† † በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! † † +"+ እንኩዋን ለቅዱስ "አናሲሞስ ሐዋርያ" እና ለእመቤታችን "ቅድስት ድንግል ማርያም" በዓል በሰላም አደረሳችሁ +"+ +*" ድንግል ማርያም "*+ =>የአምላክ እናቱ እመ-ብርሃን ድንግል ማርያም:- *በ3 ወገን (በሥጋ: በነፍስ: በልቡና) ድንግል *በ3 ወገን (ከኀልዮ: ከነቢብ: ከገቢር) ንጽሕት *ሳትጸንስ: በጸነሰች ጊዜና ከጸነሰች በሗላ ድንግል *ጌታን ሳትወልድ : በወለደችው ጊዜና ከወለደችው በሗላ ድንግል ስትሆን እናትም ድንግልም መሆኗን አምነን እመሰክራለን:: +እመቤታችን ከፍጥረት ሁሉ በላይ ክብርትና ንዕድ ናት:: ሊቃውንት አበው እንዳስተማሩን በዚህ ዕለት እንዲህ ብለን እንጸልያለን:: "ረስዪ ፍና ትሕትና አእጋርየ ይሑሩ: ትዕቢትሰ ለአምላክ ጸሩ" (እመቤቴ ሆይ ትዕቢትን አምላክ ይጠላልና እግሮቻችን በትሕትና እንዲሔዱ አድርጊ) +*" ቅዱስ አናሲሞስ ሐዋርያ "*+ =>በዘመነ ሐዋርያት ምስጉን ከነበሩ አበው አንዱ ቅዱስ አናሲሞስ ነው:: ስለ ቀና አገልግሎቱና መልካም እረኛነቱ አባቶቻችን ሐዋርያት አብዝተው በቀኖናቸው መስክረውለታል:: እርሱ ከኃጢአት ኑሮ ወደ ዘለዓለማዊ የቅድስና ሕይወት መጥቷልና:: ¤ይህስ እንደ ምን ነው ቢሉ:- =>በሮም ከተማ የሚኖር ፊልሞና የሚባል አንድ ባለጸጋ ነበር:: ይህ ሰው በስብከተ ቅዱስ ዻውሎስ አምኖ ከርስቲያን ሆነና በመንፈሳዊ አገልግሎት ተጠመደ:: ነገር ግን ከአገልጋዮቹ መካከል ያላመነ አንድ ሰው ነበር:: "ተጽዕኖ አላደርግበትም" ብሎ ዝም ይለዋል:: ግን ክርስትና እንዲገባው ለተልዕኮ መንፈሳዊ በሚሔድበት ሥፍራ ያስከትለው ነበር:: +አገልጋዩ ግን በመለወጥ ፈንታ ሌብነትን ለመደ:: ይባስ ብሎም የአሳዳሪውን (የፊልሞናን) ገንዘብ ሠርቆ ወደ ሮም ጠፍቶ ተመለሰ:: ቅዱስ ፊልሞናም ለገንዘቡ ሳይሆን ለሕይወቱ አዘነ:: +ያ ሠርቆ የጠፋው አገልጋይ ግን በሮም ከተማ ሲመላለስ ስብከተ ወንጌልን ይሰማል:: ሰባኪው ደግሞ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ዻውሎስ ነበር:: ቁጭ ብሎ ሲማርም ልቡናው በርቶለት ተጸጸተ:: ከሐዋርያውም ዘንድ ቀርቦ ኃጢአቱን ተናዞ ተጠመቀ:: +ከዚያች ዕለት ጀምሮም ብርቱ ክርስቲያን ሆነ:: በጥቂት ጊዜም የተጋ ሰባኪ : ርሕሩሕ እረኛ ሆነ:: ፈጣሪውንም ደስ አሰኘ:: ነገር ግን ስለ አንድ ነገር ፈጽሞ ያዝን : ይተክዝም ነበር:: +የድሮ አሳዳሪው ቅዱስ ፊልሞና እንዳዘነበት እያወቀ ዝም ማለት ባያስችለው ለመምህሩ ቅዱስ ዻውሎስ ነገረው:: ያን ጊዜም ሐዋርያው በእሥራትና በግርፋት ይሰቃይ ነበር:: በሮም ሳለም አጭር ክታብ (ደብዳቤን) ጽፎ ለዚህ ደቀ መዝሙሩ ሰጠውና ወደ ቀድሞ አሳዳሪው ወደ ፊልሞና ላከው:: +ይህች ጦማር (ክታብ) ዛሬም ድረስ ከ81ዱ አሥራው መጻሕፍት : ከቅዱስ ዻውሎስ 14 መልዕክታት አንዷ ሆና ተቆጥራ እንጠቀምባታለን:: ክታቧ እጅግ አጭር ብትሆንም ምሥጢሯ ግን ሰፊ ነው:: +ያ የተላከ ክርስቲያንም ያችን ክታብ ወስዶ ለቅዱስ ፊልሞና (ለቀድሞ አሳዳሪው) አስረከበ:: ቅዱስ ፊልሞናም በደስታ አቅፎ ሳመው:: ቀድሞውንም ያዘነ በወጣቱ አገልጋይ የነፍስ እዳ እንጂ በገንዘቡ አልነበረምና:: ያ ተላኪ ሰውም በአካባቢው ሲያገለግል ቆይቶ ወደ ቅዱስ ዻውሎስ ተመልሷል:: ደቀ መዝሙሩ ሆኖም ብዙ አገልግሏል:: +#ቅዱስ_አናሲሞስ ማለት . . . የቀድሞ የሰው አገልጋይ . . . ዛሬ የክርስቶስ ባሪያ . . . ቀድሞ ሠራቂ . . . ዛሬ ግን ለመንጋው የሚራራ ሰው የሆነው ይህ ክርስቲያን ነው:: +በ67 ዓ/ም ቅዱስ ዻውሎስ መሰየፉን ተከትሎ እርሱንም አሳድደው : አሰቃይተው : ጭኑንም ሰብረው አሕዛብ ገድለውታል:: በሰማይም የሐዋርያነትና የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጅቷል:: (ጢሞ. 4:6-8, ፊልሞና 1:1-25) =>አምላከ ቅዱሳን የአናሲሞስን መመለስ : ንስሃና በረከት ያድለን:: =>የካቲት 21 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት= 1.ቅዱስ አናሲሞስ ሐዋርያ (የቅዱስ ዻውሎስ ሐዋርያ ደቀ መዝሙር ሲሆን ከ14ቱ መልዕክታት አንዱ የሆነው ወደ ፊልሞና የተጻፈው በዚህ ቅዱስ ምክንያት ነው:: ፊል. 1:11) 2.አባ ዘካርያስ ዘሃገረ ስሃ 3.አባ አካክዮስ ጻድቅ 4.አባ ገብርኤል ሊቀ ዻዻሳት 5.አባ ገብርኤል (የኢትዮዽያ ዻዻስ) =>ወርኀዊ በዓላት 1.ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያም 2.አበው ጎርጎርዮሳት 3.አቡነ ምዕመነ ድንግል 4.አቡነ አምደ ሥላሴ 5.አባ አሮን ሶርያዊ 6.አባ መርትያኖስ ጻድቅ =>+"+ ስለ ጽዮን ዝም አልልም . . . አሕዛብም ጽድቅሽን ነገሥታትም ሁሉ ክብርሽን ያያሉ:: የእግዚአብሔርም አፍ በሚጠራበት በአዲሱ ስም ትጠሪያለሽ:: በእግዚአብሔር እጅ የክብር አክሊል በአምላክሽም እጅ የመንግሥት ዘውድ ትሆኛለሽ:: +"+ (ኢሳ. 62:1-3) > 679 views12:46