2022-07-28 10:32:30
በቤት ኪራይ መማረሬን ያወቀ አንድ ጴንጤ ጓደኛዬ ቤቴ መጣና (የተከራየሁት ቤት ማለቴ ነው ) ቸርች ካልሄድን ብሎ ይጨቀጭቀኝ ጀመር!…የተኛሁበት አልጋ ጋ ቆሞ ቁልቁል እያየኝ…
“ሰው ስንት ቦታ ደርሷል አንተ ዛሬም እዚህ አልጋ ላይ ተጣብቀሀል? ስምህ እኮ እዮብ ሳይሆን መፃጉ ነበር መሆን የነበረበት!”…የለበስሁትን ብርድ ልብስ ከላዬ ላይ ገፈፈውና…
“በጌታ በየሱስ ስም የመጋደም መንፈስ እንደዚህ ብርድ ልብስ ከላይህ ላይ ይገፈፍ” ብሎ ጮኸ!
‘ኧረ በናትህ ሰውዬ አከራዬ የድምፅ ፎቢያ አለባቸው እንዳታስባርረኝ!…ድምፅ ከመጥላታቸው የተነሳ ከሚስታቸው ጋ ሴክስ ሲያደርጉ እራሱ አፏን በፕላስተር አሽገው ነው’!…ምን አልባት ከፕላስተሩ አምልጦ ሚወጣ እንኳን ድምፅ ካለ ለጥንቃቄ ብለው ጆሯቸው ውስጥ ጥጥ ይወትፉሉ!’
“ምን? ይሄማ የሰይጣን መንፈስ ነው ሄጄ ልፀልይላቸው” ብሎ ሊገሰግስ ሲል እግሩን ይዤ አስቆምኩት!….ድንገት ዞር ሲል ኮመዲኖ ላይ የተቀመጠ አምስት ሊትር ዘይት አየና….
“ኦው…ዘይት አለህ እንዴ? በቃ ላንተ ልፀልይልህ የሳቸው ሌላ ግዜ ይደርሳል” ብሎ አፈፍ አድርጎ አነሳውና ወደኔ እያየ “ደግሞ Omar ነው ባክህ?”
ግንባሬን ቋጠር አድርጌ…
‘ማለት የዘይቱ አይነት ፀሎቱ ላይ የሚያመጣው ለውጥ አለ ማለት ነው?’
“እሱስ የለም! በመኪና ዘይትም ቢፀለይ ዋናው እምነት ነው!” …ብሎ ክደኑን ሊከፍተው ሲል መንጭቄ አስለቀኩትና….
‘ቀልደኛ ነህ አንተ ባክህ! በፀሎት የገዛሁትን ዘይት ፀሎት በሚል ተልካሻ ምክንያት ልታባክን ስትነሳ ትንሽ አይከነክንህም? ከቻልክ ዘይቱ ላይ ፀልይልኝና 5 የነበረውን 10 ሊትር አድርግልኝ’… ብየ አፈጠጥሁበት!
“ይህን እንዳደርግ እንኳ ጌታ አልነገረኝም! ላጤ ስለሆነ ብዙ የዘይት ፍጆታ የለበትም ያለው ይበቃዋል ነው ያለኝ”!
ድክም አለኝና….
‘እሺ አሁን ምን ፈልገህ ነው የመጣኸው?’
“ቸርች እንሄዳለን ዛሬ”!
‘ለምን?’
“እዚህ ከተማ ውስጥ የቤት ችግር እንዳንተ ያማረረው ሰው አለ? ሌላው ቀርቶ ቤት የሚመታ ግጥም ስታይ ራሱ እኮ ልብህ ሰፍ ይላል!”
‘እና ምን ይሁን?’
“የቤት ችግርህ ዛሬ ታሪክ ሆኖ ይቀራል ! አሜን!”
‘የቤት ስጦታ ሰጥተህ surprise ልታደርገኝ ነው እንዴ ?እኔ እኮ አለምንህም’
“እሱን እዛው church ስንሄድ ታየዋለህ!…አንኳኩ ይከፈትላችኋል ሲባል አልሰማህም?”
‘እኮ ቤት ሳይኖረኝ ምኑን ላንኳኳ?’
“ካሁን በኋላ ማንኳኳት አያስፈልግህም!…ዛሬ የቤትህን ቁልፍ የዘህ መጥተህ እራስህ ነህ ከፍተህ ምትገባው! ተነስ!!
አለኝና ቸርች ወሰደኝ….
ቸርች ውስጥ እየተዘመረ ነው! አይናቸውን ጨፍነው አንድ እጃቸውን ደረታቸው ላይ ለጥፈው..አንድ እጃቸውን ደግሞ አየር ላይ ዘርግተው እንደ ባንዲራ እያወለበለቡ በሚዘምሩ ሴቶች ውበት ልቤ ተማረከ! አቤት ታፋቸው ደግሞ ቅላቱ! መዝሙሩን ትቼ በአይኔ ማመንዘር ጀመርሁ! … ድንገት መዝሙሩ ቆመና ሱፉን ግጥም አድርጎ የለበሰ….የፀጉሩ የጎን ክፍል ላይ ጭረት አድርጎ በቄንጥ የተቆረጠ ፍሪክ መድረክ ላይ ወጣና ማውራት ጀመረ…
“ቦቦቦቦቦታታሴካ …..ሀሟሏሯሷሿሌማሴኔ…ባርሳማድሪድ ጋላሴሬ….”
ቋንቋው የአልጋ ወይም የበር ጠርዝ የእግሬን ትንሿን ጣት ሲነድለው ከማወራው ቋንቋ ጋ ተማሰለብኝ! ወዲያው…
“የቤት ችግር ያለባችሁ ቅዱሳን ወደ ፊት ኑ “ማለት ጀመረ! ይህን ቃል ከመናገሩ ጓደኛዬ “እስካሁን እዚሁ ነህ ? “ ብሎ ገፈተረኝና ከኋላ የነበርሁት ሰውዬ ፊት ለፊት ተገኘሁ! ፀሎቱ ተጀመረ…
“የቤት ችግር ያለባችሁ ሰዎች በየሱስም ዛሬ አግኙ”
አሜንንንንን
“የቤት ችግር ያለባችሁ ሰዎች ዛሬ ውረሱ”
አሜንንንንንን
“ተሰርቶ ያለቀ ባለሁለት መኝታ ኮንድሚኒየም ውስጥ ግቡ”
‘ኦ ይሄ ሰውዬ ከ አዳነች አቤቤ ጋ ሊያያይዘን ነው እንዴ’ ስል በልቤ አሰብሁ!
ቀጠለ…
“ከአሁኗ ደቂቃ ጀምሮ ተአምራት ይሆናል! የreal estate እና የ apartment ቁልፍ ትረከባላችሁ! በኪራይም የምትኖሩ የተከራያችሁትን ቤት ትወርሳላችሁ”
አሜንንንንንንንን!!!! ሰማይ ምድሩ ተናወጠ!
ማታ! ወንበር ላይ ቁጭ ብዬ ከጓደኛዬ ጋ እያወራሁ ነው!
“በቃ እመን! ካሁን በኋላ ስለ ሌላ ችግርህ አስብ እንጂ የቤት ጉዳይ ያንተ ችግር አይደለም!”… እያለኝ እያለ ድንገት በሬ ተንኳኳ…’ቆይ አንዴ መልሼ ደውልልሀለሁ’ብዬ ስልኩን ዘጋሁና በሩን ከፈትሁት! አከራዬ ናቸው! ወዲያው ፓስተሩ …“በኪራይም የምትኖሩ የተከራችትን ቤት ትወርሳላችሁ” ያለው ቃል ትዝ አለኝ! …’እንዴት ያለ ድንቅ ፓስተር ነው?’ ስል በልቤ አደነቅሁት!
አከራዬ የሸሚዜን ኮሌታ እያስተከከሉ….
“ልጅ እዮብ እንዴት ነህ?”
‘ደህና ነኝ ጋሼ ደህና ነኝ”… ቶሎ ወደ ገደለው እስኪገቡ ቸኮልሁ!
“ያው መቼም እንደ ልጄ እንደምወድህ ታውቃለህ….”
አሁን እርግጠኛ ሆንኩ! “እንደ ልጄ ሰለምወድህ አሁን ያለህበትን ክፍል ጨምሮ ከጎኑም ያለውን ቤት አብሬ በስጦታ መልክ አበርክቼልሀለሁ” ሊሉኝ እንደሆነ በልቤ ደመደምሁ! … ‘አመሰግናለሁ ጋሼ አባቴ ኖት’ ብዬ ልጠመጠምባቸው ስል “ቆይ ቆይ ተረጋጋ እንጂ” ብለው በእጃቸው መለሱኝ…
‘ምነው ጋሼ?’
“እንዴ አስጨርሰኝ እንጂ!…እኔ ልል የፈለግሁት ምንም እንደ ልጄ ብወድህም የኑሮ ውድነት አናት በመውጣቱ የቤት ኪራይ 500 ብር ጨምሬብሀለሁ ልል ነው”!
የሰማሁትን ማመን አቃተኝ! ምን አልባት ከጆሮዬ ከሆነ ብዬ ኮረኮርኩትና ….’ምን አሉኝ ?’ አልኳቸው! እራሱኑ ቃል በደንብ ረገጥ አድርገው ደገሙልኝ!
ንዴቴን መቆጣጠር ተሳነኝ! ወዲያው ጓደኛዬ ጋ ደወልሁና የሆነውን ነገርሁት!! ጓደኛዬ በሚያስተሳዝን ቅላፄ ድምፁን ዝቅ አድርጎ….
“አይዞህ በቃ ክርስቲያን ቤቱ በሰማይ ነው”
ብሎ ስልኩን ዘጋው
“እዮብ ዘ ማርያም”
Join
@poeteyobzmariam
@poeteyobzmariam
@poeteyobzmariam
1.3K viewsedited 07:32