2022-06-04 09:48:31
❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖
✞ አቡነ ሀብተ ማርያም ✞
=====================
አቡነ ሀብተ ማርያምም ይህን በተመለከቱ ጊዜ ቅዱስ ሚካኤልን ‹‹መስቀል ታሳልሟት ዘንድ ያችን ነፍስ ወደ መስቀል ለምን ወሰዳችኋት?›› ብለው ጠየቁት፡፡ መልአኩም ‹‹በትልቅም በትንሽም ነገር ክርስቲያናዊትን ነፍስ የሚቃወም ቢመጣባት ድል የምትነሳበትን በመስቀል ፍርድ ይታይላታልና ስለዚህ ነው፡፡ የሚከራከራት ቢኖር ግን እንዳየኸው ወደ መስቀል ባደረሷት ጊዜ የሚቃወማት ሰይጣን ፈጥኖ ይርቅላታል ዳግመኛም ሊከራከራት አይችልም›› አላቸው፡፡
ከአቡነ ሀብተማርያም በረከት ለመቀበል ብዙ ቅዱሳን ከሮም፣ ከግብፅ፣ ከአስቄጥስና ከሲሐት ገዳም ወደ አባታችን ዘንድ ይመጡ ነበር፤ ከየሀገራቸውም በአንበሳ ተቀምጠው የሚመጡ አሉ፤ ክንፍ ተሰጥቷቸው እንደ ንስር የሚበሩም አሉ፤ ብፁዕ አቡነ ሀብተ ማርያምም የቅዱሳኑን ብቃት አይተው ‹‹ሥራችሁ እንዲህ እንዲህ ሲሆን ለምን ወደኔ መጣችሁ?›› ብለው ሲጠይቋቸው ቅዱሳኑም ‹‹በማንኛውም ሥራ እግዚአብሔርን በለመነው ጊዜ በኢትዮጵያ የሚኖር እንደ ሙሴ ያለ ሀብተ ማርያም የሚባል ወዳጄ አለና ሁሉን ስለሚነግራችሁ ዘወትር እርሱን ጠይቁ ብሎ ስላዘዘን ወደ አንተ መጣን›› አሏቸው፡፡ አባታችንም ቅዱሳኑን ከባረኳቸውና ከእነርሱም ከተባረኩ በኋላ አባታችን ለቅዱሳኑ የሚመጣውን እንዳለፈ የሚደረገውንም እንደተደረገ አድርገው ይነግሯቸዋል፡፡ ቅዱሳኑም ከልጅነታቸው ጀምረው እስከዚያች ቀን ድረስ የሠሩትን ሥራ ሁሉ ይነግሯቸዋል፡፡ እነርሱም እጃቸውን እየሳሙ በረከታቸውን ይቀበሉ ነበር፡፡
እንደዚሁም አቡነ ሀብተ ማርያም ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል እየተራዱዋቸው ቀድሰው በሚያቆርቡ ጊዜ ተሰውረው የሚኖሩ 500 ስውራን ቅዱሳን መጥተው ሥጋ ወደሙን ከአባታችን እጅ ተቀበሉ፡፡ ቀድሰውም ወደበዓታቸው እንደገቡ እመቤታችን ተገልጣላቸው ‹‹በነገውም ዕለት ቅዳሴዬን ቀድስ፣ ይህም ቅዳሴ መዓዛ ቅዳሴ ነውና፡፡ የዓለም መሠረት ማርያም ወደኔ ነይ ብለህ በጠራኸኝ ጊዜ ነቢያትን ሐዋርያትን አስከትዬ መጥቼ እባርክሃለሁ›› አለቻቸው፡፡ አባታችንም ‹‹በነገው ዕለት ሌላ ተረኛ ቄስ ይቀድሳልና ይህ እንዴት ይሆንልኛል?›› አሏት፡፡ እመቤታችንም ‹‹ፈቃዴ ስለሆነ አንተ እንድትቀድስ አደርጋለሁ›› አለቻቸው፡፡ በነጋታው ተረኛው ቄስ ከእንቅልፉ በነቃ ጊዜ ቸኩሎ እየተፋጠነ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲገሰግስ ወድቆ ጥርሱ ደማና ስለ ሥጋ ወደሙ ቅዳሴ እጅግ ደንግጦ ወደ አባታችን መጥቶ ‹‹ቅዳሴው በእኔ ስም ከሚታጎል አንተ ቀድስልኝ›› አላቸው፡፡ አባታችንም አስቀድማ እመቤታችን የነገረቻቸውን ነገር አስበው እያደነቁ ሄደው ቀደሱ፡፡ እመቤታችንም ነቢያትን ሐዋርያትን አስከትላ መጥታ ባረከቻቸው፡፡
በወቅቱም በሀገራችን ላይ ሃይማኖቱ የቀና ደጉ ንጉሥ ዐፄ ናዖድ ነግሦ ሳለ በእርሱ ዘመን እግዚአብሔርን የሚያስቆጣ ሥራ በሀገሩ ተሠርቶ ነበርና ጌታችን ለአቡነ ሀብተ ማርያም የምሥጢር መጽሐፍን ሰጣቸውና ለንጉሡ ወስደው እንዲሰጡ አዘዛቸው፡፡ ወስደውም ለንጉሡ ሰጡትና መብረቅም ወርዶ ሀገሪቱን ሊያጠፋት መሆኑን ነገሩት፡፡ ዐፄ ናዖድ ይህን በሰሙ ጊዜ መልእክቱንም ካስተረጎሙ በኋላ እጅግ ደንግጠው አቡነ ሀብተ ማርያምን ‹‹ሀገራችንን በጸሎትዎ ታደጓት›› አሏቸው፡፡ በጸሎታቸውም እንዲያስቡት በወርቅ የከበረ መስቀል ሰጣቸው፡፡ አባታችንም ወደ በዓታቸው ተመልሰው በጾም በጸሎት ተወስነው እያለቀሱ ስለ ሀገራችን አጥብቀው ጸለዩ፡፡ ጌታችንም ተገልጦላቸው ‹‹ድካምህን አይቻለሁና በሀገርህ የታዘዘው መቅሰፍቴ ይርቃል ነገር ግን በቸነፈር ጥቂት ሰዎች ይሞታሉ›› አላቸው፡፡ አባታቸንም ደስ ተሰኝተው ይህንንም ሰምቶ ይደሰት ዘንድ ለንጉሡ መልእክተኛ ልከው ነገሩት፡፡
ከዚህም በኋላ አቡነ ሀብተማርያም በጸሎት ላይ ሳሉ ጌታችን መላእክቱን አስከትሎ መጥቶ አባታችንን ‹‹የቆምክባትን ቦታ ምሥራቁን፣ ምዕራቡን፣ ሰሜኑን፣ ደቡቡን ባርክ›› አላቸው፡፡ አባታችንም እንደታዘዙት ሲባርኩ ሦስት አጋንንት በትይዩ ቆመው ታዩአቸው፡፡
ከኖኅ ዘመን ከተደረገው ማየ አይህ ተርፈን ብዙ ዘመን ከኖርን በኋላ ከአንተ ጋር ምን ፀብ አለን? ሀብተ ማርያም ሆይ ታጠፋን ዘንድ መጣህን›› ብለው ጮኹ፡፡ አባታችንም ‹‹በሰው ላይ የምታደርጉትን የምታስቱበትን ብልሃታችሁን ነገሩኝ›› አሏቸው፡፡
ከእነርሱም ውስጥ አንዱ ‹‹እኔ ከጥንትም ጀምሮ አምላክ ነኝ እያልኩ ሳታልላቸው ኖርኩ፤ ክታብ መጻፍን፣ ቅጠል መበጠስን፣ ሞቶ ያደረውን ከብት መብላትን፣ የሰውን ሥጋ መብላትን፣ በወፍ ማሟረትን አስተማርኳቸው፡፡ በሚሞቱበትም ጊዜ ወደ ሲኦል አወርዳቸዋለሁ፡፡ በእንዲህም ሥራ ሳለሁ ክርስቶስ ተወለደና ሥራዬ የተገለጠ ሆነ፡፡ ከብዙ ዘመንም በኋላ ተክለ ሃይማኖት የሚባል ኃይለኛ ሰው መጥቶ ከክርስቶስ በቀር ለእኔ እንዳይገዙ አደረጋቸው፤ እገድለውም ዘንድ ብዙ ጊዜ ሞከርኩ ነገር ግን እርሱ እጅግ በረታብኝ፤ ወገኖቼንም ቀማኝ፡፡ ሁለተኛ ወንድሜም ይውጠው ዘንድ በዘንዶ ተመሰለ ነገር ግን በመስቀል ባማተበበት ጊዜ ተሰንጥቆ ሞተ፡፡ እኔም ከእርሱ የተነሣ ስለነፈራሁ ሸሽቼ ተሸሽጌ መንደር ለመደንር ስቅበዘበዝ ኖርኩ ፈንታዬ የሆኑ ጥቂት ሰዎችንም አገኘሁ›› አላቸው፡፡ አባታችንም ‹‹ያሳትካቸው እነማን ናቸው?›› ባሉት ጊዜ ሁሉንም ስማቸውን እየጠራ በዝርዝር ነገራቸው፡፡ ‹‹የእገሌ ኃጢአቱ ይህ ነው…›› እያለ የእያንዳንዱን የበደላቸውን መጽሐፍ አነበበላቸው፡፡
ዳግመኛም ሰዎች እርሱን የሚያሸንፉበትን ነገር ለአባታችን ሲነግራቸው ‹‹ነገር ግን ኃጢአት ሠርተው በደላቸውን ለካህን በመንገር ንስሓ ገብተው እኔ ልሰውረው ስወድ ምክሬን በገለጡብኝ ጊዜ ትቻቸው እሸሻለሁ›› አላቸውና እንዲያሰናብቱት ለመናቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ጌታችን አቡነ ሀብተ ማርያምን ‹‹ብዙ ቅዱሳንን አስቷልና አታሰናብተው፣ ከእግሩ በታች ያለውን መሬት ባርክና ምድር አፏን ከፍታ ትዋጠው›› አላቸው፡፡ አባታችንም ጌታችን እንዳዘዛቸው አድርገው ያንን እርኩስ መንፈስ ምድር አፏን ከፍታ እንትውጠውና ጽኑ ፍዳ ወዳለበት ወደ ሲኦል እንዲወርድ አደረጉት፡፡
ይህንንም ሲያዩ እዚያው ቆመው የቀሩት ሁለቱ አጋንንትም እጅግ ፈሩ፡፡ አንደኛውም ክንፍ ያለው እባብ ሆኖ ወደ አየር በበረረ ጊዜ ቅዱሳን መላእክት በእሳት መንኰራኩር ራስ ራሱን ቢቀጠቅጡት አፏን ወደ ከፈተችው ምድር ወደቀና እንደ ጓደኛው ወደ ሲኦል ወረደ፡፡ የቀረው ሦስተኛው ግን አባታችንን ‹‹ሀብተ ማርያም ሆይ ያደረኩት ክፉ ነገር ሳይኖር ያለ ጊዜዬ እንዳታጠፋኝ በምታመልከው አምላክ ስም አምየሃለሁ፣ እኔ በዚህ ወር ነው ከዚህ ሀገር የደረስኩት›› እያለ ለመናቸው፡፡
=====================
✥ ✞ ✥
❖ ✥┈•◦●◈◎❖◎◈●◦•┈✥❖
98 views06:48