2022-02-13 15:06:32
አርሴማ ቅድስት ሰማዕት
አጠር በጠር ያለ ታረኳ
ሰማዕትነትን የተቀበለችበትን እለት በማሰብ በድጋሚ የተለጠፈ
በቀሲስ መምህር ሄኖክ ወልደ-ማርያም
ሼር በማድረግ ለሰማዕቷ ልጆች አዳርሱ
ሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ እግዚአብሔርን ከሚፈሩ ከሚያከብሩ ብሩካን ከሆኑ፤በጾም በጸሎት በስግደት በትጋት ከሚኖሩ ከአባቷ ከቅዱስ ቴዎድሮስ ከእናቷ ከቅድስት አትናስያና በጥር 6 ቀን የተወለደች ደገኛ የገድል አርበኛ ናት፡፡
በተለይ ስትወለድ ይህ ቀረሽ የማትባል እጅግ መልከኛ እና ግርማዋ የሚያስፈራ ነበር፡፡ እናት እና አባቷም በጾም በጸሎት በስዕለት ስላገኟት እስከ 3 ዓመት ካሳደግዋት በኃላ በእመቤታችን በድንግል ማርያም ስም በተሰራች ቤተ ክርስትያን ታገለግል ዘንድ ሰጧት፡፡ እመቤታችንን 12 ዓመት አገልግላ ያለፈቃድዋ በቤተሰቦችዋ ግፊት በ15 ዓመቷ ዳሯት፡፡ ሰማዕቷ ግን ዓለማዊ ህይወት ባለመፈለግዋ ወደ ገዳማዊ ምናኔ ህይወት ገብታለች፡፡
በዚያን ዘመን ብዙ ሰማዕታት ያስፈጀ ጨካኙ የሰው አውሬ ካሃዲው ዲዮቅልጥያኖስ መላኳ ውብ የሆነ ብላቴና ድንግል ሴት ሊያገባ ሽቶ በየአገሩ ሁሉ ፈልገው መርጠው ያመጡለት አንድ አሽከሮቹን አዘዘ፡፡
እንግዲህ የሰማቷ አሳዘኝ የመከራ ህይወት ከዚህ ነው የሚጀምረው፡፡
የዲዮቅልጥያኖስ ሠራዊቶች አርሴማ የምትባል ውብ ሴት እንዳለች በሰሙ ጊዜ ቅድስት አርሴማ በሮሜ በአንድ ገዳም እንዳለች ሰሙ፡፡ አዋቂዎችም የሰማዕቷን ውብ መልኳን ስለው ለንገሡ ለዲዮቅልጥያኖስ ላኩለት፡፡ ንጉሡም ስዕሏን ባየ ጊዜ እጅግ ደስ አለውና በሥጋዊ ጋብቻ አብራት ሊኖር እንዳሰበ ለመኳንንቱ ነግሮ ለሠርግ እንዲመጡ አዘዘ፡፡
ቅድስት አርሴማ ይህንን በሰማች ባወቀች ጊዜ ከደናግሉ ጋር የንጉስ ድርጣድስ ግዛት ወደ ሆነው አርመንያ አገር ሸሸች፡፡ ንጉስ ዲዮቅልጥያኖስ የከበረች አርሴማን አስፈልጎ ባጣት ጊዜ በአርመንያ እዳለች ሰማ፡፡
ለአርመንያው ንጉሥ ለድርጣድስ ከእሱ ሸሽታ እንደሄደች እና ባስቸኳይ አስጠብቆ እንዲልክላት አዘዘው፡፡ ደናግሉ ይንን በሰሙ ጊዜ ወደ ሌላ ቦታ ተሰወሩ፡፡ ንጉሡም ቅድስት አርሴማን በክብር ያመጧት ዘንድ አዘዘ፡፡ ሰማዕቷም ወደ እርሱ መምጣትን እንቢ ባለች ጊዜ በመሬት እየጎተቱ ወደ ንጉሡ አቀረቧት፡፡
ድርጣድስ የቅድስት አርሴማን ደም ግባት እና ውበት ባየ ጊዜ ድንግልናዋን ሊያረክስ ሽቶ የመንፈስ እናቷን አጋታን አባብላ እሺ ታሰኛት ዘንድ አዘዛት፡፡
አጋታም ወደ ሰማዕቷ ሄዳ ልቧን አስጨከነች እንዲህም አለቻት ‹‹ ዕወቂ ይህ ርኩስ አረሚ እንዳያረክስሽና ሰማያዊ ምሽራሽን ክርስቶስን እንዳትተይ›› ብላ አጸናቻት፡፡
ንጉሥ ድርጣድስም ሰማዕቷን ይዞ ወደ እልፍኝ ሊያስገባት ከአደባባይ መካከል ተነስቶ ድንግል አርሴማ በእጁ ያዛት፡፡ በዚያን ጊዜ በቅድስት አርሴማ ላይ የእግዚአብሔር ኃይል አደረባትና በምድር ላይ ጣለችው፡፡ ድርጣድስም በጦትነት እጅግ የጸና አርበኛ ስለነበር በታናሽ ብላቴና ስለተሸነፈ መኳንንቱ ፊት ስለተዋረደ አፈረ፡፡
ከዚህ በኃላ በሰው አንደበት ለመናገር የሚከብድ መከራና ስቃይ አጸናባት፡፡ ሰማዕቷም ከንጉሡና ከጋሻ ጃግሬዎቹ የሚደርስባትን መከራ በመታገስ በረታች፡፡ ንጉሥ ድጣድስ በሰማዕቷ ላይ የሚያደርሰውን ሥጋዊ መከራ የልቡ ስላልደረሰለት ጡቷን በማስቆረጥ ዓይኗን በወረንጦ በማስወጣት ቢያሰቃያትም ሰማዕቷ ይበልጥ በክርስቶስ ፍቅር ጸናች፡፡ በሚደርስባትም ነገር ደስ ተሰኘች፡፡
ወዳጆቼ እኛ በሚደረስብን ሥጋዊ ህመም ስቃይ መከራ ፈተና እንደሰታለን? አንደሰትም ይልቁንም እናማርራለን፡፡ ምንያቱም የክርስቶስ የመከራ ህይወት ውስጣችን ስላልገባ ነው፡፡ ክርስቶስ ጋር ለመድረስ መንገዱ፣በአጋንንት እና በሥጋ እየተጎዱ መሆኑን ስለማንረዳ ነው፡፡ ብንረዳም የደስታ እንጂ የመከራ ትከሻ ስለሌለን ነው፡፡ የመከራ ትከሻ ቢኖረንም ትዕግስት ስለሌለን በመከራችን አንጸናም፡፡
በመጨረሻም ንጉሥ ድርጣድስ የሚያደርገውን ሲያጣ አንገቷን በሰይፍ ሊያስቆርጥ ወሰነ፡፡ ከዚህ በኃላ ንጉሥ ድርጣድስ ቡርክት ቅድስት አርሴማን ወደ መገደያ ወንዝ እንዲወስዷትና በዚያም የከበረ ራሷን ይቆርጧት ዘንድ አዘዘ፡፡ ንጉሡም ቅድስት አርሴማን ወታደሮች አንገቷን ሲቆርጧት ያይ ዘንድ ከእርሷ ጋር ወጣ፡፡ ሰማዕቷ በምትገደልበት ትይዩ ከሠራዊቱ ጋር ተቀመጠ፡፡
የእጃቸው ክንድ የበረታ ልባቸው ግን የጨከነ ሮማውያን ወታደሮች ሰይፍ ይዘው ወደ ሰማዕቷ ቀረቡ፡፡ ሰማዕቷ ሞቷ ሰማያዊ እረፍቷ ስለሆነ በደስታ ትመለከታቸው ነበር፡፡
ቅድስት አርሴማም ወታደሮቹን የጸሎት ጊዜ እንዲሰጧት ጠይቃቸው ፈጣሪዋን ካመሰገነች በኃላ ፊቷን ወደ ምስራቅ መልሳ ወገቧን ታጥቃ አንገቷን ከፍ አድርጋ ለሚቆወጣት ታመቻችላቸው ነበር፡፡
ቆራጮች ወታደሮች ከቅድስት አርሴማ ግርማ የተነሳ ደንግጠው ሰይፋቸውን እንደያዙ በምድር ላይ ወደቁ ሰይፋቸውንም ጣሉ፡፡ ሰማዕቷም እያበረታታች የታዘዛችሁትን ፈጽሙ ትላቸው ነበር፡፡ ወታደሮቹም እኛስ ወዳንቺ መቅረብ እና አንገትሽን መቁረጥ አልቻልንም በግንባርሽ ላይ ያለው ትዕምርተ መስቀል አስፈርቶና፤ግንባርሽን ካልሸፈንሽልን አንገትሽን ፈጽሞ ልንቆርጥ አንችልም አሏት፡፡
ሰማዕቷም ለወታደሮቹ ፊቴን የምሸፍንበት ቁራጭ ልብስ ወይም ቁራጭ ጨርቅ ስጡኝ አለቻቸው፡፡ እነሱም ቁራጭ ጨርቅ ጣሉላት እሷም ፊቷን ሸፈነች፡፡
ቅድስት አርሴማም ንጉሥ ድርጣድስ እና ሠራዊቱ ህዝቡም እየተመለከቱ ምስከረም 29 ቀን አንገቷን በሰይፍ ቆረጡ፡፡ ወዳጆቼ እኛን ጌታችን እንደ እነ ቅድስት አርሴማ፣ቅድስት ወለተ ጴጥሮስ፣ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ወዘተ አንገታችሁን ተቆረጡልኝ ሰማዕት ሁኑልኝ አላለንም፡፡ ኃጢአትን ከእናንተ ሰውነት ቆርጣችሁ ጣሉት ነው ያለን፡፡
የዝሙትን ፍላጎት ከሰውነታችሁ ቁረጡና ደም አላባ ሰማዕት ሁኑ ነው የተባልነው፡፡ የኃጢአቶችን ተቀጽላ ከሥጋችሁ ላይ ቁረጡና በንስሐ ጻድቅ ሁኑ ነው ያለን፡፡ እንደ ሰማዕታት በደማቸው ዋጋ ገነት ግቡ ሳይሆን በደሜ ፈሳሽት መንግስቴን ውረሱ ነው ያለን፡፡ እንደ ሰማዕታት ጽኑ መከራን በስጋችሁ ተቀበሉ ሳይሆን ቅዱስ ሥጋዬን ብሉና የርስቴ ተካፋይ ሁኑ ነው ያለን፡፡ ሰማዕት ሁኑ ሳይሆን በእኔ መስዋዕትነት ዳኑ ወደ መንግስቴ ጎዳና አቅኑ ነው ያለን፡፡ አወይ አለመጠቀማችን እንደ እኛ ያደለው ማን አለ?
ከአንገቷም ደም፣ውኃ፣ቀተትና ማር እንደ ክረምት ነጠብጣብ እየተንጠባጠበ መነጨ፡፡
ደም ከአንገቷ የመነጨው ስለ ሃይማኖትዋ ቆራጥነት ስለ ሞት አለመፍራት እና የጌታችንን መከራ ተሸክማ ሰማዕት ስለሆነች ነው፡፡
ውኃ የፈሰሰው ስለ ብዙ ጸሎትዋ፤ስለልመናዋና የቤተ ክርስትያን መጻሕፍትንና ምስጢራትን ሁሉ ልብ ስለምታደርግ ነው፡፡
ወተት የመነጨላት ስለ ክብሯ ስለ ከፍታዋ እና ንጽሃ ድግልናዋን ስለጠበቀች ነው፡፡
ማር የወረደው ስለሚያስደንቅ የፊቷ ወዝ፣ደም ግባቷ፣ስለ ጣፋጭ የከንፈሯ ቃልና የሰማዕታት ሁሉ እህት ስለሆነች ነው፡፡
ከዚህ በኃላ ብሩህ የሆነ የደመና አምድ ወረደና በላይዋ ጋረዳት፡፡ ወደ ሰማይም እንደ መብረቅ ሳባት፡፡ የቅዱሳን መላእክትም ማህበር ነፍሷን አሳረጓት፡፡ በክብር በእልልታ በዝማሬና በማህሌት ሃሌ ሉያ እያሉ ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም አስገቧት፡፡
እርሷ እንደ ሞተች ባወቁ ጊዜ ወታደሮቹ ደናግሉን ሁሉ ጫማቸውን እየበሱ እራሳቸውን ቆረጡ፡፡ ቁጥራቸውም ሰባ ሁለት ነፍሳት ነበሩ፡፡
፨ ቃል ኪዳንዋ ፨
1.1K views12:06