2022-08-27 21:13:27
ሸይኽ ሙሐመድ ኸሊል ሀራስ
-------------
ሸይኽ ሙሐመድ ኸሊል ሀራስ ይባላሉ። የተወለዱት በሂጅራ አቆጣጠር በ1934 ወይም በፈረንጆች በ1916 በሀገረ ግብፅ ሺይን በተባለች መንደር ነው።
የትምህርት ጉዟቸውን ከልጅነታቸው ጀምነረው በአዝሀር አሽ ሸሪፍ በ1926 እንደጀመሩ ይነገራል። የ2ኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ጨምሮ የዶክትሬት ማዕረግ ድረስ የደረሱት በዚሁ ታዋቂው የግብፅ ዩኒቨረሲቲ አዝሀር አሽ ሸሪፍ ነው። እንደሚታወቀው የአዝሀር አሽ ሸሪፍ የትምህርት ካሪኩለም የአሽዓሪያን ዓቂዳ መሰረት ያደረገ በመሆኑ ሸይኹም የትምህርት ዘመናቸውን በሙሉ ለዓቂዳ (እምነት) የአሽዓሪያን አካሄድ በመከተል ዒልመል ከላም (ፍልስፍና) ጥልቅ እውቀትን ማካበት ችለዋሉ! ከዚህም በዘለለ ለከፍተኛ ትምህርት የመረጡት የእውቀት ዘርፍ ተውሂድ (የአሽዓሪያው ተውሂድ ማለት ነው) በመሆኑ የዒልመል ከላም እውቀትን እስከ ዶክትሬት ማእረግ ድረስ በክህሎት ተጉዘውበታል።
ሸይኹ በኡሱሉ ዲን የትምህርት ዘርፍ ከመመረቅም አልፎ በአዝሀር አሽሸሪፍ የኩሊየቱ ኡሱሊ ዲን ኡስታዝ (መምህር) በመሆን አገልግለዋል።
ሸይኹ አላህ ይዘንላቸውና በአላህ ስሞችና ባህሪያት ዙሪያ የሰለፊያን መንሀጅ አብዝተው የጠሉ ብቻ ሳይሆን በብርታት ጦር የመዘዙና እጅግ የተዋጉትም ሸይኽ ነበሩ።
ነገር ግን ሳይታሰብ አንድ አስደንጋጭ ክስተት በሸይኹ ህይወት ላይ ተከሰተ! ይህ ክስተትም በሸይኹ ብቻ የቆመ ሳይሆን አዝሀርን ዩኒቨርሲቲንም ግራ ያጋባ ነበር
ክስተቱን የሽይኹ ተማሪ የነበሩት ሀበሻዊው ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ ከሸይኻቸው የሰሙትን እንዲህ ይተርኩታል:-
ግዜው ሸይኽ ሙሀመድ ኸሊል ሀራስ የዶክትሬት መመረቂያ ጥናታዊ ፅሁፍ እያዘጋጁ የነበረበት ሰአት ነው። በተማሩበት በተውሂድና መንጢቅ ዘርፍ ለየት ያለ ስራ የመመረቂያ ፅሁፍ ለማዘጋጀት ስላሰቡ ግራ ቀኝ አይተው አንድ ሀሳብ ፈልቆላቸዋል። ይኸውም በዒልመል ከላም ላይ አሽዓሪያዎችን በድርሰቶቹ እያንበረከከ እጅ በማስነሳት የሚታወቀውን የሸይኹል ኢስላም ኢብኑ ተይሚያህን ኪታቦች በማጥናት በማያዳግም መልኩ አካሄዱን የሚያጋልጥ ጥናታዊ ፅሁፍ ማዘጋጀት በጌታችን አላህ ሱብሀነሁ ወተዓላ ስሞችና ባህሪያት ላይ የኢብኑ ተይሚያን መንሀጅ ለማንኮታኮት ያቀደ ውጥን ነበር።
ይህንም ድንቅ የመመረቂያ ፅሁፍ በማዘጋጀት የአሽዓሪያን አካሄድ ለመነሰር የሸይኹል ኢስላም ኢብኑ ተይሚያ ኪታቦችን ማጥናት ጀመሩ። ተማሪያቸው ሸይኽ ሙሀመድ አማን አል ጃሚ እንደሚሉት የሸይኹል ኢስላም ኪታቦችን ለሶስት ወራት ያህል አጠኑ።
በስተመጨረሻ ግን የመመረቂያ ጥናታዊ ፅሁፋቸው የሸይኹል ኢስላም ኢብኑ ተይሚያህን መንሀጅ ማንኮታኮት መሆኑ ቀረ። ሸይኹ በአሽዓሪያ መንገድ ላይ ይህን ያህል አመት የኖሩት ፍፁም በስህተት ላይ ሆነው እንደነበረ ተገለፀላቸው። ሸይኹል ኢስላም ኢብኑ ተይሚያህም ቁርአን እና ሀዲስን የገጠመ እና ለነሱ ጥብቅና የቆመ መንሀጅ ባለቤት መሆኑ ተገለፀላቸው።
በስተመጨረሻም የመመረቂያ ፅሁፋቸው ኢብኑ ተይሚያን ከነመንሀጁ የሚያንኮታኩት መሆኑ ቀርቶ በአላህ ባህሪያት ዙሪያ ትክክለኛው የሰለፎችን መንሀጅ የተከተለው ኢብኑ ተይሚያህ መሆኑን የሚያፀና በማድረግ "ሰለፊዩ ኢብኑ ተይሚያህ" ( ابن تيمية السلفي ኢብኑ ተይሚያህ አስ ሰለፊ) የተሰኘ ፅሁፍ ሆነ።
እነሆ ይህ የዶክትሬት የመመረቂያ ፅሁፍ በኪታብ መልክ ታትሞ ለህዝብ የደረሰ ድንቅ ስራ ሆኗል።
ሸይኽ ሙሀመድ ኸሊል ሀራስ በሀገረ ግብፅ በአዝሀር በኩሊየቱ ኡሱሊ ዲን ዘርፍ በኡስታዝነት ሲያገለግሉ የቆዩ ሲሆን ሸይኽ አብዱል ዓዚዝ ቢን ባዝ ባቀረቡላቸው ጥያቄ መሰረት ወደ ሳውዲት ዓረቢያ በመጓዝ በመካ ኡሙል ቁራ በዓቂዳ ዘርፍ መምህርና የዘርፉ ዋና በመሆን አገልግለዋል።
ሸይኽ ሙሀመድ ኸሊል ሀራስ የሰለፊያን ዓቂዳ ካወቁበት ግዜ አንስቶ በዓቂዳቸው ጠንካራ ነበሩ፣ በዒልመል ከላም የተዘፈቁት የፈላስፋዎችንና ሙተከሊሞችን መንሀጅ የኖሩበት በመሆኑ በድርሰቶቻቸው አካሄዳቸውን በማጋለጥና ትክክለኛውን ቁርአናዊና ሀዲሳዊ ግንዛቤ በመግለፅ ይታወቃሉ።
ሙሳ ዋሲል አስ ሲልሚ የተባለ በኡሙል ቁራ ዩኒቨረሲቲ የዳዕዋና ኡሱሉዲን ዘርፍ ተማሪ በዓቂዳ ዘርፍ የማስተርስ የመመረቂያ ፅሁፉን "ሸይኽ ኸሊል ሀራስና የሰለፎችን ዓቂዳ በማረጋገጥ ላይ ያደረጉት ጥረት" በሚል ርእስ በማዘጋጀት አጠናቋል።
በጥናቱም እነዚህን ቃላት አስነብቧል:- "የሸይኽ ኸሊል ሀራስ መፅሀፍቶች የእውቀት መመንጫዎች፣ ቀላል አገላለፅን የተላበሱ፣ የሰለፎችን አካሄድ የኻለፉ ሰዎችን አካሄድ እጅግ የተገነዘቡ መፅሀፍት ናቸው።" ይላል።
ሸይኽ ሙሀመድ ኸሊል ሀራስ በርካታ ተማሪዎችን ማፍራት የቻሉ ታላቅ ሸይኽ ከመሆናቸው ጋር ከታዋቂ ተማሪዎቻቸው መካከል:-
ሸይኽ ሙሀመድ አማን አልጃሚ
ዶክተር ዓብዱልፈታህ ሰላማህ
ሸይኽ ዓሊይ ቢን ናሲር አል ፈቂሂ ተጠቃሽ ናቸው።
ሸይኽ ሙሀመድ ኸሊል ሀራስ በርካታ መፃህፍትን ደርሰው ያለፉ ሲሆን ለአብነት ያህል:-
ኢብኑ ተይሚያህ አስ ሰለፊይ (የዶክትሬት መመረቂያ ድርሰታቸው ነች)
አሲፋት አልኢላሂያ ዒንደ ኢብኒ ተይሚያህ
ሸርህ አልዓቂዳህ አልዋሲጢያህ
ሸርሁ ኑኒየቲ ኢብኒል ቀዪም
ኢብኑ የትሚያህ ወነቅዱሁ ሊመሳሊኪል ሙተከሊሚነ ፊ መሳኢሊል ኢላሂያ ተጠቃሾች ናቸው።
ከዚህም ውጪ በርካታ የቀደምት መፃህፍቶች ላይ የተህቂቅና ተዕሊቅ ስራ ሰርተዋል።
ሸይኽ ሙሀመድ ኸሊል ሀራስ በፈረንጆች 1975 ከዚህ አለም በሞት የተለዩ ሲሆን ከመሞታቸው በፊት ( التوحيد وأهمية العودة اليه ተውሂድና ወደ ተውሂድ የመመለስ አንገብጋቢነት ) በሚል ርእስ ያቀረቡት ሙሀደራ የመጨረሻ ስራቸው እንደሆነ ይነገራል።
አላህ በሰፊ እዝነቱ ይዘንላቸው!
1.1K views18:13