Get Mystery Box with random crypto!

✞ ✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞ ✞ ❖የካቲት ፳፪ (22 | ✞ገድለ ቅዱሳን✞

✞ ✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞ ✞

❖የካቲት ፳፪ (22) ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

+ " አቡነ አቢብ (አባ ቡላ) " +

+ይህን ታላቅ ቅዱስ በምን እንመስለዋለን!
*እኛ ኃጥአን ጣዕመ ዜናውን: ነገረ ሕይወቱን ሰምተን ደስ
ተሰኝተናል!
*ቅዱሱ አባታችን:- "ቡላ-የእግዚአብሔር አገልጋይ"
ብለን እንጠራሃለን::
*ዳግመኛም "አቢብ-የብዙኃን አባት" ብለን እንጠራሃለን::

+እርሱ ቅሉ አባትነትህ አንተን ለመሰሉ ቅዱሳን ቢሆንም
እኛን ኃጥአንን ቸል እንደማትለንም እናውቃለን::
*አባ! ማነው እንዳንተ የክርስቶስን ሕማማት የተሳተፈ!
*ማን ነው እንዳንተ በፈጣሪው ፍቅር ብዙ መከራዎችን
የተቀበለ!
*ማንስ ነው እንዳንተ በአንዲት ጉርሻ አማልዶ ርስትን
የሚያወርስ!
*የፍጡራንን እንተወውና በፈጣሪ አንደበት ተመስግነሃልና
ቅዱሱ አባታችን ላንተ ክብር: ምስጋናና ስግደት በጸጋ
ይገባሃል እንላለን::

+" ልደት "+

+አባታችን አቡነ አቢብ የተወለደው በ3ኛው መቶ ክ/
ዘመን መጨረሻ አካባቢ ሲሆን ሃገረ ሙላዱ ሮሜ ናት::
ወላጆቹ ቅዱስ
አብርሃምና ቅድስት ሐሪክ እጅግ ጽኑ ክርስቲያኖች ነበሩ::
ልጅ ግን አልነበራቸውም:: ዘመነ ሰማዕታት ደርሶ ስደት በሆነ ጊዜ እነርሱም በርሃ ገቡ::

+በዚያም ሳሉ በቅዱስ መልአክ ብሥራት ሐሪክ ጸንሳ
ብሩሕ የሆነ ልጅ ወለደች:: ቅዱሱ ሕጻን ሲጸነስ ማንም
ሳይተክለው
የበቀለው ዛፍ ላይ መልአኩ እንዲህ የሚል የብርሃን
ጽሑፍ ጽፎበት ወላጆቹ ዐይተዋል::
"ቡላ ገብሩ ለእግዚአብሔር: ወቅዱሱ ለአምላከ ያዕቆብ:
ዘየኀድር ውስተ ጽዮን"

+" ጥምቀት "+

+ቅዱሱ ሕጻን ከተወለደ በኋላ ሳይጠመቅ ለ 1 ዓመት
ቆየ:: ምክንያቱም ዘመኑ የጭንቅ ነውና ካህናትን እንኳን
በዱር
በከተማም ማግኘት አይቻልም ነበር:: እመቤታችን ግን
ወደ ሮሙ ሊቀ ዻዻሳት አባ ሰለባስትርዮስ ሒዳ
'አጥምቀው' አለችው::

+ወደ በርሐ ወርዶ ሊያጠምቀው ሲል ሕጻኑ ተነስቶ:
እጆቹንም ዘርግቶ:- "አሐዱ አብ ቅዱስ: አሐዱ ወልድ
ቅዱስ አሐዱ
ውዕቱ መንፈስ ቅዱስ" ብሎ አመስግኖ ተጠመቀ::
ከሰማይም ሕብስና ጽዋዕ ወርዶላቸው ሊቀ ዻዻሳቱ
ቀድሶ ሁሉንም
አቆረባቸው:: የሕጻኑ ወላጆች "ለልጃችን ስም አውጣልን"
ቢሉት "ቡላ" ብሎ ሰየመው:: እነርሱም ምሥጢሩን ያውቁ ነበርና አደነቁ::

+" ሰማዕትነት "+

+የቅዱሱ ቡላ ወላጆች ለ10 ዓመታት አሳድገውት ድንገት
ሕዳር 7 ቀን ተከታትለው ዐረፉ:: ሕጻኑን የማሳደግ
ኃላፊነትን
የአካባቢው ሰዎች ሆነ:: ሕጻኑ ቡላ ምንም የ10 ዓመት
ሕጻን ቢሆንም ያለ ማቁዋረጥ ሲጾም: ሲጸልይ ክፉ
መኮንን
"ለጣዖት ስገዱ" እያለ መጣ::

+በዚህ ጊዜ በሕጻን አንደበቱ አምልኮተ ክርስቶስን ሰበከ:: በዚህ የተበሳጨ መኮንኑ ስቃያትን አዘዘበት:: በጅራፍ ገረፉት: በዘንግ ደበደቡት: ቆዳውን ገፈፉት: በመጋዝ ቆራርጠውም ጣሉት:: ነገር ግን ኃይለ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነበርና 2 ጊዜ ከሞት ተነሳ:: በመጨረሻ ግን ሚያዝያ 18 ቀን ተከልሎ ሰማዕት ሆኗል::

+" ገዳማዊ ሕይወት "+

+ቅዱስ ቡላ ሰማዕትነቱን ከፈጸመ በኋላ ቅዱስ ሚካኤል በአክሊላት አክብሮ ወስዶ በገነት አኖረው:: ከሰማዕታትም ጋር ደመረው:: በዚያም ቡላ ቅዱስ ጊዮርጊስን ተመልክቶ ተደነቀ:: መንፈሳዊ ቅንዐትን ቀንቷልና "እባክህን ወደ ዓለም መልሰኝና ስለ ፍቅርህ እንደ ገና ልጋደል" ሲል ጌታን ለመነ::

+ጌታችን ግን "ወዳጄ ቡላ! እንግዲህስ ሰማዕትነቱ
ይበቃሃል:: ሱታፌ ጻድቃንን ታገኝ ዘንድ ግን ፈቃዴ ነውና ሒድ" አለው:: ቅዱስ ሚካኤልም የቅዱስ ቡላን ነፍስ ከሥጋው ጋር አዋሕዶ: ልብሰ መነኮሳትንም አልብሶ ግብጽ በርሃ ውስጥ አኖረው::

+" ተጋድሎ "+

+አባ ቡላ ወደ በርሃ ከገባ ጀምሮ ዐርብ ዐርብ የጌታን
ሕማማት እያሰበ ራሱን ያሰቃይ ገባ:: ራሱን ይገርፋል:
ፊቱን
በጥፊ ይመታል: ሥጋውን እየቆረጠ ለአራዊት ይሰጣል:
ከትልቅ ዛፍ ላይ ተሰቅሎ ወደ ታች ይወረወራል::

+በጭንቅላቱ ተተክሎ ለብዙ ጊዜ ጸልዮ ጭንቅላቱ
ይፈሳል:: ሌላም ብዙ መከራዎችን የጌታን ሕማማት
እያሰበ ይቀበላል::
ስለ ጌታ ፍቅርም ምንም ነገር ሳይቀምስ ለ42 ዓመታት
ጹሟል:: ጌታችንም ስለ ክብሩ ዘወትር ይገለጥለት ነበር::

+የሚታየውም እንደ ተወለደ: እንደ ተጠመቀ: እንደ
ተሰቀለ: እንደ ተነሳ: እንዳረገ እየሆነ ነበር:: አንድ ቀንም
ጌታችን መጥቶ "ወዳጄ ቡላ! እንዳንተ ስለ እኔ ስም
መከራ የተቀበለ ሰው የለም:: አንተም የብዙዎች አባት
ነሕና ስምህ
አቢብ (ሃቢብ) ይሁን" አለው::

"እስከ ይቤሎ አምላክ ቃለ አኮቴት ማሕዘኔ:
ረሰይከኑ ለባሕቲትከ ኩነኔ:
ዘመጠነዝ ታጻሙ ነፍስከ በቅኔ" እንዲል::

+" ዕረፍት "+

+አቡነ አቢብ ታላቁ ዕብሎን ጨምሮ በርካታ ደቀ
መዛሙርትን አፈራ:: ከእመቤታችን ጋርም ዕለት ዕለት
እየተጨዋወተ
ዘለቀ:: በተጋድሎ ሕይወቱም ከ10 ጊዜ በላይ ሙቶ
ተነስቷል:: በዚህች ቀን ሲያርፍ ገዳሙ በመላእክት
ተሞላ::
+ጌታም ከድንግል እናቱ ጋር መጥቶ "ወዳጄ ቡላ!
ስምህን የጠራውን: መታሰቢያህን ያደረገውን
እምርልሃለሁ:: አቅም ቢያጣ
'አምላከ አቢብ ማረኝ' ብሎ 3 ጊዜ በዕለተ ዕረፍትህ
የሚለምነኝን: በስምሕ እንኳ ቁራሽ የሚበላውን ሁሉ
እምርልሃለሁ"
ብሎት ነፍሱን በክብር አሳረገ: በሰማይም ዕልልታ
ተደረገ::

✞አምላከ ጻድቃን ወሰማዕት በቃል ኪዳናቸው እንዲምረን ቸርነቱ ይርዳን:: በረከታቸውንም አትርፎ ይስጠን::

✞ ✞ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ✞ ✞