Get Mystery Box with random crypto!

† † በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! † † +'+ እንኩዋን ለቅዱስ 'አ | ✞ገድለ ቅዱሳን✞

† † በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! † †

+"+ እንኩዋን ለቅዱስ "አናሲሞስ ሐዋርያ" እና ለእመቤታችን "ቅድስት ድንግል ማርያም" በዓል በሰላም አደረሳችሁ +"+

+*" ድንግል ማርያም "*+

=>የአምላክ እናቱ እመ-ብርሃን ድንግል ማርያም:-
*በ3 ወገን (በሥጋ: በነፍስ: በልቡና) ድንግል
*በ3 ወገን (ከኀልዮ: ከነቢብ: ከገቢር) ንጽሕት
*ሳትጸንስ: በጸነሰች ጊዜና ከጸነሰች በሗላ ድንግል
*ጌታን ሳትወልድ : በወለደችው ጊዜና ከወለደችው በሗላ ድንግል ስትሆን እናትም ድንግልም መሆኗን አምነን እመሰክራለን::

+እመቤታችን ከፍጥረት ሁሉ በላይ ክብርትና ንዕድ ናት:: ሊቃውንት አበው እንዳስተማሩን በዚህ ዕለት እንዲህ ብለን እንጸልያለን::
"ረስዪ ፍና ትሕትና አእጋርየ ይሑሩ:
ትዕቢትሰ ለአምላክ ጸሩ"
(እመቤቴ ሆይ ትዕቢትን አምላክ ይጠላልና እግሮቻችን በትሕትና እንዲሔዱ አድርጊ)

+*" ቅዱስ አናሲሞስ ሐዋርያ "*+

=>በዘመነ ሐዋርያት ምስጉን ከነበሩ አበው አንዱ ቅዱስ አናሲሞስ ነው:: ስለ ቀና አገልግሎቱና መልካም እረኛነቱ አባቶቻችን ሐዋርያት አብዝተው በቀኖናቸው መስክረውለታል:: እርሱ ከኃጢአት ኑሮ ወደ ዘለዓለማዊ የቅድስና ሕይወት መጥቷልና::
¤ይህስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-

=>በሮም ከተማ የሚኖር ፊልሞና የሚባል አንድ ባለጸጋ ነበር:: ይህ ሰው በስብከተ ቅዱስ ዻውሎስ አምኖ ከርስቲያን ሆነና በመንፈሳዊ አገልግሎት ተጠመደ:: ነገር ግን ከአገልጋዮቹ መካከል ያላመነ አንድ ሰው ነበር:: "ተጽዕኖ አላደርግበትም" ብሎ ዝም ይለዋል:: ግን ክርስትና እንዲገባው ለተልዕኮ መንፈሳዊ በሚሔድበት ሥፍራ ያስከትለው ነበር::
+አገልጋዩ ግን በመለወጥ ፈንታ ሌብነትን ለመደ:: ይባስ ብሎም የአሳዳሪውን (የፊልሞናን) ገንዘብ ሠርቆ ወደ ሮም ጠፍቶ ተመለሰ:: ቅዱስ ፊልሞናም ለገንዘቡ ሳይሆን ለሕይወቱ አዘነ::

+ያ ሠርቆ የጠፋው አገልጋይ ግን በሮም ከተማ ሲመላለስ ስብከተ ወንጌልን ይሰማል:: ሰባኪው ደግሞ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ዻውሎስ ነበር:: ቁጭ ብሎ ሲማርም ልቡናው በርቶለት ተጸጸተ:: ከሐዋርያውም ዘንድ ቀርቦ ኃጢአቱን ተናዞ ተጠመቀ::
+ከዚያች ዕለት ጀምሮም ብርቱ ክርስቲያን ሆነ:: በጥቂት ጊዜም የተጋ ሰባኪ : ርሕሩሕ እረኛ ሆነ:: ፈጣሪውንም ደስ አሰኘ:: ነገር ግን ስለ አንድ ነገር ፈጽሞ ያዝን : ይተክዝም ነበር::

+የድሮ አሳዳሪው ቅዱስ ፊልሞና እንዳዘነበት እያወቀ ዝም ማለት ባያስችለው ለመምህሩ ቅዱስ ዻውሎስ ነገረው:: ያን ጊዜም ሐዋርያው በእሥራትና በግርፋት ይሰቃይ ነበር:: በሮም ሳለም አጭር ክታብ (ደብዳቤን) ጽፎ ለዚህ ደቀ መዝሙሩ ሰጠውና ወደ ቀድሞ አሳዳሪው ወደ ፊልሞና ላከው::
+ይህች ጦማር (ክታብ) ዛሬም ድረስ ከ81ዱ አሥራው መጻሕፍት : ከቅዱስ ዻውሎስ 14 መልዕክታት አንዷ ሆና ተቆጥራ እንጠቀምባታለን:: ክታቧ እጅግ አጭር ብትሆንም ምሥጢሯ ግን ሰፊ ነው::

+ያ የተላከ ክርስቲያንም ያችን ክታብ ወስዶ ለቅዱስ ፊልሞና (ለቀድሞ አሳዳሪው) አስረከበ:: ቅዱስ ፊልሞናም በደስታ አቅፎ ሳመው:: ቀድሞውንም ያዘነ በወጣቱ አገልጋይ የነፍስ እዳ እንጂ በገንዘቡ አልነበረምና:: ያ ተላኪ ሰውም በአካባቢው ሲያገለግል ቆይቶ ወደ ቅዱስ ዻውሎስ ተመልሷል:: ደቀ መዝሙሩ ሆኖም ብዙ አገልግሏል::
+#ቅዱስ_አናሲሞስ ማለት . . . የቀድሞ የሰው አገልጋይ . . . ዛሬ የክርስቶስ ባሪያ . . . ቀድሞ ሠራቂ . . . ዛሬ ግን ለመንጋው የሚራራ ሰው የሆነው ይህ ክርስቲያን ነው::

+በ67 ዓ/ም ቅዱስ ዻውሎስ መሰየፉን ተከትሎ እርሱንም አሳድደው : አሰቃይተው : ጭኑንም ሰብረው አሕዛብ ገድለውታል:: በሰማይም የሐዋርያነትና የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጅቷል:: (ጢሞ. 4:6-8, ፊልሞና 1:1-25)
=>አምላከ ቅዱሳን የአናሲሞስን መመለስ : ንስሃና በረከት ያድለን::

=>የካቲት 21 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=

1.ቅዱስ አናሲሞስ ሐዋርያ (የቅዱስ ዻውሎስ ሐዋርያ ደቀ መዝሙር ሲሆን ከ14ቱ መልዕክታት አንዱ የሆነው 'ወደ ፊልሞና' የተጻፈው በዚህ ቅዱስ ምክንያት ነው:: ፊል. 1:11)
2.አባ ዘካርያስ ዘሃገረ ስሃ
3.አባ አካክዮስ ጻድቅ
4.አባ ገብርኤል ሊቀ ዻዻሳት
5.አባ ገብርኤል (የኢትዮዽያ ዻዻስ)

=>ወርኀዊ በዓላት

1.ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያም
2.አበው ጎርጎርዮሳት
3.አቡነ ምዕመነ ድንግል
4.አቡነ አምደ ሥላሴ
5.አባ አሮን ሶርያዊ
6.አባ መርትያኖስ ጻድቅ

=>+"+ ስለ ጽዮን ዝም አልልም . . . አሕዛብም ጽድቅሽን ነገሥታትም ሁሉ ክብርሽን ያያሉ:: የእግዚአብሔርም አፍ በሚጠራበት በአዲሱ ስም ትጠሪያለሽ:: በእግዚአብሔር እጅ የክብር አክሊል በአምላክሽም እጅ የመንግሥት ዘውድ ትሆኛለሽ:: +"+ (ኢሳ. 62:1-3)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>