፈጸም ሰውነታችን ሊቀበለው ቻለ ድርጊቱንስ ስንፈጽመው ሰው እንኳን አጠገባችን ባይኖር ህሊና የሚባለውን ዳኛ እንዴት ሳናፍረው ቀረን? ከዚህ በላይ የፈጠረንን አምላክ እንደምን ችላ አልነው? ማንም ሰው የጭካኔ ሥራን ለመሥራት ሲነሳሳ ሰውነቱን ወይም ምንነቱን ስለረሳ ነው ወደ ጭካኔ አሰራር የሚገባው የትኛውም ሰው ክፉ ተግባርን በሌሎች ሲፈጽም ድርጊቱን በገዛ ሰውነቱ ላይ እንደፈጸመ ይቆጠራል:: ምክንያቱም ወገኑን የሚቆራርጥበት ስለት ሰውነቱን ቢወጋው ጉዳቱ እንደሚሰማው አከራካሪ አይደለም::
ስለዚህ ሚዛናዊ አእምሮ ማጣት ካልሆነ በስተቀር በጭካኔ ወንድሙ ወይም እህቱ ላይ ስለቱን ሲያሳርፍ በገዛ ሰውነቱ ላይ እዳሳረፈ ለአፍታ ቢሰማው ኖሮ ለክፉ መንፈስ ተላልፎ መሰጠት አይኖርም ነበር::
በትንቢተ ሆሴ 4÷6 ላይ " ሕዝቤ ዕውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቶል " እንዲል የዕውቀት ማነስ ብቻ ሳይሆን የዕውቀት መብዛትም የብዙ ሰዎችን ዐይን አሳውሮ የማንነትን ጉዞ በማተረማመስ በጨለማ ውስጥ ሆኖ የጥፋት ድርጊቱን ማጧጧፉን ቀጥሏል::
በተለይ ምሁራን ለችግሮች ሁሉ መፍትኤ እንደሚሰጡ ይገመት ነበር እንዳለ መታደል ሆኖ ዛሬ በዘረኝነት ጽኑ ህመም ተይዘው የጸናው ሕመም እራሳቸው ላይ ሰለወጣ ስተው የሚያስቱ ከኤች አይ ቪ ኤድስና በጊዜያችን ከተነሳው ወረሽኝ ከኮሮና ቫይረስ ይልቅ ብዙዎችን እየጨረሰ ያለው የዘር በሽታ ሰለባ መሆናቸው እጁግ ያሳዝናል:: ይህ የዘር በሽታ የሕመሙ መተላለፊያ መንገድ መገናኛ ብዙኃን በመሆናቸው የሚሰማቸውና የሚያቸውን እንዲሁ የሚያነባቸውን ሁሉ የመመረዝ ኃይላቸው ከፍተኛ ነው ::እልቂቱም እጅግ የከፋ ይሁናል :: ቅዱስ ጳውሎስ ስለ ጥበበኞች ወይም ስለ ሙሁራን መሳት እንደሚከተለው ተናግሯል "ጥበበኛ የት አለ ? ጸአፊስ የት አለ? የዚህ ዓለም መርማሪስ የት አለ? እግዚአብሔር የዚህችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት እንዲሆን አላደረገምን?"1ቆሮ1÷20
እጅግ የተመሰገነው የእግዚአብሔር አገልጋይ ቅዱስ ጳውሎስ የጻፈልንን ይህን ንግግር ከዘመናችን አንጻር ብንመዝነው ከዓለም አቀፍ እስከ አህጉራችን እና እስከ ትንሿ ሀገራችን ብናይ ጥበበኞች ጸአፊዎች ተመራማሪዎች ጥበባቸው የከበረ የሰው ልጅ ከመጥቀሙ በተቃራኒው አጥፊ እየሆነ እንደመጣ እየተመለከትን ነው::
ማብቂያ የሌላቸው ጦርነቶች ንጹሐን ሕጻናትን አረጋዊያንን ደካሞችን ብቻ ሳይሆን የጎበዛዚትንም ሕይወት እየቀጠፈ ነው ::ዓለም በትርምስ በእልቂት እየተቀጣ ነው የእልቂቱም መንገድ እጅግ ያስገርማል ሰደድ እሳት ፣ የመሬት ነውጥ ፣ የመሬት መንቀጥቀጥ ፣ ጎርፍ፣ ርሃብ፣ ቸነፈር፣ድርቅ፣ አውሎ ነፋስ ፣የአሸባሪና ተሸባሪ መጠፋፋት ወዘተ በዘመናችን የሚገኙ የእግዚአብሔር ቁጣ መገለጫዎች ናቸው ::
አሁን አያላን ነን ብለው የሚስቡ እኔ ከማን እንሳለው በማለት ዓለም ይጠፋል እንጂ ከሥልጣኔ ከዙፋኔ አልወርድም የታላቆች ታላቅ ነኝ የሚል የመከረ መፍለቂያ ንግግር ወደ ማያባራ የነፍስና የሥጋ መከራ ብዙኃኑን ወደ ሞት መንገድ እየወሰደ ይገኛል ::በልዮ ልዮ ደረጃ ዓለም አቀፍ ስብሰባዎች እየተባሉ ውይይቶች ይደረጋሉእጅግ የሚገርመው ነገር ግን በጉባኤው የእግዚአብሔር ስም አይጠራም ታዲያ እንዴት ከቁጣና እልቂት ለመዳን ይቻላል? ያልተፈታ እቆቅልሽ ነው :: ከፍ ብለን በዓለም አቀፍ ደረጃ የተገለጠውን በቅድምያ የመቀመጫና መቆሚያን ወይም ቅድሚያ የሀገር ጉዳይ ካልን ደግሞ ወደ ሀገራችን ኢትዮጲያ መለስ ብለን "ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች " የሚለውን አስበን ወደ ፈጣሪ በችግሮቻችን ዙሪያ መለመን ብንጀምር እና ወደ ቀሪው ጉዳያችን ብናልፍ የሚሻለው መንገድ ይህ ነበር :: መዝ 67(68)÷31
ለዚህ በጎ ሀሳብ አዋቂዎች በጥብዐት ስመ እግዚአብሔርን ጠርተው ቢወያዮ መልካም ሁሉ ለቅድስት ሀገራችን ይሆንላት ነበር::ዘር መቁጠሩም ቀርቶ ሁሉም ፊደል ይቆጥር ነበር :: ፊደሉም እ....ን....ስ....ማ......ማ.....የሚል ነው::
ይህችን ጊዜያዊ የእንግድነት መኖሪያችንን ስንለቅ ዘር ጾታ ቀለም የሥልጣን የሀብትና ዕውቀት ጀረጃ ሳይለያዮባት መልካም የሥራ ሁሉ የአዳም ዘር የሚወርሳት ገነት መንግሥተ ሰማያት አስበን በጊዜያዊ ምድራዊ ሕይወት ጥቅም ዘላለማዊ መንግስት እንዳናጣ እንጠንቀቅ ለዚህም የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት የቅዱሳን ተራዳይነት አይለየን......አሜን
ምንጭ:- መለከት 27 ዓመት ቁጥር2 ገጽ 2012ዓ.ም
520 views21:51