Get Mystery Box with random crypto!

✞ ✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞ ✞ ❖ የካቲት 13 ቀን | ✞ገድለ ቅዱሳን✞

✞ ✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞ ✞

❖ የካቲት 13 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

+*" ማር ፊቅጦር "*+

=>ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በደማቸውና በገድላቸው ያስጌጡ ብዙ ሰማዕታት አሉ:: ነገር ግን ከኮከብም ኮከብ ይበልጣልና ማን እንደ ጊዮርጊስና እስጢፋኖስ! ከእነርሱ ቀጥለው ከሚጠሩ ሰማዕታት ደግሞ አንዱና ዋነኛው ቤተ ክርስቲያን "ማር" የምትለው ቅዱስ ፊቅጦር ነው::

=>እስኪ ከበዛው መዓዛ-ገድሉ ጥቂት እንካፈል:-
+ቅዱስ ፊቅጦር አባቱ ኅርማኖስ ይባላል:: አረማዊና
ጨካኝ ነው:: እናቱ ግን የተመሰገች ቅድስት ማርታ
ትባላለች:: ልጇን እንደሚገባ አሳድጋው 20 ዓመት
ሲሞላው የአንጾኪያ ንጉሥ የሠራዊት አለቃና በመንግሥቱ
3ኛ አድርጐ ሾመው::

+የድሮዋ አንጾኪያ (ሮም) እንደ ዛሬዋ አሜሪካ ዓለምን
የተቆጣጠረች ሃገር ነበረች:: ቅዱስ ፊቅጦር ደም ግባቱ
ያማረ: በጦርነትም ኃይለኛ ስለ ነበር ሁሉ ያከብሩት:
ይወዱትም ነበር::

+እርሱ ግን ቀን ቀን ሲጾም: ነዳያንን ሲያበላ ይውል
ነበር:: ሌሊት ደግሞ እኩሉን ሲጸልይና ሲሰግድ እኩሉን
የእስረኞችን እግር ሲያጥብ ያድር ነበር:: ይህ ሁሉ ሲሆንኮ
እርሱ የንጉሡ 3ኛ: የሠራዊትም አለቃ ነው:: በዘመኑ
የሚያገድፍ ምግብና የወይን ጠጅ በአፉ ዙሮ አያውቅም::

+ከነገር ሁሉ በሁዋላ ንጉሡ ዲዮቅልጢያኖስ ካደ:: ዘመነ
ሰማዕታትም ጀመረ:: አብያተ ክርስቲያናት ተቃጠሉ:: ከ47
ሚሊየን በላይ ክርስቲያኖች በመንኮራኩር ተፈጩ::
በመጋዝ ተተረተሩ:: ለአራዊት ተሰጡ:: በግፍም
ተጨፈጨፉ:: ቀባሪ አጥተውም ወደቁ::

+በዚሕ ጊዜ ማር ፊቅጦር እናቱን ቅድስት ማርታን በዕንባ
ተሰናብቶ ወደ ንጉሡ ቀርቦ በክርስቶስ ስም ታመነ::
ክፉ አባትም በልጁ ላይ ሞትን መከረ::

+ከዚያም ቅዱሱን አፉን በብረት ለጉመው ወደ ምድረ
ግብፅ አወረዱት:: መሪያቸው እንዳልነበረ ወታደሮቹ
መኩዋንንቱ ሁሉ ተዘባበቱበት:: እርሱ ከምድራዊ ንግሥና
ሰማያዊ መንግስትን: በሰዎች ፊት ከመክበር ስለ ክርስቶስ
ሲል መናቅን መርጧልና::

+ለቀናት: ለወራትና ለዓመታት መኩዋንንቱ እየተፈራረቁ
አሰቃዩት:: በርሱ ላይ ያልሞከሩት የስቃይ ዓይነት
አልነበረም:: አካሉን ቆራርጠዋል: ዓይኖቹን አውጥተዋል:
ምላሱንም ቆርጠዋል:: ሚያዝያ 27 ቀን ግን በሰይፍ
አንገቱን ቆርጠውታል:: ስለዚህም እናት ቤተ ክርስቲያን
በታላቅ ማክበር ታከብረዋለች::

❖እግዚአብሔርም ለቅዱስ ፊቅጦር እንዲህ አለው:-
"እንደ አቅሙ ስምህን የጠራ: መታሠቢያህን ያደረገ:
ስምህን ያከበረ: የብርሃን ልብስ አጐናጽፌ ወደ መንግስተ
ሰማያት አስገባዋለሁ::"

❖ይህች ቀን ማር ፊቅጦር የተወለደባት ናት፡፡ እናቱን ቅድስት ማርታ (ሶፍያንም) እናስባለን፡፡

❖ቸሩ አምላከ ፊቅጦር ሁላችንም ይማረን:: ከቃል ኪዳኑ አሳትፎ ለርስቱ ያብቃን::

✞✞ ቅዱስ አውሳብዮስ ካልዕ (ጥዑመ ዜና) ✞✞

=> ቅዱስ አውሳብዮስ በወጣትነቱ ከተባረከች ሚስቱ ጋ
በድንግልና የኖረ; በዘመኑ ባሕር ውስጥ ሰጥሞ ይጸልይ;
4,000
አቡነ ዘበሰማያት በአንድ ቀን ያደርስ የነበረ; ስለ
ሃይማኖትም በቀስት የተወጋ; በእሳት የቃጠለ; አካሉን
ቆራርጠው
የጣሉትና እግዚአብሔር ከሞት ያስነሳው ጻድቅና ሰማዕት
ነው:: ከዚህ ሁሉ ነገር በኋላ ከነሥጋው ወደ ሰማይ
ተነጥቆ ለ14
ዓመታት ቆይቷል:: ወደ ምድርም ተመልሶ ለ40 ዓመታት
በሐዋርያነት ከ85,000 በላይ አሕዛብን ወደ ሃይማኖት
መልሷል::
ጌታም በስምህ የተማጸነውን እስከ 7 ትውልድ
እምርልሃለሁ ብሎታል::"

❖አባቶቻችን ደግሞ 'ስም አጠራሩ የከበረ ዜና ሕይወቱ
ያማረ' ሲሉ ይጠሩታል::

❖ ከበረከቱ ያድለን::

✞ የካቲት 13 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ አውሳብዮስ ጻድቅ (ጥዑመ ዜና)
2.ቅዱስ ፊቅጦር ሰማዕት (ልደቱ)
3.ቅዱስ ሰርግዮስ ሰማዕት
4.ቅዱስ መፁን ቀሲስ
5.ቅዱስ ቴዎድሮስ ሰማዕት (የቅ/ፋሲለደስ ልጅ)
6.አባ ጢሞቴዎስ ሊቀ ዻዻሳት
7.አባ ክፍላ
8.አባ ኅብስ

=>ወርኀዊ በዓላት
1.እግዚአብሔር አብ
2.ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላዕክት
3."99ኙ" ነገደ መላዕክት
4.ቅዱስ አስከናፍር
5."13ቱ" ግኁሳን አባቶች
6.ቅዱስ አርሳንዮስ ጠቢብ ገዳማዊ
7.አቡነ ዘርዐ ቡሩክ

=>+"+ እግዚአብሔር ቅዱሳንን ስላገለገላችሁ : እስከ
አሁንም ስለምታገለግሏቸው ያደረጋችሁትን ሥራ :
ለስሙም ያሳያችሁትን ፍቅር ይረሳ ዘንድ ዓመጸኛ
አይደለምና:: በእምነትና በትእግስትም የተስፋውን ቃል
የሚወርሱትን እንድትመስሉ እንጂ ዳተኞች እንዳትሆኑ
ተስፋ እስኪሞላ ድረስ እያንዳንዳችሁ ያን ትጋት እስከ
መጨረሻ እንድታሳዩ እንመኛለን::+"+ (ዕብ. 6:10-13)

✞ ✞ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ✞ ✞