Get Mystery Box with random crypto!

† † እንኳን ለጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረ | ✞ገድለ ቅዱሳን✞

† † እንኳን ለጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። † †

† † በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! † †

† † አቡነ ገብረ ሕይወት † †

† † ጻድቁ የተወለዱት ግብፅ (ንሒሳ አካባቢ) ሲሆን አባታቸው ስምዖን እናታቸው አቅሌስያ ይባላሉ:: አባታችን ገብረ ሕይወት የጻድቃን አለቃ: የቅዱሳን የበላይ: ተጋድሎአቸውና ድንቅ ተአምራቸው እንደ ሰማይ ከዋክብት የበዛ ቅዱስ ሰው ናቸው::

የጻድቁን ክብር መናገር የሚችል ምን አንደበት ይኖራል?
*እንደ ምንስ ባለ ብራና ይጻፋል?
*ዜናቸውንስ ለመስማት የታደለ እንደ ምን ዓይነት ሰው ይሆን?

አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስ ለ562 ዓመታት በዚህች ዓለም ሲኖሩ:-
*እህል ያልቀመሱ (ምግባቸው ምስጋና ነውና)::
*ልብስ ያልለበሱ (ጠጉር አካላቸውን ይሸፍን ነበርና)::
*ሐዋርያዊ ሆነው ከግብፅ እስከ ኢትዮዽያ ብዙ ነፍሳትን ያዳኑ አባት::
*ሃገራችንን አስምረው: አስራት እንድትሆናቸውም ተቀብለው ምድረ ከብድ አካባቢ አርፈዋል::

ጻድቁ ገብረ መንፈስ ቅዱስም : ገብረ ሕይወትም ይባላሉ:: በ562 ዓመታት ሕይወታቸው እንደ ሐዋርያት ከምድረ ግብፅ እስከ ኢትዮዽያ ወንጌልን ሰብከዋል:: በዚህም በሚሊየን (አእላፍ) ለሚቆጠሩ ነፍሳት የድኅነት ምክንያት ሆነዋል::

ጻድቁ እንደ ሰማዕታትም ከከሃዲ ሰዎች ብዙ መከራን ተቀብለዋል:: እንደ ባሕታውያን ለብዙ መቶ ዓመታት ሰው ሳያዩ ቆይተዋል:: ለየት የሚለው ግን የጽድቅ ሕይወታቸው ነው:: ከእልፍ አዕላፍ አጋንንት ጋር ተዋግተው ድል ማድረግ ችለዋልና::

የንሒሳው ኮከብ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ለኢትዮዽያ ልዩ ፍቅር አላቸው:: ስለ ሃገሪቱና ሕዝቧ ፍቅር ሲሉ ለ100 ዓመታት በደብረ ዝቋላ መከራን ተቀብለዋል:: ምሕረትን ሲለምኑ ሥጋቸው አልቆ በአጥንታቸው ቁመው ነበርና ሃገራችን አሥራት ሆና ተሰጠቻቸው::

ስለዚህም ነው በሃገሪቱ ውስጥ ከ2,000 በላይ የጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳማትና አድባራት ዛሬም ድረስ ያሉት:: በ8ኛው ክ/ዘመን አካባቢ የተወለዱት አባታችን ያረፉት በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን አካባቢ ነው:: ፍጥረታትን ሁሉ አዘው መጋቢት 5 ቀን ሲያርፉ ግሩማን መላእክት ገንዘው አካላቸውን ሠውረዋል::

ሥላሴን የተሸከመ አካላቸው በጐልጐታ ተቀብሯል የሚሉም አሉ::
"ሰላም ለመቃብሪከ ዘኢተከሥተ ለባዕድ::
ከመ መቃብሩ ለሙሴ ወልደ ዮካብድ::
ዜና መቃብሪከሰ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጸማድ::
ቦ ዘይቤ በኢየሩሳሌም አጸድ::
ወቦ ዘይቤ ኀለወ በከብድ::" እንዲል::

††† የጻድቁ በዓል ጥቅምት 5 ቀን የሚከበረው ብዙ ጊዜ መጋቢት 5 ዐቢይ ጾም ውስጥ ስለሚውል ተውላጥ (ቅያሪ) ሆኖ ነው::

††† ቸር አምላክ ከጻድቁ ዋጋና በረከት ይክፈለን::

††† መጋቢት 5 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጻድቅ (አባ ገብረ ሕይወት)
2.ቅዱስ አባ ሰረባሞን (በምድረ ግብፅ ምንኩስናን ካስፋፉ ታላላቅ ቅዱሳን አንዱ)
3.አባ ግርማኖስ ጻድቅ (ሶርያዊ)
4.ቅድስት አውዶክስያ ሰማዕት (ከከፋ የኃጢአት ሕይወት ተመልሳ ለቅድስና የበቃች እናት)
5.ቅዱሳን ስምዖንና ሚስቱ አቅሌስያ (የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ወላጆች)

††† ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ዼጥሮስ ሊቀ ሐዋርያት
2.ቅዱስ ዻውሎስ ሐዋርያ
3.ቅዱስ ዮሐኒ ኢትዮዽያዊ
4.ቅዱስ አሞኒ ዘናሒሶ

††† "ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ይወስዳል:: ጻድቅን በጻድቅ ስም የሚቀበል የጻድቁን ዋጋ ይወስዳል:: ማንም ከእነዚህ ከታናናሾቹ ለአንዱ ቀዝቃዛ ውሃ ብቻ በደቀ መዝሙር ስም የሚያጠጣ እውነት እላቹሃለሁ ዋጋው አይጠፋበትም::" †††
(ማቴ. 10:41)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††